በ2ኛ ነገሥት የታሪክ ዘመን የነበሩ ዋና ዋና ኃይላት

የ2ኛ ነገሥት የታሪክ ዘመናት በዋና ዋና የዓለም መንግሥታት ዘንድ ከፍተኛ ትግል የተካሄደባቸው ጊዜያት እንደነበሩ 2ኛ ነገሥት ይነግረናል። የጳለስጢና ምድር በዚህ ትግል መሀል ተይዛ ጦርነትን አሳልፋለች። እስራኤላውያን የትኛውን ወገን መደገፍ እንዳለባቸው ለመወሰን የተቸገሩበት ጊዜ ነበር፤ ስለዚህ ነገሥታቱ ከአንድ ኃያል መንግሥት ጋር የነበራቸውን ስምምነት እርሱን በሚጥለው ሌላ ኃያል መንግሥት ሲቀይሩና ሲዋዥቁ እንመለከታለን። በእነዚህ ዓመታት በእስራኤልና በይሁዳ መንግሥታት ታሪክ ውስጥ ታላቅ ሚና የተጫወቱ ሦስት ዋና ዋና መንግሥታት ነበሩ።

  1. ግብፅ፡- በእነዚህ ዓመታት ግብፅ እስከዚህም ብርቱ የሆነችበት ጊዜ ጨርሶ አልነበረም። ነገር ግን ወደ ቀድሞ ስፍራዋ ለመመለስና የመካከለኛው ምሥራቅ ዋና መንግሥት የመሆን ሕልም ሁልጊዜ ነበራት፤ ስለዚህ ግብፅ ብዙ ጊዜ እንደ አሦርና ባቢሎን ካሉት ሌሎች ኃያላን መንግሥታት ጋር ግጭት በመፍጠር ጦርነትን ታካሂድ ነበር። ይህም ጦርነት ብዙ ጊዜ የሚደረገው በከነዓን ምድር ነበር። በተጨማሪ ብዙ ጊዜ ግብፅ በመሰጴጦሚያ የሚገኙ ሌሎች ግዛቶችንና መንግሥታትን ለመውጋት የእስራኤልንና የይሁዳ መንግሥታትን ድጋፍ ለማግኘት ትሞክር ነበር። ግብፅ በአሦርና በባቢሎን የተሸነፈች ብትሆንም፥ የምትገኘው እጅግ ርቃ ስለ ነበር፥ እነርሱ ሊቆጣጠሯት አልቻሉም ነበር።

በ2ኛ ነገሥት ያለው ታሪክ በተፈጸመበት ዘመን፥ ግብፅ በሁለት ዋና ዋና መንገዶች በጳለስጢና ላይ ተጽዕኖ አድርጋበት ነበር። በመጀመሪያ፥ በ609 ዓ.ዓ. ኢዮስያስ ብልህነት በጎደለው መንገድ ከግብፅ ጋር ተዋግቶ በጦርነቱ ተገደለ። ልጁም ኢዮአካዝ ወደ ግብፅ በምርኮ ተወሰደ። የግብፅ ንጉሥ በእርሱ ምትክ ኢዮአቄም የተባለውን ወንድሙን አነገሠው። 

ሁለተኛ፥ በ586 ዓ.ዓ. ኢየሩሳሌም ከተደመሰሰች በኋላ፥ ብዙ አይሁድ ተሰድደው ወደ ግብፅ ሄዱ። ነቢዩ ኤርምያስንም አስገድደው ከእነርሱ ጋር ወሰዱት። በዚያም በርካታ የሆነ የአይሁድ ኅብረተሰብ ሰፈረና ለብዙ መቶ ዓመታት በዚያ ኖረ። ሴፕቱዋጀንት የሚባለው የግሪክ ቋንቋ መጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው በ70 ዓ.ዓ. አካባቢ በግብፅ ነበር።

  1. አሦር፡- ባለፈው ሳምንት የአሦር መንግሥት በእስራኤል ሕዝብ ታሪክ ውስጥ የተጫወተውን ከፍተኛ ሚና ተመልክተናል፤ ሆኖም እስከ 853 ዓ.ዓ. ለእስራኤል መንግሥት ዋና ፈተና የነበረች ሶርያ ናት። በ745 ዓ.ዓ. በአሦር ቴልጌልቴልፌልሶር የተባለ ታላቅ ንጉሥ በሥልጣን ወንበር ላይ ተቀመጠ። የአሦርንም ግዛት ማስፋፋት ጀመረ። ለመጀመሪያ ጊዜ አንድ አገር ወርረው የሚይዙ ሕዝቦች በተወረረችው ከተማ ላይ ያደርጉት ስለ ነበረው ነገር ያስተዳደር መመሪያ ለውጥ አመጣ። ይህም ያስተዳደር መመሪያ በተወረረው አገር የሚኖሩ የሚጠቅሙ ዜጎችን የተማሩ፥ ንጉሣዊ ቤተሰብ የሆኑ፥ የሥነ-ጥበብ ሰዎች ወዘተ.) መውሰድና በግዛቷ ሁሉ ውስጥ መበተን ነበር። ሉሎች የተወረሩ ሕዝቦችን ደግሞ ወደ ሌላ የተወረረ ከተማ አምጥተው ማስፈር ነበር። ይህም ያ ሕዝብ እንደገና እንዳያንሰራራና እንዳይዋጋ የማድረጊያ ዘዴ ነበር። አሦር እስራኤልን ባሸነፈች ጊዜ ሕዝቡን ወደ ምርኮ የወሰደችውና በግዛቱ ሁሉ ውስጥ የበተነችው ለዚህ ነበር። ሕዝቡ ወደ እስራኤል እንደገና ለመመለስ ጨርሶ አልቻለም። ይህንን ልምድ አሦራውያን ብቻ ሳይሆኑ፥ ባቢሎናውያንም አደረጉት። ይሁዳን ባሸነፉ ጊዜ፥ ሕዝቡን ወደ ምርኮ ወሰዱና በባቢሎን ግዛት ሁሉ ውስጥ በተኑአቸው። የባቢሎን መንግሥት በፋርስ መንግሥት በተሸነፈና በወደቀ ጊዜ፥ ወደ እስራኤል ለመመለስ የቻሉ አይሁድ በጣም ጥቂትና የተወሰኑ ብቻ ነበሩ።

የቴልገልቴልፌልሶር ልጅ ስልምናሶር 5ኛ ከ727-722 ዓ.ዓ. የገዛ ንጉሥ ሲሆን፥ የእስራኤልን መንግሥትና የሰማርያን ከተማ የከበባትና አሸንፎ የያዛት እርሱ ነበር። አጠቃልሉ ይህን ከማድረጉ በፊት ግን ዳግማዊ ሳርጎን በተባለው የጦር ጄኔራሉ ተገደለ። ዳግማዊ ሳርጎን የሰሜኑን መንግሥት የማረከና ወደ ግዛቱም የደባለቀ ሰው ነው። 

የሳርጎን ልጅ የሆነው ሰናክሬም (704-681 ዓ.ዓ.) በኋላ በሕዝቅያስ ዘመነ መንግሥት ይሁዳን ወግቶ ወደ 200000 የሚደርሱ ሰዎች ወደ ምርኮ ቢወስድም፥ ኢየሩሳሌምን ግን ለመውጋትና አሸንፎ ለመያዝ አልቻለም፡ ኢየሩሳሌም ከመውደቋ በፊት በራሱ ሁለት ልጆቹ ተገደለ የሚቀጥለው የአሦር ንጉሥ፥ አስራዶን ይባል ነበር። የይሁዳ ንጉሥ የነበረውን ምናሴን በምርኮ ወደ ባቢሎን የወሰደ እርሱ ነበር (2ኛ ዜና 33፡10-13)። የመጨረሻው ታላቁ የአሦር ንጉሥ አሱርባኒፓል (668.630 ዓ.ዓ.) የሚባለው ሲሆን፥ እርሱም መንግሥቱን እስከ ግብፅ ድረስ አስፋፍቷል። እርሱ ከሞተ ከጥቂት ጊዜ በኋላ፥ የአሦር መንግሥት መዳከም ጀመረና በመጨረሻ በ605 ዓ.ዓ. በባቢሎናውያን ተደመሰሰ። 

  1. ባቢሎን፡- የ2ኛ ነገሥት ታሪክ በተፈጸመበት ዘመን በእስራኤል መንግሥት ላይ ተጽዕኖ ያደረገ ሦስተኛው ታላቅ መንግሥት የባቢሎን መንግሥት ነበር። የባቢሎን መንግሥት ከ626-539 ዓ.ዓ. ድረስ ጠንካራ ነበር። በአሥር እጅ በነበረችም ጊዜ የባቢሎን ምድር በጣም ታዋቂ ክፍለ አገር ነበረች። ከአሱርባኒፓል ሞት በኋላ በ633 ዓ.ዓ. የባቢሎን ከተማ በአሦር ላይ ማመፅ ጀመረ። ከ626-605 ዓ.ዓ. የባቢሎን ንጉሥ በነበረው በናቦፖላሳር አመራር የባቢሎን መንግሥት ብቅ አለና የአሦርን መንግሥት ለመጣል ቻለ። በ612 ዓ.ዓ. የአሦር ዋና ከተማ የነበረችው ነነዌ ተደመሰሰች። በ609 ዓ.ዓ. የአሦር ጦር ተደመሰሰ። ናቦፖላሳር የይሁዳን መንግሥት ጦር ማጥቃት ቢጀምርም ሊያሸንፍ ግን አልቻለም ነበር።

ከናቦፖላሳር በኋላ፥ በባቢሎን መንግሥት ውስጥ በታላቅነቱ አቻ የማይገኝለት ናቡከደነፆር ነገሠ። እርሱም ከ605-562 ዓ.ዓ. በሥልጣን ላይ ቆየ። የይሁዳ መንግሥት ሦስት ጊዜ የተጠቃውና በመጨረሻም በምርኮ የተወሰደ በእርሱ ዘመነ መንግሥት ነበር።

  1. አብዛኛው ንጉሣዊ ቤተሰብና ጠቃሚ የሆኑ ዜጎች የተወሰዱት በ605 ዓ.ዓ. ነበር። ከኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ አብዛኛው ሀብት ወደ ባቢሎን የተወሰደውና ዳንኤልና ሦስቱ ጓደኞቹ ወደ ምርኮ የተወሰዱት በዚህ ጊዜ ነበር (ዳን. 1፡1)። የይሁዳ መንግሥት የባቢሎን መንግሥት አገልጋይ የሆነውም ያኔ ነበር፡፡ 
  2. በ597 ዓ.ዓ. የሆነው ምርኮ፡- ኢዮአቄም ከግብፅ ጋር አብሮ በባቢሎን ላይ ባመፀ ጊዜ፥ ባቢሎን ኢየሩሳሌምን አጥቅታ ወረረቻት። በዚህ ጊዜ የንጉሣዊው ቤተሰብ ሌላ አባሎች የሆኑት ንጉሥ ዮአኪንና እጅግ ታዋቂ ከሆኑት 10000 ያህል የኢየሩሳሌም ዜጎች እንደነ ሕዝቅኤል ያሉት ጭምር ወደ ባቢሎን ተወሰዱ።
  3. በ586 ዓ.ዓ. የሆነው ምርኮ፡- የመጨረሻው የይሁዳ ንጉሥ ሴዴቅያስ በባቢሎን ላይ ባመፀ ጊዜ ናቡከደነፆር ትዕግሥቱን አጣ። በ588 ዓ.ዓ. ከኢየሩሳሌም ጋር መዋጋት ጀመረ። ከግብፅ ጋር ለመዋጋት ሲል ከኢየሩሳሌም ጋር የጀመረውን ውጊያ አቆመ። ከጥቂት ቆይታ በኋላ ግን በ586 ዓ.ዓ. ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰና ከረጅም ውጊያ በኋላ በወረራ ኢየሩሳሌምን ያዘ። የሴዴቅያስ ልጆች ተገደሉ። እርሱንም ዓይኑን አሳውረው ወደ ምርኮ ወሰዱት። የኢየሩሳሌም ቅጥር፥ እንዲሁም ከብዙ ዓመታት በፊት የተሠራው የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ተደመሰሱ። በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ አይሁድ በምርኮ ተወሰዱ። ድሀ የሆኑ ሰዎች ብቻ በምድሪቱ ላይ ቀሩ። ናቡከደነፆር ጎዶልያስን በይሁዳ ላይ ሾመው፤ ነገር ግን በእስማኤል ተገደለ። የቀሩትም አብዛኛዎቹ ሰዎች ወደ ግብፅ ሸሹ።

ከናቡከደነፆር ሞት በኋላ፥ የባቢሎን መንግሥት ኃይል ፈጥኖ በመቀነሱ በ539 ዓ.ዓ. በሜዶንና በፋርስ የተባበረ ኃይል ከሥልጣን ተወገደ። አይሁድን ወደ ትውልድ አገራቸው እንዲመለሱ የፈቀደ በብሉይ ኪዳን የተጠቀሰ የመጨረሻ ኃያል መንግሥት የሜዶንና የፋርስ መንግሥት ነው።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading