ሰዎች ስለ ወደፊቱ ለማወቅ ያላቸው ጉጉት አብሯቸው የኖረ ሲሆን ብዙ ነቢያት (እውነተኞቹም ሆኑ ሐሰተኞቹ) ይህን የሰው ፍላጎት ለማርካት ጥረት አድርገዋል። መተንበይ አደገኛ ሥራ ነው ምክንያቱም ትንበያው ስሕተት በሆነ መጠን፥ በአገልግሎቱ መቀጠሉ አስቸጋሪ እየሆነ ይሄዳል። በብሉይ ኪዳን ዘመን አንድ ነቢይ በእግዚአብሔር ስም መናገር ካቃተው፥ ወይም የተናገረው ትንቢት ባይፈጸም ያለ ምሕረት ይወገር ነበር (ዘዳግ. 13፡1-11፥ 18፡20-22)። አልፎ አልፎ ትክክለኛ ነገር ያመለከቱ ሐሰተኛ ነቢያት ቢነሱም (ይህ ዛሬም እንደተከሰተ ነው)፥ መልእክታቸው ቀደም ሲል እግዚአብሔር ለሕዝቡ በሰጠው እውነተኛ ትንቢቶች ይመዘን ነበር። እነዚህም ነቢያት ሚዛን ካላነሱ ይወገሩ ነበር። በመጽሐፍ ቅዱስ የተነገሩ ትንቢቶች በትክክል መፈጸማቸው ተረጋግጧል። ይህም ያልተፈጸሙ ትንቢቶች በጽሑፍ በሰፈረው መሠረት በትክክል እንደሚከናወኑ እርግጠኛ ያደርገናል። የወደፊቱን ሁኔታ በሚመለከት ብዙዎች አይስማሙም። ከዚህም የተነሳ ትንቢትን በመተርጎም ረገድ በቤተ ክርስቲያን ሦስት መሠረታዊ አመለካከቶች አሉ። እነዚህም እግዚአብሔር ከአይሁዳውያን፥ በተለይ ከአብርሃም ጋር ከገባው ቃል ኪዳን ጋር የሚያያዙ ናቸው። እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባው ቃል (ዘፍጥ. 12፡1-3) እየቆየ ሊረጋገጥና ይፋ ሊሆን ችሏል (ዘፍጥ. 13፡14-17፥ 15፡1-7፥ 17፡1-18)። አብርሃም በጊዜያዊና በመንፈሳዊ በረከቶች ሁሉ እንደሚባረክ በዚህ ቃል ኪዳን ተገልጧል። በዚህም መሠረት ርስት፥ ባሪያዎች፥ መንጋዎች፥ ብርና ወርቅ ማግኘቱ ሲታይ (ዘፍጥ. 13፡14-15፥ 17፤ 15፡7፣ 24፡34-35)፣ ከእግዚአብሔር ጋር ደስ የሚያሰኝ ኅብረት ስለነበረው የእግዚአብሔር ወዳጅ ተብሎ ለመጠራትም በቅቷል (ዘፍጥ. 18፡17፤ ያዕ. 2፡23)። እነዚህ ትንቢቶች ልክ በተነገሩት አኳኋን ተፈጽመዋል፡፡ ለአብርሃም ልጆችና ለእስራኤል ለራሷም በዚያ ቃል ኪዳን ተስፋ ተሰጥቷቸው ነበር። እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ከአብርሃም ልጆች ጋር እንደሚቀጥልና (ዘፍጥ. 17፡7)፣ ቁጥራቸው እንደ ባሕር አሸዋ የበዛ ታላቅ ሕዝብ እንደሚያደርጋቸው ተናግሯል (ዘፍጥ. 12፡2፥ 13፡16፥ 15፡5)። የሚደንቀው የአብርሃም ልጆች የሆኑት አይሁዳውያን ዛሬ የሚኖሩበት መሬት ዳርቻውና ክልሉ ቀደም ብሎ በተስፋ መገለጡና ለዘላለምም የነርሱ ርስት እንደሚሆን መነገሩ ነው (ዘፍጥ. 15፡18፣ 17፡8)። ቃል ኪዳኑ ሌሎች ሕዝቦችን የሚጨምር ተስፋ ነበር። አብርሃምንና ልጆቹን የሚባርኩ እንደሚባረኩና፥ የሚረግሟቸው ደግሞ እንደሚረገሙ ተናግሯል። ይህ በአብርሃም የሕይወት ዘመን የተረጋገጠ ጉዳይ ነው (ዘፍጥ. 14፡12-20፥ 20፡2-18)። በእስራኤል ልጆች ልምምድ ውስጥ እንዲሁ (ዘዳግ. 30፡7፤ ኢሳ. 14፡12)፥ ትንቢቱ ወደፊት በሚጠበቀው የፍዳ ዘመንም ይሠራል (ማቴ. 25፡40)። የምድር ነገዶች ሁሉ በአብርሃም እንደሚባረኩ ተስፋ ነበር። እግዚአብሔርም በእስራኤል በኩል መጽሐፍ ቅዱስን በመስጠትና ከአብርሃም ዘር የሆነ ክርስቶስን በመላክ ቃሉን ፈጽሟል(ገላ. 3፡16)። ለአብርሃም የተገባው የተስፋ ቃል አብዛኛው የተፈጸመ ለመሆኑ ሰዎች ሁሉ ይስማማሉ። የእስራኤልን ምድር በተመለከተ የተሰጠው የተስፋ ቃል ግን ሙሉ በሙሉ ተፈጽሟል ለማለት አይቻልም። የምድሪቱ ዳርቻ “ከግብፅ ወንዝ ጀምሮ እስከ ኤፍራጥስ ወንዝ ድረስ” (ዘፍጥ. 15፡18) መሆኑ ተገልጧል። የምድሪቱ ምሥራቅ ዳርቻ የኤፍራጥስ ወንዝ እንደሚሆን ሰዎች ሁሉ ይስማማሉ። የግብፅ ወንዝ የተባለው የቱ ነው? ለሚለው ጥያቄ ነው የተለያየ መልስ ያላችው። አንዳንዶቹ ወንዝ የሚለው ቃል አባይን ያመለክታል ሲሉ፥ ሌሉቹ ደግሞ ዋደ ኤል አሪሽ የተባለውንና ከጋዛ እጅግም የማይርቀውን ወንዝ ይጠቅሳል ይላሉ። ከሁለቱም አመለካከት አቅጣጫ ሲታይ እስራኤል በታሪኳ እስከዛሬም ቢሆን እነዚህን ድንበሮች አልያዘችም፡፡ ለአብርሃም በተሰጠው ቃል ኪዳን ላይ የሚነሳው ሌላ ጥያቄ የተስፋው ቃል በታዛዥነት ላይ የተመሠረተ ነው፥ ወይስ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ ይፈጸማል? የሚል ነው። ተስፋው በአይሁድ ታማኝነትና መልካምነት ላይ የተመሠረተ ከሆነ፣ ስለ ፍልስጥኤም የተባለው ነገር እና በቃል ኪዳኑ የተሰጠው በረከት ሁሉ ተሰርዟል ማለት ነው። ምክንያቱም የአይሁድ ሕዝብ ደግሞ ደጋግሞ ኃጢአት ሠርቷል። ተስፋው በእግዚአብሔር ታማኝነት ላይ የሚመሠረት ከሆነ ግን በሰው መታመን ወይም አለመታመን ሳይታገድ ይፈጸማል። ቃል ኪዳኑ በቅድመ ሁኔታ ላይ ለመመሥረት ወይም ላለመመሥረቱ ጥያቄ መልስ የሚሆነን ነገር ስዘፍጥረት 15፡9-17 ላይ የሚገኝ ሲሆን፥ ይህም እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ለማጽናት ያደረገው ተግባር ነው። በእነዚያ ጊዜያት ቃል ኪዳንን ለማጽናት የተለመደው መንገድ በመጀመሪያ እንስሳትን መሥዋዕት ማድረግ፥ ከዚያም እንስሳቱን ቆራርጦ መሬት ላይ ማስቀመጥ ነበር። በቃል ኪዳኑና በተለመደው አሠራር መሠረት ቢሆን ሁለቱ ተስማሚ ወገኖች በመሥዋዕቱ መካከል መሄድ ይገባቸው ነበር። በዚህ አሠራር ግን አሰገራሚና ልዩ ሁኔታ ታይቷል። እግዚአብሔርና አብርሃም በመሥዋዕቱ መካከል አልተመላለሱም። በዚያ ፈንታ እግዚአብሔር በአብርሃም ላይ ከባድ እንቅልፍ ጣለበትና ብቻውን በመሥዋዕቱ መካከል አለፈ። ይህ የሚያሳየን እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ብቻውን የሚጠብቅ መሆኑን ነው። በተጨማሪም ቃል ኪዳኑ ለአብርሃም፥ ለይስሐቅ፥ ለይስሐቅም ልጅ ለያዕቆብ፥ እንደገና ተረጋግጧል (ዘፍጥ. 26፡2-4፥ 28፡13-15)። በዚህ ጊዜ ሁሉ ለትንቢቱ ፍጻሜ ቅድመ ሁኔታ ያልተጠቀሰ ሲሆን፥ እግዚአብሔር ለአብርሃም ማረጋገጫውን ያጸናለት ያለ ቅድመ ሁኔታ የገባውን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ ብቻ ነው። ከዚህም ሌላ ቃል ኪዳኑ በተሰጠበትና ለይስሐቅ በተረጋገጠበት ጊዚ መካከል አብርሃም ኃጢአት ፈጽሞ ነበር። ታዲያ ቃል ኪዳኑ የታዛዥነት ቅድመ ሁኔታ ቢኖረው ኖሮ፥ በአብርሃም አለመታዘዝ ምክንያት በተሰረዘ ነበር (ዘፍጥ. 12፡10-20)። በትክክል ለመናገር ለቃል ኪዳኑ ተፈጻሚነት በአንዳንድ መለስተኛ ጉዳዮች ላይ ቅድመ ሁኔታዎች መኖራቸው ቢታይም፥ ለቃል ኪዳኑ አጠቃላይ ፍጻሜ ግን ግዴታ አልነበረም። በእስራኤል ታሪክ ውስጥ የተስፋይቱን ምድር ለጊዜውም ቢሆን፥ በከፊል ለመውረስ ታዛዥነት እግዚአብሔር የጠየቀው ግዴታ የነበረ ሲሆን፥ አለመታዘዝና ኃጢአት መፈጸምም የመበተንን ፍርድ ያስከትል ነበር (ዘዳግ. 28፡25፤ ኤር. 25፡11)። ይሁን እንጂ የቃል ኪዳኑ መጨረሻ በእግዚአብሔር ይከናወናል፤ እስራኤልም በመሢሁ በምትገዛበት ዘመን ወደ ፍጹም ታዛዥነት ትለወጣለች። ለዳዊትና ለልጆቹም እግዚአብሔር እንደዚሁ “በዳዊታዊ ቃል ኪዳን” በጣም ጠቃሚ የሆኑ ቃል ኪዳኖች ገብቷል (2ኛ ሳሙ. 7፡12-16)። ቤተ መቅደሱን የሚገነባው ዳዊት ሳይሆን ልጁ ሰሎሞን መሆኑን ጠቅሶ፥ ዙፋኑና መንግሥት በዳዊት ዘር ለዘላለም እንደሚጸና ቃል ገብቷል፡፡ ክርስቶስ ከዳዊት ዘር ለመሆኑና የተስፋ ቃል ፈጻሚ ለመሆኑ ሰዎች ሁሉ ይስማማሉ፤ ምክንያቱም ሉቃስ 1፡32-33 ይህን ስለሚያረጋግጥ ነው። እነዚህ ንጉሡንና መንግሥቱን የተመለከቱ ተስፋዎች በብሉይ ኪዳን የተደጋገሙ ቢሆንም፥ ከሁሉም ጠንከር ያለው ኃይለ ቃል በመዝሙር 89 ላይ የተጠቀሰው ነው። በዚህ ሰፍራ ጌታ አለመታዘዝን እንደሚቀጣና፥ ቃል ኪዳኑም በምንም ሁኔታ እንደማይሻር ወይም እንደማይለወጥ በተጠናከረ ሁኔታ ተገልጧል (ቁ. 30-37)። ሌሎች ተመሳሳይ ቃሎች ኢሳ. 9፡6-7፤ ኤር. 23፡5- 6፤ ሕዝ. 37 ፡24-25፤ ሆሴእ 3፡4-5፤ 152 አሞጽ 9፡11 እና ዘካ. 14፡4-9 ናቸው። እነዚህን ሁሉ የሚፈጽማቸው ክርስቶስ ስለመሆኑ የትምህርተ-መለኮት ሰዎች ሁሉ ይስማማሉ። መቼ? ለሚለው ጥያቄ የሚሰጡት መልስ ግን ተመሳሳይ አይደለም። አሁን ክርስቶስ በሰማይ ባለው የዳዊት ዙፋን ነው የተቀመጠው? ወይስ ቤተ ክርስቲያን ናት መንግሥቱ? ወይስ ይህ ሁሉ የሚፈጸመው ክርስቶስ ወደፊት መንግሥቱን ምድር ላይ በሚመሠርትበትና በሚገዛበት ጊዜ ነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች የሚሰጡት መልሶች ናቸው ስለ ወደፊቱ ሁኔታ ያሉትን አመለካከቶች የተለያዩ የሚያደርጓቸው። ስለ ሺሁ ዓመት አገዛዝ [Millenium/ሚሌኒየም] ያሉት ሦስት የተለያዩ አመለካከቶች የተመሠረቱት ለአብርሃምና ለዳዊት የተሰጧቸው ቃል ኪዳኖች ቅድመ ሁኔታዎች ነበሯቸውን? በሚለው ጥያቄ ላይ ነው። የድህረ-ሺህ ዓመት አገዛዝ አመለካከት [Postmillennialism] ይህ አመለካከት የሚያስተምረው የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ከሺህ ዓመቱ አገዛዝ በኋላ ይሆናል በማለት ነው። የዚህ አመለካከት አራማጆች በቤተ ክርስቲያን ጥረት በምድር ላይ ፍጹም የሆነ አገዛዝ ይመሠረታል በማለት ያስተምራሉ። በወርቃማው ዘመን የአብርሃምንና የዳዊትን ቃል ኪዳን የምትለማመደው ቤተ ክርስቲያን እንጂ እስራኤል አይደለችም ይላሉ። ይህ መንግሥት ምድራዊ ስለሚሆን “የቤተ ክርስቲያን መንግሥት” እንጂ የአይሁድ መንግሥት አይሆንም። ንጉሡ ክርስቶስም በምድር ላይ አይኖርም፤ የሚገዛው በሰዎች ልብ ውስጥ በማደር ሲሆን፥ ሺሁ ዓመት የአገዛዝ ዘመን ሲያበቃ ነው ወደ ምድር የሚመለሰው። በዚያን ጊዜም የሙታን አጠቃላይ ትንሣኤ ይሆንና፥ ለሰዎች ሁሉ ፍርድ ይሰጣል፤ ከዚያ በኋላ ነው ዘላለማዊ ሕይወት የሚጀመረው። በድህረ-ሺህ ዓመት አገዛዝ እምነት ተከታዮች አመለካከት መሠረት፥ ለአብርሃም የተሰጠው ቃል ኪዳን የሚፈጸመው በቤተ ክርስቲያን በኩል ቢሆንም፥ አፈጻጸሙ ቃል በቃል በሚሰጠው ትርጉም መሠረት አይደለም። የአተረጓጎም ዘዴውም ትንቢቶቹን ምሳሌያዊ ትርጉም በመስጠት ነው። የአልቦ-ሺህ ዓመት አገዛዝ አመለካከት [Amillennialism] ይህ አመለካከት ሺህ ዓመት የሚባል ነገር ጨርሶ የለም ብሎ ነው የሚያስተምረው። መንግሥት ቢኖር ያለው አሁን ነው፤ ይህም መንግሥት በቤተ ክርስቲያን ላይ ያለው