2ኛ ነገ. 1፡1-8፡15

  1. የነቢዩ ኤልያስ የመጨረሻ ሥራና ከዚህ ዓለም መሄዱ (2ኛ ነገ. 1-2፡18)

በ1ኛ ነገሥት መጨረሻ ላይ አካዝያስ ስለሚባል የእስራኤል ንጉሥ ተመልክተናል። አካዝያስ የነገሠው ለሁለት ዓመታት ብቻ ሲሆን፥ ከፍተኛ ውድቀት ስላጋጠመው ታመመ፤ ስለዚህ ስለ መሞቱና በሕይወት ሰለመኖሩ ለማወቅ ወደ ኤልያስ ላከ። የእግዚአብሔር ነቢይ መከበር ያለበት መሆኑንና እንደማንኛውም አገልጋይ መልእክት ተልኮበት መታዘዝ እንደሌለበት ለማሳየት፥ ኤልያስ ከሰማይ እሳት አወረደና ወደ ንጉሡ ሊወስዱት የመጡትን ሰዎች እንድትበላ አደረገ። በመጨረሻም ኤልያስ ወደ ንጉሡ ዘንድ በሄደ ጊዜ እንደሚሞት ነገረው። ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆዩ ንጉሥ አካዝያስ ሞተ።

ታማኝ የሆነውን ነቢዩ ኤልያስን እግዚአብሔር አከበረው። ሄኖክ ሞትን እንዳላየ ሁሉ ኤልያስም አልሞተም። እግዚአብሔር ሰማያዊ ሰረገሎችን ልኮ ኤልያስን ወደ መንግሥተ ሰማያት አስወሰደው። 

በብሉይ ኪዳን መጨረሻ፥ እግዚአብሔር መሢሑ ከመምጣቱ በፊት ኤልያስ እንደሚመለስ የተስፋ ቃል ሰጥቶ ነበር (ሚል.4፡5 ተመልከት)። ይህ ትንቢት በመጥምቁ ዮሐንስ ተፈጽሟል(ማቴ. 11፡14)። በአዲስ ኪዳን ኤልያስ የብሉይ ኪዳን ነቢያትን በመወከል፥ በተራራ ላይ ኢየሱስ ክርስቶስን ተገናኝቶታል (ማቴ. 17፡2-8)። 

  1. የነቢዩ የኤልሳዕ አገልግሎት (2ኛ ነገ. 2-8፡15) 

ከብዙ ዓመታት በፊት እግዚአብሔር፥ ኤልሳዕን ለነቢይነት እንዲጠራው ለኤልያስ ነግሮት ነበር። ኤልሳዕ ሀብታም ቤተሰቦቹን ትቶ (አባቱ ብዙ ጥማድ በሬዎችና አገልጋዮች እንደነበሩት አስተውል) ከኤልያስ ጋር ተጓዘ። ከኤልያስ ጋር በነበረበት ጊዜ ጌታን መውደድ ተማረ። ኤልሳዕ ልምድ ካለው ነቢይ ጋር አብሮ በመሥራት ለነቢይነት ሠለጠነ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎችን በማሠልጠን ሥራ ውስጥ፥ አዳዲስ መሪዎችን ልምድ ካላቸው መሪዎች ጋር ቀላቅሎ ማሠልጠን እንዴት ጥሩ መንገድ ሊሆን ይችላል? ለ) የቤተ ክርስቲያንህ መሪዎች ለመሪነት የሚሠለጥኑት እንዴት ነው? ሐ) ይህ ዓይነት የማሠልጠኛ ዘዴ ተግባራዊ ሊሆን የሚችልባቸውን መንገዶች ዘርዝር። 

ከኤልሳዕ ታሪክ የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡-

  1. ኤልያስ ሞትን ሳያይ ወደ ሰማይ በሚወሰድበት ጊዜ በማየት፥ በመጎናጸፊያው የተመሰለውን የኤልያስን ኃይልና ሥልጣን ተቀበለ። ኤልያስ ከሄኖክ ቀጥሉ ሞትን ሳያይ ወደ ሰማይ የተወሰደ ሁለተኛ ሰው ነው (ዘፍ. 5፡24)። 
  2. ኤልሳዕ በርካታ ተአምራትን አደረገ፡-

ሀ. መራራ ውኃን አገልግሎት ላይ ሊውል ወደሚችል ንጹሕ ውኃ ለወጠ። 

ለ. በመላጣነቱ ለመቀለድ የሞከሩ ልጆችን ድብ እንዲበላቸው አደረገ። 

ሐ. የእስራኤል ነገሥታት ለነበሩት ለኢዮሳፍጥና ለኢዮራም ከሞዓባውያን ጋር ሲዋጉ ረዳቸው። 

መ. የመበለቲቱን ዘይት በመባረክ እንዳትራብ አደረገ። 

ሠ. የሱነማይቱን ልጅ ከሞት አስነሣ። 

ረ. የተመረዘ ምግብን ሊበላ ወደሚችል ንጹሕ ምግብነት ለወጠ። 

ሰ. በ20 ዳቦ 100 ሰዎችን መገበ። 

ሸ. የሶርያ ጀኔራል የነበረውን ንዕማንን ከለምጹ አነጻው። 

ቀ. ጠፍቶ የነበረው የመጥረቢያ ዛፍ በውኃ ላይ እንዲንሳፈፍ አደረገ። 

በ. ሊይዙት የመጡትን የሶርያ የጦር ኃይላትን አሳውሮ ለእስራኤል ንጉሥ አሳልፎ ሰጣቸው። 

ተ. የሶርያ ጦር ኃይል የሰማርያን ከተማ ከመክበብ እንደሚመለሱ አመለከተ። 

ቸ. ቤንሃጻድ የሚባለው የሶርያ (አራም) መሪ እንደሚሞትና በምትኩ አዛሄል የሚባለው ሰው እንደሚነግሥ አመለከተ። ራቅ ብሎ በሚገኘው የሶርያ ግዛት ውስጥ የሚገኙ ሰዎች እንኳ፥ ኤልሳዕ የእግዚአብሔር ነቢይ እንደሆነ አውቀው ነበር። ሶርያ (አዛሄል) በእስራኤል ላይ ስለምታገኘው ድልም አስቀድሞ ተናግሮ ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ከኤልሳዕ ታሪክ ስለ ቤተ ክርስቲያን አመራር የምናገኛቸውን መንፈሳዊ ትምህርቶች ዘርዝር። ለ) ከኤልሳዕ አገልጋይ ክፉ ምኞት የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ሐ) ስለ መንፈሳዊ ዓይን ከኤልሳዕ፥ ከአገልጋዩና ከሶርያ የጦር ኃይል የምንማረው ነገር ምንድን ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: