መጽሐፍ ቅዱስ፦ እስትንፋሰ- እግዚአብሔር
መጽሐፍ ቅዱስ፥ ጸሐፊዎቹ በእግዚአብሔር እየተመሩ የጻፉት ብቸኛ መጽሐፍ ነው። ይህ በእግዚአብሔር ምሪት መጽሐፍ ቅዱስን መጻፍ፥ እስትንፋሰ-እግዚአብሔር ይባላል። የእስትንፋሰ-እግዚአብሔር ትርጉም እግዚኣብሔር ሰብአውያን ጸሐፊዎችን ተጠቅሞ ለሰው ዘር ያለውን ሙሉና ተከታታይነት ያለውን አሳቡን ማስጻፉ ነው። ይህን ሲያደርግ ጸሐፊዎቹ እነሱነታቸውን፥ የአጻጻፍ ስልታቸውን እና የግል ሁኔታቸውን ሳይተዉ እንዲጽፉ ፈቅዷል። ጽሑፉን በማዘጋጀት ረገድ እግዚአብሔር በሰዎች መገልገሉ እውነት ነው። እነዚህ ሰዎች የሚጽፉትን ሁሉ ባይረዱም፥ በእግዚአብሔር እየተመሩ መጽሐፉን መጽሐፍ ቅዱስ ያሰኙትን ስድሳ ስድስት መጻሕፍት ጽፈዋል። እነዚህ መጻሕፍት አስገራሚ አንድነት ወይም ተያያዥነት ያላቸው ከመሆናቸውም ሌላ፥ የተጻፈው ቃል ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ መጻፉ ቋሚ ማስረጃዎች አሏቸው። በዚህ መሠረት መጽሐፍ ቅዱስ ምንም እንኳን በሰው ብዕር ቢጻፍ፥ ሰው ለመሰሉ ሰው የጻፈው ሳይሆን፥ እግዚአብሔር ለሰው ያስተላለፈው መልእክት ነው። መጽሐፍ ቅዱስን እግዚአብሔር ቃል በቃል አጻፈውም አላጻፈው፥ የጥንት ዘገባዎች ግልባጭ ሆነም አልሆነ፥ የሰብአዊ ጻሐፊዎች የምርምር ውጤት፥ አሳብ፥ ምኞታቸው ወይም ፍርሃታቸው ሆነም አልሆነ፥ በማንኛውም መንገድ እግዚአብሔር እርሱ የሚፈልገውን ብቻ ይጽፉ ዘንድ ጸሐፊዎቹን መርቷቸዋል። ይህ በመሆኑም መጽሐፍ ቅዱስ በትክክል የእግዚአብሔር ቃል ነው። ምንም እንኳን የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባቦች በአቀራረባቸው ምናልባት የሚለያዩ ቢሆኑ፥ እያንዳንዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እስትንፋሰ-እግዚአብሔር ነው። የእስትንፋሰ-እግዚአብሔር አስተምህሮ፥ ልዕለ ተፈጥሮ (supernatural) በመሆኑ፥ ለሰዎች ግንዛቤ አንዳንድ ችግሮች ያስከትል ይሆናል። እንዴት ነው አንድ ሰብአዊ ጻሐፊ በራሱ አሳብና እውቀት እየጻፈ፥ እግዚአብሔር እንዲመዘግብ የሚያዘውን ብቻ በትክክል ሊጽፍ የሚችለው? ይህን ከመሳሰሉ ጥያቄዎች የተነሣ፥ ሰብአዊው ጸሐፊው ምን ያህል በመለኮት ቁጥጥር ሥር ነበር? በሚለው ጥያቄ ላይ የተለያዩ አስተያየቶች ተሰንዝረዋል። እነዚህ አስተያየቶች “እስትንፋሰ-እግዚአብሔርን አስመልክቶ የቀረቡ ንድፈ-አሳቦች” ተብለዋል። ስለሆነም የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ፈቺዎች ሁሉ ከነዚህ ንድፈ-አሳቦች አንዱን ወይም ከዚያ በላይ የሆኑትን ንድፈ-አሳቦች ይከተላሉ። ተቀባይነት ያለው ንድፈ-አሳብ ለመጽሐፍ ቅዱስ ቃል አፈታት ሁሉ መሠረት የሆነው ነው። ስለሆነም ስለ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ትክክለኛ የሆነውን ንድፈ-አሳብ በጥንቃቄ መለየት ይገባል። ሀ. የእስትንፋሰ-እግዚአብሔር ንድፈ-አሳቦች 1. “ቃል” እና “ምሉእ” እስትንፋሰ-እግዚአብሔር። በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ትክክለኛው እስትንፋሰ-እግዚአብሔር የቃልና ምሉእ እስትንፋሰ-እግዚአብሔር ተብሎ ይገለጣል። “የቃል እስትንፋሰ-እግዚአብሔር” ትርጉሙ የመጀመሪያዎቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ጽሑፎች በተጻፉበት ጊዜ ጸሐፊዎቹን በቃላት አመራረጥ ሳይቀር እግዚአብሔር መርቷቸዋል ማለት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ግን የሰውን ጸሐፊነትም ያመለክታል። የተለያዩ የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት የጸሐፊዎቹን የግል ባሕርይ ሰአጻጻፍ ስልታቸውና በቃላት አመራረጣቸው የሚገልጡ ሲሆን፥ ማንነታቸውም ብዙውን ጊዜ በአስተሳሰባቸው፥ በአመለካከታቸውና በጸሎታቸው ወይም በፍርሃታቸው ይታወቃል። ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰብኣዊነት ቢኖርም፥ እስትንፋሰ-እግዚአብሔር፣ የተመዘገቡት ቃላት ሁሉ ከእግዚአብሔር እንዲሆን ያደርጋል። ይህ “ምሉእ” በመባል የሚታወቅ ሲሆን፥ ትርጉሙም (“ምሉእ እስትንፋሰ-እግዚአብሔር” ማለት ነው። ይህ አሳብ፥ ለመጽሐፍ ቅዱስ የተሰጠው እስትንፋሰ-እግዚአብሔር ግማሽ ነው የሚለውን አመለካከት ይቃወማል። ትክክለኛውና መሠረታዊው የእምነት ትምህርት ምን እንደሆነ ግልጥ ለማድረግ ብዙ ጊዜ ተጨማሪ ገላጭ ቃላት ታክለዋል። መጽሐፍ ቅዱስ ስሕተት የለሽና ትክክል መሆኑን ለመግለጥ፥ የማይሳሳት፥ የእውነት ቃል መሆኑን ለመግለጥ ደግሞ፥ ስሕተት ኣልባ ተብሏል። ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ ኣንዳንድ ጊዜ እውነት ያልሆኑ ገለጣዎችን፥ ከዚያም አልፎ ዘፍጥረት 3፡4 ላይ እንደተመለከተው፥ የሰይጣንን የሐሰት ትምህርት ቢያቀርብም፥ እነዚህ ሁሉ ሰዎችን ወይም ሰይጣንን የሚያመለክቱ እንደሆኑ በግልጥ ተጠቅሷል። እግዚአብሔርም የእነዚህን ገለጣዎች እውነትነት አላረጋገጠም። መጽሐፍ ቅዱስ ቃል በቃል እስትንፋሰ-እግዚአብሔር ነው ብሎ መግለጥ፥ እንዲሁም እውነትን በመግለጥ ረገድ ስሕተት አልባና ሐቅ ነው ማለት፥ መጽሐፉ እንደ መለኮታዊ ቃልነቱ ተዓማኒ ይሆን ዘንድ ለእያንዳንዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ልዕለ-ተፈጥሮና ፍጹም የሆነው የእግዚአብሔር ምሪት አለው ማለት ነው። እስትንፋሰ-እግዚአብሔር በእርግጥ የሚመለከተው የመጀመሪያዎቹን ወይም ዋነኞቹን ጽሑፎች እንጂ፥ ቅጂዎችንና ትርጉሞችን አይደለም። የመጀመሪያው ዋና ጽሑፍ በአሁኑ ጊዜ የሌለ ከመሆኑ የተነሣ፥ ምሁራን አሁን ያለውን መጽሐፍ ቅዱስ ትክክለኛነት ለማረጋገጥና ለመወሰን ብዙ ጥረዋል። እውነትን ለመማማር ላለን ዓላማ ግን፥ አሁን በእጃችን የሚገኙት የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂዎች፥ የመጀመሪያዎቹ ጽሑፎች ትክክለኛ ብዢዎች መሆናቸውን ለመገመት ይቻላል። በይዘት ሳይሆን፥ በአገባብ ጥቃቅን፥ ልዩነቶች ቢኖሩም፥ የመጽሐፍ ቅዱስን አስተምህሮን እምብዛም የሚያዛንፉ አይደሉም። የተገኙት ተጨማሪ ጽሑፎችም ከላይ ከተጠቀሰው የግንዛቤ መደምደሚያ ጋር ይስማማሉ። ለተግባራዊ ዓላማዎች ሲባል፥ በዕብራይስጥ የተጻፈው ብሉይ ኪዳንና በግሪክኛ የተጻፈው አዲስ ኪዳን በአንድነት፥ የእግዚአብሔር የራሱ ቃል መሆናቸውንና እርሱ ለሰው ሊያስተላልፍ የፈለጋቸው እውነቶች መሆናቸውን አምኖ ለመቀበል ይቻላል። 2. ሜካኒካዊ ወይም የቃል በቃል ንድፈ-አሳብ። ቀደም ሲል እንደተመለከተው፤ እውነተኛው እስትንፋሰ-እግዚአብሔር ቃሉ በሚጻፍበት ጊዜ፥ በእግዚአብሔር አመራር ውስጥ የጸሐፊዎችን የመጻፍ ሰብእናና ነጻነት ይፈቅዳል የሚለው እውነተኛ አስተምህሮ ተገልጧል። የዚህ ተቃራኒ አመለካከት ግን ቅዱሳት መጻሕፍት በሚጻፉበት ጊዜ፥ ሰዎች የራሳቸውን የአጻጻፍ ዘዴ ምንም ሳይጠቀሙ እግዚአብሔር እንደ ጽሕፈት መኪና ተጠቅሞባቸዋል ይላል። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን ቃል በቃል አጽፎት ሲሆን ኖሮ፥ የአጻጻፉ ስልትና ቃላቱ በአጠቃላይ አንድ ዓይነት በሆኑ ነበር። የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች የግል ፍርሃታቸውን፥ ስሜታቸውን፥ የእግዚአብሔርን ማዳን እና ጸሎታቸውን በብዙ ሁኔታዎች ገልጠዋል። በመሆኑም በተዘዋዋሪ መንገዶች የራሳቸውን ማንነት በዚሁ መለኮታዊ ጽሑፍ ውስጥ አስገብተዋል። ለምሳሌ ሮሜ 9፡1-3 ውስጥ ሐዋርያው ጳውሎስ ለእስራኤል ያደረገው ጸሎት ቃል በቃል ከእግዚአብሔር የተሰጠ ቢሆን ኖሮ ትክክለኛ ትርጉሙን ያጣ ነበር። በመሆኑም እስትንፋሰ-እግዚአብሔር እያንዳንዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል የሚመለከት ቢሆንም፥ ማንነትን፥ የአጻጻፍ ስልትን ወይም የግል ፍላጎትን አያስቀርም። መጽሐፍ ቅዱስ በአጻጻፍ ረገድ መለኮታዊውን ሥልጣን እንደሚቀበል ሁሉ፥ የጸሐፊውን ነጻነትም ያረጋግጣል። እግዚአብሔር ሰብአዊ ጸሐፊዎችን በመጠቀም ትክክለኛነትን አከናውኗል፤ ይህን ሲያደርግ ግን የቃል በቃል አጻጻፍን ተከትሎ አይደለም። አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እግዚአብሔር በቀጥታ እየተናገረ የተጻፉ መሆናቸው ተዘግቧል። አብዛኛዎቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ግን፥ ቀጥታ ቃል በቃል ለመጻፋቸው ምንም ማስረጃ ስለሌለ በሰብአዊ ጸሐፊዎች ነው የተመዘገቡት ለማለት ይቻላል። 3. ፅንሰ-ሐሳባዊ ንድፈ-አሳብ። አንዳንዶች የመጽሐፍ ቅዱስን ፍጹም እስትንፋሰ እግዚአብሔርነት በማቃለል፥ እግዚአብሔር እስትንፋሱን የሰጠው በትክክለኛዎቹ ቃላት ሳይሆን፥ ፅንሰ-አሳብን ብቻ ነው በማለት የመጽሐፉን ደራሲነት ለሰብአዊ ጸሐፊዎቹ ለመስጠት ሞክረዋል። ይህ አመለካከት ችግሮች አሉት። ምክንያቱም ሰዎች በሚጽፉበት ጊዜ እግዚአብሔር የገለጠላቸውን የተረዱት በከፊል ብቻ ቢሆንና ያን በራሳቸው ቃላት ቢያሰፍሩት ኑሮ በቀላሉ የማይገመት ችግር ያስከትሉ ነበር። ለጸሐፊዎች የተሰጧቸው ንድፈ-አሳቦች ብቻ ናቸው የሚለውን አስተያየት መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ ይቃወማል። የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በእግዚአብሔር መሪነት የተጻፈ መሆኑ ተደጋግሞ በአጽንኦት የተገለጠ እውነት ነው። የቃላት ጠቃሚነት በተደጋጋሚ ተጠቅሷል (ዘጸ. 20፡1፤ ዮሐ. 6፡63፤ 17፡8፤ 1ኛ ቆሮ. 2፡13)። ከብሉይ ኪዳን በመጥቀስ ቃላቱ ከእግዚአብሔር መሆናቸው በተደጋጋሚ ተረጋግጧል (ዮሐ. 10፡17፤ ገላ. 3፡16)። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑ ኤፌሶን 6፡17፤ ያዕቆብ 1፡21-23፤ 1ኛ ጴጥሮስ 2፡2 ውስጥ በተደጋጋሚ ተመልክቷል። ከእግዚኣብሔር ቃል ላይ በሚቀንስ በማንኛውም ሰው ላይም ከባድ እርግማን ተላልፎበታል (ራእይ 22፡18-19)። ስለዚህም ይህ ንድፈ-አሳባዊ ትንታኔ፥ ቅዱሳት መጻሕፍት ራሳቸው በእግዚአብሔር እስትንፋስ የተጻፉ ስለመሆናቸው የሚያውጁትን እውነት በተመለከተ ከትክክለኛነት የራቀ ነው። 4. ከፊል እስትንፋሰ-እግዚኣብሔር። ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰኑ ክፍሎች ብቻ ናቸው በእግዚአብሔር መሪነት የተጻፉ የሚሉ የተለያዩ ንድፈ-ሐሳቦች ተከሥተው ነበር። ለምሳሌ አንዳንዶች፥ ስለ መለኮታዊ እውነት መገለጥ የሚናገሩት የቃሉ ክፍሎች ትክክለኛ ቢሆኑም፥ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙትን ታሪካዊ፥ መልከዓ-ምድራዊ ወይም ሳይንሳዊ አባባሎችን በዚህ መልኩ ኣንቀበላቸውም ብለዋል። ከዚህ ጋር ተጓዳኝ የሆነው አመለካከት ደግሞ፥ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቂት ክፍሎች ይበልጥ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያለባቸው ስለሆኑ፥ የእውነትና የስሕተታቸው ሁኔታ የደረጃ ጉዳይ ነው የሚለው ነው። ይህም መጽሐፍ ቅዱስ በሚጻፍበት ወቅት እግዚአብሔር ጻሐፊዎቹን በተለያዩ ደረጃዎች የረዳቸው ቢሆንም፥ ያለ ስሕተት ለመጻፍ የሚያስችላቸውን ክህሎት ግን አልሰጣቸውም የሚል ነው። በመሆኑም ከፊል እስትንፋሰ-እግዚአብሔር በሁሉም አቀራረቡ የቃሉን የመጨረሻ ዳኝነት ለእያንዳንዱ አንባቢ ይተዋል። በመሆኑም በዚህ አካሄድ የቃሉ ሥልጣን፥ የአንባቢው ግለሰብ ሥልጣን ይሆንና፥ ሁለት አንባቢዎች በትክክል እውነት የሆነውና ያልሆነው የቱ ነው በሚለው እሳብ የማይስማሙበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል። 5. አዲሱ ኦርቶዶክሲ (Neo-Orthodoxy) አስተሳሰብ ስለ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያለው አመለካከት። በሀያኛው ምዕተ ዓመት ካርል ሳርት በሚባል ሰው አማካይነት አዲስ መለኮታዊ መገለጥ ማለት “እዲሱ ኦርቶዶክሲ” የተሰኘ አመለካከት ተከሠተ። ይህ አመለካከት
መጽሐፍ ቅዱስ፦ እስትንፋሰ- እግዚአብሔር Read More »