እስከ መጨረሻው ጸንቶ ስለ መገኘት የቀረበ ጥሪ (ዕብ. 10፡19–39)

የዕብራውያን ጸሐፊ ይህንን የመጨረሻ ክፍል የሚጀምረው ወደ እግዚአብሔር መቅረብ እንዳለብን፥ ይህ ካልሆነ ግን ከእምነት ርቀን በመቅበዝበዝ የእግዚአብሔርን ፍርድ እንደምንቀበል በማስጠንቀቅ ነው።

ሀ. በግላዊ እና በቅርብ ግንኙነት ወደ እግዚአብሔር መቅረብ አለብን። የክርስቶስ ሞት ኃጢአተኛ ሰዎችን ከተቀደሰው አምላክ የሚለየውን መጋረጃ ስላስወገደው እና ክርስቶስም አሁን በሰማይ በሊቀ ካህንነት እያገለገለ ስለሆነ፥ በጸሎት እግዚአብሔር ወደሚገኝበት ስፍራ የመቅረብ ድፍረት አለን። እግዚአብሔር ወደሚገኝበት ቦታ በድፍረት ለመቅረብ እራት ነገሮች ያስፈልጉናል፡

  1. ንጹህ ልብ ወይም ለእግዚአብሔር እውነተኛ ፍቅር ያለው እና ኢየሱስን ደስ ለማሰኘት የሚፈልግ ልብ። እንዲህ ዓይነቱ ልብ ሰዎችን ለማስደነቅ በመሻት የግብዝነትን ተግባር እያከናውንም። ይህ ሙሉ በሙሉ ለኢየሱስ ክርስቶስ ታማኝ የሆነ ልብ ነው።
  2. ሙሉ የእምነት ማረጋገጫ፥ ክርስቶስ ለእኛ ሲል እንደ ሞተ ሙሉ በሙሉ ማመን። ይህም ወደ እግዚአብሔር ዘንድ እንድንቀርብ መብትን ይሰጠናል። እንዲህ ዓይነት እምነት ልባችን በጥርጣሬ እንዲሞላ፥ የራሳችንን ጥረት እንድንጨምር ወይም ክርስቶስ ይቀበለን ዘንድ እርሱን ለማስደሰት እንድንሞክር እያደርገንም።
  3. ከክፉ ሕሊና ለመንጻት ልባችንን ተረጭተን። ይህ ክርስቶስ የኃጢአታችንን ዋጋ በመስቀል ላይ እንደከፈለ እና እግዚአብሔርም ይቅር እንዳለንና ንጹሐን አድርጎ እንደሚቀበለን እና መገንዘባችንን ያሳየናል። እንዲሁም፥ የእግዚአብሔር ልጆች ከመሆናችን የመነጨው ግንኙነት ለኃጢአት የማይቋረጥ እንደሆነና ኃጢአታችን በእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታ እንደተደረገለት መረዳታችንን ያሳያል።
  4. ሰውነታችንን በጥሩ ውኃ ታጥበን። ጸሐፊው ለአዲስ ኪዳን መርሆ የብሉይ ኪዳንን ምሳሌ ሲሰጥ እንመለከታለን። በብሉይ ኪዳን ዘመን፥ ካህኑ በቤተ መቅደሱ ገብቶ ከማገልገሉ በፊት በነሐስ ሳህን ውስጥ በተቀመጠው ውኃ እጁን መታጠብ ያስፈልገው ነበር። ይህም ቅዱሱን አምላክ ለማገልገል በሚዘጋጁበት ወቅት ከኃጢአት መንጻታቸውን በተምሳሌትነት ያሳይ ነበር። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ ወደ እግዚአብሔር በምንቀርብበት ጊዜ እኛም ኃጢአተኝነትን ለእግዚአብሔር በመናዘዝ ልንታጠብ ይገባል። ክርስቶስ በመስቀል ላይ የኃጢአታችንን ዋጋ ስለከፈለ፥ በእግዚአብሔር ችሎት ፊት ይቅር ተብለናል። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር ግልጽ ግንኙነት ይኖረን ዘንድ ኃጢአታችንን በኑዛዜ ውኃ ታጥበን እናጠራዋለን። (ማስታወሻ፡ ጸሐፊው በዚህ ስፍራ ስለ ጥምቀት ማስተማሩ አይደለም። እዚህ ላይ ለመግለጽ የፈለገው ከንስሐ እና ኃጢአትን ከመናዘዝ ስለሚመጣው መንጻት ነው)

ለ. እንዳይነቃነቅ የተስፋችንን ምስክርነት እንጠብቅ። ይህ ተስፋ ወንጌል ነው። ይህም መዳናችንን ብቻ ሳይሆን በመንግሥተ ሰማይ እየተጠበቅን መሆናችንን የሚያሳይ ትምህርት ነው። በመሆኑም ያመንበትን እውነት ፍርሀት እንዲነጥቅብን መፍቀድ የለብንም። ነገር ግን ዓይኖቻችንን በሰማይ ላይ ተክለን በዚያ የሚጠባበቁንን ነገሮች ልናስታውስ ይገባል።

ሐ. ለፍቅር እና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ። እያንዳንዱ አማኝ የአማኞች ኅብረት አካል መሆን ይኖርበታል። በዚህ ውስጥ እያንዳንዱ አማኝ ለመንፈሳዊ እድገቱ ተጠያቂነት ይኖረዋል። እነዚህ የቅርብ ጓደኞቻችን በሚገባ ሊያውቁን እና ድክመታችንን ሊገነዘቡ ይገባል። መውደቅ ስንጀምርም በመንፈሳዊ ሕይወታችን እንድንበረታ ሊያደፋፍሩን ያሻል። እማኞች እንደ መሆናችን፥ ለእራሳችን እምነት ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም ወገኖች ኃላፊነት አለብን። ሁሉም አማኞች በሕይወታቸው እንዲያድጉ፥ እንዲሁም እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዲመላለሱ መርዳት ይኖርብናል።

መ. ለአምልኮ መሰባሰብ አለብን። አንዳንድ ምሁራን ከስደት ፍርሃት የተነሣ አንዳንድ አማኞች ወደ ቤተ ክርስቲያን ላለመሄድ ወስነው እንደነበር ይናገራሉ። እናም ቤታቸው ውስጥ ይቀመጣሉ። ሌሎች ደግሞ አይሁዳውያን አማኞች ከአሕዛብ ክርስቲያኖች ጋር እንዳይተባበሩ የሚቀርብባቸውን ትችትና ስደት በመፍራት በአይሁዳውያን የኅብረት ቡድኖች ተወስነው ለመቅረት ያስባሉ። እነዚህ ሁለቱ ክርስቲያኖች ለስደት የሰጧቸው ምላሾች ትክክል አልነበሩም። ምክንያቱም የክርስቶስ አካል ተባብሮ ይጸና ዘንድ አማኞቹ ሁሉ ተሰባስበው እግዚአብሔርን ሊያመልኩ እና እርስ በርሳቸው ሊበረታቱ ይገባል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ከእምነታችን እንዳንወድቅ እነዚህ አራት ነገሮች መንፈሳዊ ሕይወታችንን ለማጠናከር የሚያግዙት እንዴት ነው። ለ) ስደት ወይም ችግሮች በሚመጡበት ጊዜ ሳትሰናከል ጸንተህ ትቆም ዘንድ እነዚህ አራት ነገሮች የሕይወትህ አካላት እንዲሆኑ ምን እያደረግክ ነው?

ጸሐፊው በእምነታችን እንጸና ዘንድ ልናደርጋቸው የሚገቡንን አዎንታዊ ነገሮች መዘርዘሩን አቋርጦ፥ ሌላ ጠንካራ የማስጠንቀቂያ ምንባብ ያቀርባል። አይሁዳውያን አማኞች በክርስቶስ ላይ ያላቸውን እምነት ትተው ከአሕዛብ አማኞች ጋር መሰባሰባቸውን ቢያቆሙ፥ ይህ ኃጢአት ይሆንባቸዋል።

ጸሐፊው የኃጢአት ይቅርታ የሚገኘው ከክርስቶስ ብቻ መሆኑን ገልጾአል። እነዚህ ሰዎች ክርስቶስን ከተዉት፥ ሌላ የኃጢአትን ይቅርታ የሚያገኙበት መንገድ አይኖራቸውም ነበር። ጸሐፊው በክርስቶስ ላይ የነበረውን እምነት የካደ ሰው፥ «የእግዚአብሔርን ልጅ የረገጠ፥ ያንንም የተቀደሱበትን የኪዳኑን ደም እንደ እርኩስ ነገር የቆጠረ የጸጋውንም መንፈስ ያግፋፋ» ሲል ይገልጸዋል። አሮጌውን ኪዳን መተው ከፍተኛ ቅጣት የሚያስከትል ከሆነ፥ ይህንን ታላቅ የመዳን መንገድ ቸል ማለት ደግሞ ከዚያ የከፋ ቅጣት ያስከትል ነበር። የክርስቶስ ደም ኃጢአታቸውን ካልሸፈነው፥ በሕያው እግዚአብሔር እጆች ላይ ወድቀው ፍርድን ይቀበላሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እምነታችንን ለመካድ በምንፈተንበት ጊዜ በአመዛኙ ስለ እግዚአብሔር ባህሪ የምንዘነጋው ምንድን ነው? ለ) እግዚአብሔር እምነታቸውን የሚክዱ ሰዎችን እንደሚቀጣ ማወቁ በእምነታችን እንድንጸና የሚያግዘን እንዴት ነው? ሐ) እምነታቸውን የሚክዱ ሰዎች እንዴት ክርስቶስን በእግራቸው እንደሚረግጡት፥ የክርስቶስን ሞት እንደ ከንቱ ነገር እንደሚቆጥሩና መንፈስ ቅዱስን እንደሚያግፋፉ ግለጽ።

ሠ. እግዚአብሔር ከዚህ በፊት በሕይወታችን ውስጥ እንዴት እንደሠራ ማስታወስ ይኖርብናል። ጸሐፊው እምነታቸውን ለመካድ የሚፈተኑት አይሁዳውያን አማኞች ቀደም ሲል ለክርስቶስ ምን ያህል እንደ ተሰደዱና ከሌሎች ተሰዳጅ አማኞች ጋር በእስር ቤት እንደ ተባበሩ ያስታውሳቸዋል። ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ የቀድሞው የመሥዋዕትነት ሕይወታቸው ታላቅ ሽልማት ያስገኝላቸው ነበር። ነገር ግን እምነታቸውን ለመካድ ቢወስኑ፥ ይህ ሁሉ እርባና አይኖረውም ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading