መክብብ 1-6

የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች በተለይም ወጣቶች፡- ሀብታም፥ የተማረ፥ ጥሩ ኑሮ የሚኖርና ከፍተኛ ሥልጣን ያለው ሰው ለመሆን የሚፈልጉት ለምንድን ነው? ለ) ይህ መልካም ነውን? መልስህን አብራራ። ሐ) ለእነዚህ ነገሮች ያለው አመለካከት ሚዛናዊነት ለጐደለውና ያለ እግዚአብሔር ከንቱና እርባናቢስ መሆናቸውን ላልተገነዘበው ሰው እንዴት ትመክረዋለህ? 

የውይይት ጥያቄ፥ መክብብ 1-6 አንብብ። ሀ) የመጽሐፈ መክብብ ጸሐፊ «ከንቱ» የሚላቸውን ነገሮች ዘርዝር። ለ) ጸሐፊው እነዚህ ነገሮች ከንቱ ናቸው የሚለው ለምንድን ነው? ሐ) ከእግዚአብሔር ጋር በሚደረግ ግንኙነት ሕይወት ትርጒም እንደምታገኝ ለማንጸባረቅ ጸሐፊው በእነዚህ ምዕራፎች ስለ እግዚአብሔር የሚናገረው ነገር ምንድን ነው?

1. አጠቃላይ አሳብ፡- ሕይወት ሁሉ ከንቱ ነው (1፡1-11)።

ጸሐፊው ከእግዚአብሔር የተለየን ሕይወት ሲመለከት ከንቱ ነው ከማለት በቀር ምንም ለመናገር አልቻለም። ሰው በከፍተኛ ድካም ይሠራል፤ ከዚያም ይሞታል። ከትውልድ ወደ ትውልድ ሰዎች ይሞታሉ፤ ስማቸውን እንኳ የሚያስታውስ የለም። ሕይወት የከንቱ ድግግሞሽ የማያቋርጥ ዑደት ይመስላል። 

2. የዓለም ጥበብ ከንቱ ነው (መክብብ 2፡12-18)። ጸሐፊው ጥበብን ለመመርመር የተቻለውን ያህል ጥረት አድርጓል፤ ነገር ግን በተመራመረ ቊጥር፥ በምድር ላይ የሚያየው ነገር የበለጠ እያሳዘነው ሄደ። ጥበብ ከአላዋቂነት የሚሻል ቢሆንም፥ በመጨረሻ ግን ጥበበኛውም ሆነ ሞኙ ይሞታሉ። ከሞቱ በኋላ ሁለቱም ይረሳሉ፤ ስለዚህ አንዱ ከሌላው አይሻልም። 

3. ዓለማዊ ደስታ ከንቱ ነው፤ (መክብብ 2፡1-11)። ለመሆኑ ሳቅና ደስታ ምን ትርጕም አላቸው? ጸሐፊው ብዙ ወይን በመጠጣትና በመሳቅ በሕይወት ደስ ለመሰኘት ሞክሯል። በተጨማሪ ታላላቅ ሕንጻዎችን ከገነባ፥ መዝናኛዎችን ካቋቋመ። በርካታ አገልጋዮችና ቁሳቁስ ካለው፥ ደስተኛ እንደሚሆን አስቦ ነበር፤ ዳሩ ግን ከእነዚህ ነገሮች አንዳቸውም እውነተኛ ደስታን ወይም የሕይወት ዓላማ ሊያስጨብጡት አልቻሉም፤ ከንቱዎች ነበሩና። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ሀብት አንድን ሰው ደስተኛ የሚያደርገው ይመስልሃል? መልስህን አብራራ። ለ) መልስህን የሚደግፉ ምስሌዎችን ከሰዎች ሕይወት ስጥ።

4. በትጋት መሥራት እርካታን አያስገኝም (መክብብ 2፡17-23)። ሰው እጅግ ጠንክሮና ተግቶ ሊሠራ ይችላል፤ በሚሞትበት ጊዜ ግን የድካሙ ፍሬ ሁሉ ለሌሎች ይሆናል። በዚያን ጊዜ የደከመበትን ነገር ሁሉ ስለሚያጣ በድካሙ ሁሉ ላይ የበላይ ተቆጣጣሪ ሊሆን አይችልም። ሞኝ ሰው የደከመበትን ሁሉ ሊያጠፋና ሊያበላሽ ይችላል፤ ስለዚህ ብዙ ሀብት ለማግኘት ጠንክሮና ተግቶ መሥራቱ ከንቱ ነው። ሰው ልክ እንደ እንስሳት ሞቶ ወደ ዐፈርና ወደ ትቢያ መመለሱ ስለማይቀር ከእንስሳት አይሻልም። 

5. ሕይወት በፍትሐዊነት የተሞላች ናት (መክብብ 5፡8-9)። በምድራዊ መንግሥታት ዘንድ ብዙ ጊዜ የፍርድ መዛባትን እናያለን። በምድር ላይ በክፋትና በኃጢአት ከመኖር ይልቅ የዚህ ዓይነቱን ክፋትና ኃጢአት ላለማየትና ላለመልመድ አለመወለድ ይሻል ነበር (መክብብ 2፡16፤ 4፡1-3)። በመንግሥት አመራር ውስጥ የተለያየ ደረጃ ባላቸው ሰዎች ዘንድ ራስ ወዳድነትን አስከትሏል። ባላቸው ሥልጣንና ሀብት ከቶ ስለማይረኩ ያለማቋረጥ ባላቸው ነገር ላይ ለመጨመር ይፈልጋሉ፤ ስለዚህም የበታቾቻቸውን ይጨቁናሉ። 

6. ሰዎች፥ ሀብት ደስታን ያስገኛል ብለው ቢያስቡም፥ ፍጹም አያስገኝላቸውም (መክብብ 5፡10-6፡12)። ሀብት ያላቸው ሰዎች ነጋ ጠባ በያዙት ላይ ለመጨመር ይጥራሉ እንጂ በፍጹም አይረኩም። ሰው በርካታ ሀብትና ቁሳቁስ ሲኖረው ሌቦች ይሰርቁብኛል ብሉ ይጨነቃል። ዳሩ ግን ሰው በሚሞትበት ጊዜ ሀብቱን ይዞ ሊሄድ አይችልም። ይህም ደግሞ ከንቱ ነው። ሰው ባለው ቢደሰት ይሻላል፡፡ ሰዎች ከሚፈልጓቸው ከንቱ ነገሮች በተቃራኒ፥ ጸሐፊው እውነተኛ ደስታና እርካታ የሚሰጡትን ነገሮች አመልክቷል። አንድ ሰው በሕይወቱ ትርጕም ያለው ኑሮ ሊኖር የሚችለው ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ሲኖረው ብቻ ነው። ጸሐፊው የሚሰጠውን የሚከተለውን ምክር አስተውል፡- 

1. ሰው ሕይወትን የተቀበለው ከእግዚአብሔር እጅ መሆኑን በመገንዘብ ደስ ሊለው ይገባል (መክብብ 2፡24)። እግዚአብሔር በሰው ልብ ውስጥ ዘላለማዊ አምላክ ከሆነው ከእርሱ ጋር ኅብረት የማድረግን ፍላጎት ወይም «ዘላለማዊነትን» ሰጠው። ሙላትና እርካታ ሊኖር የሚችለው በዚያ ግንኙነት ውስጥ ብቻ ነው (መክብብ 3፡1-14)። ሁልጊዜ የተሻለና የበለጠ ነገር ከመፈለግ ይልቅ እግዚአብሔር በሰጠን ነገር መመራትና መርካት አስፈላጊ ነው (መክብብ 5፡18-20)። 

2. እግዚአብሔር እውነተኛ ጥበብን የሚሰጠው፥ ሰው ከእርሱ ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ሲኖረው ብቻ ነው (መክብብ 2፡26)። 

3. ሰው በፈራጁ በእግዚአብሔር ፊት ተጠያቂ መሆኑን ማስታወስ አለበት (መክብብ 3፡15)። 

4. ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት ሃይማኖታዊ ሥርዓት ብቻ ሳይሆን፥ ልባዊና በተግባርም የሚገለጥ መሆን አለበት (መክብብ 5፡1-7)። ሰው ወደ እግዚአብሔር ፊት መምጣት ያለበት መሥዋዕቶች በሚቀርቡበት ባዶ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ወይም በበርካታ ከንቱ ቃላት ሳይሆን፥ እርሱ የሚለውን በፍርሃትና በአክብሮት ለመስማት መሆን አለበት። ለእግዚአብሔር የሚነገሩ ቃላት ከእውነተኛ ልብ የመነጩ መሆን አለባቸው። በእግዚአብሔር ፊት የምናደርጋቸው ስእለቶች የቱንም ያህል ዋጋ ቢያስከፍሉንም እንኳ መጠበቅ አለባቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ወጣት ክርስቲያኖች በሰው ሕይወት ውስጥ ከፍተኛና ከሁሉ የላቁ ነገሮች፡- ትምህርት (ጥበብ)፥ ሀብት፥ ቁሳዊ ነገሮች፥ ወዘተ. እንደሆነ በማሰብ በአጉል ወጥመድ ሊጠመዱ የሚችሉባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ለ) አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ከሌለው፥ እነዚህ ነገሮች ሁሉ ከንቱ መሆናቸውን እነዚህ ምዕራፎች የሚያሳዩት እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “መክብብ 1-6”

Leave a Reply to Habtamu DoriCancel reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading