፩. በመሠረቱ የኦሪት ዘኁልቁ ታሪክ፥ የእስራኤል ሕዝብ ከሲና ተራራ ጀምሮ እስከ ከነዓን ምድር ያደረገውን ጉዞ በአጭሩ የሚያቀርብ ነው። እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ባለማመናቸው ምክንያት ወደ ከነዓን ምድር ለመግባት አለመቻላቸውንና በእነርሱ ላይ ስለ ተሠጠው የእግዚአብሔር ፍርድ የሚናገር ታሪክ ነው። በኦሪት ዘፍጥረት ተጀምሮ በዘጸአትና በዘሌዋውያንም የቀጠለው የእስራኤል ሕዝብ ታሪክ አካል ነው።
፪. እንደቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ኦሪት ዘኁልቁም ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ በግልጽ ያስተምረናል። መጽሐፉን በምታጠናበት ጊዜ፥ የሚከተሉትን የእግዚአብሔር ባሕርያት አስተውል፡-
ሀ) እግዚአብሔር ሕዝቡ በማይታዘዘው ጊዜም ቢሆን ታጋሽ ነበር። ኃጢአት በሚሠሩበት ጊዜ ጨርሶ አያጠፋቸውም። ነገር ግን ፈጥኖ ይቅር ይላቸዋል። ጸሎታቸውን ከመመለስና ፍላጎታቸውን ሁሉ ከማሟላት አይዘገይም።
ለ) እግዚአብሔር “ቀናተኛና” ቅዱስ አምላክ ነው። ለእርሱ የሚገባውን ክብሩን ለመጠበቅ ቀናተኛ ነው። እርሱ ቅዱስ ነው፤ ማለትም ኃጢአት በሚፈጸምበት ጊዜ ተገቢውን ፍርድ ይሰጣል።
ሐ) እግዚአብሔር ሕዝቡን «ለመፈተን» አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ተጠቅሟል (ዘዳ. 8፡1-2 ተመልከት)። የአዳምን (ዘፍ. 2፡15-17)፥ የአብርሃምን (ዘፍ. 22፡1-14)፥ የዮሴፍን (ዘፍ. 22፡1-17) እምነት ለመፈተን አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ተጠቀመ። እግዚአብሔር ፈተናን ወደ ሕዝቡ የሚልከው ሊያጠፋቸው ወይም ኃጢአት እንዲሠሩ ለማድረግ ሳይሆን፥ እምነታቸውን ለማጠንከር ነው።
የውይይት ጥያቄ፥ ያዕ. 1፡2-4 እና ሮሜ 5፡3-5 አንብብ። ሀ) ፈተና በሕይወታችን ውስጥ የሚቀርጻቸውንና የሚገነባችውን ባሕርያት ዘርዝር። ለ) ይህ በሕይወትህ እንዴት ሲፈጸም አየህ? ሐ) ብዙ ክርስቲያኖች በሕይወታቸው ላይ ፈተና በሚደርስበት ጊዜ የሚያጉረመርሙት ለምንድን ነው? (1ኛ ዜና 29፡17፤ ኤር. 11፡20፤ መዝ. (139)፡23፤ ኢሳ. 48፡10-11 ተመልከት)።
እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ የፈተነው ለምንድን ነው? ምናልባት ለዚህ ሦስት ምክንያቶችን መጥቀስ እንችላለን።
1) የእስራኤልን ሕዝብ ትሑት ለማድረግና የቃል ኪዳኑን ቅድመ ሁኔታዎች ለሟሟላት፥ በእግዚአብሔር ብቻ መታመን እንዳለባቸው ለማስተማር ነበር። የብርታታቸው ምንጭ እርሱ እንደሆነ እግዚአብሔር ሊያስተምራቸው ይፈልግ ነበር።
2) እስራኤላውያን የእግዚአብሔርን በረከት ለመቀበል ለእርሱ በጥንቃቄ መታዘዝና በእርሱ ላይ መደገፍ እንዳለባቸው ለማስተማር ነበር። እግዚአብሔር የሚፈልገው ከፊል መታዘዝን ሳይሆን ፍጹም የሆነ መታዘዝን ነው። እግዚአብሔርን በከፊል ብቻ ስንታዘው ዓመጽ ስለሆነ፥ ሕዝቡን ከኃጢአት ለማንጻት ፍርድን ያመጣል።
3) የእስራኤላውያንን ውስጣዊ የልብ ሁኔታ በግልጽ ለማሳየት ነበር። ነገሮች ሁሉ በተመቻቹ ጊዜ በእግዚአብሔር መደገፍ እጅግ ቀላል ነው፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ላይ በእርግጥ እንደምንደገፍ የሚያሳዩን አስቸጋሪ ጊዜያት ናቸው (ዕብ. 3፡16-4፡2)። የሚያሳዝነው ግን እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በፈተናችው ጊዜ፥ በፈተናው ወደቁ። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከግብፅ አውጥቶአቸዋል። ዳሩ ግን አሁንም የግብፅ አለማመንና ውሸት በልባቸው ስለቀረ የተቀደሰ የእግዚአብሔር ሕዝብ ሆነው ወደ ተስፋይቱ ምድር ከመግባታቸው በፊት መንጻት ነበረባቸው። ስለዚህ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ መታመንና ለእርሱ መታዘዝን ለማስተማር 38 ዓመታት በምድረ በዳ እንዲንከራተቱ ማድረግ ነበረበት።
የውይይት ጥያቄ ሀ) እነዚህ ትምህርቶች ለዛሬስ የሚያስፈልጉን እንዴት ነው? ለ) በአሁኑ ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖች ምላሽ በምድረ በዳ ከነበሩት አይሁድ ምላሽ ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ሕይወታችንን ከኃጢአት ፍላጎትና ዓለምን ከመምሰል ለማንጻት የምንቸገረው ለምንድን ነው?
መ) እግዚአብሔር ለእስራኤልና ለአብርሃም የገባውን ቃል ኪዳን ጠበቀ፡- አብዛኛዎቹ እስራኤላውያን ባለማመናቸው እግዚአብሔር ቢፈርድባቸውም፥ በትዕግሥት እርሱን ሊያከብሩ የሚችሉ ሕዝብ ያደርጋቸው ዘንድ የተለያዩ ተግባራትን ፈጸመ እንጂ፥ ሕዝቡን አላጠፋም። እግዚአብሔር ባሪያ የነበሩትን ሕዝቦችን ወሰደና አንድ ነጻ ሕዝብ በማድረግ ከእነርሱ ጋር በሲና ተራራ የገባውን ቃል ኪዳን ለመፈጸም ይችሉ ዘንድ አዘጋቸው።
ሠ) እግዚአብሔር ተከታዩ የእስራኤል ትውልድ በእርሱ ማመንና ለእርሱ መታዘዝ እንደሚገባቸው ለማስጠንቀቅ ፈልጎ ነበር። አለበለዚያ፥ አባታቸው በምድረ በዳ ያጋጠማቸው ዓይነት ፍርድ ያገኛቸዋል።
ረ) እግዚአብሔር ባለማመንና በዓመፅ ላይ ፈረደ፡፡ በብዙ ረገድ የኦሪት ዘኁልቁ ታሪክ ያለማመን፥ ያለመታዘዝና በዚህም ምክንያት በሕዝቡ ላይ የመጣው ፍርድ ታሪክ ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ በኃጢአታቸው ምክንያት ስላገኛቸው ፍርድና ሞት የተዘገበ ታሪክ ነው። ግልጽ የሆነው የኃጢአት ባሕርይ በእግዚአብሔር ላይ ፃመፅ መሆኑን ያሳያል። ኃጢአት ድንገተኛ ስሕተት ወይም ያልታሰበ ክስተት አይደለም። ሆን ብሎ በእግዚአብሔር ላይ በግልጽ ማመፅ ነው።
በመንፈሳዊ ረገድ ኦሪት ዘኁልቁ የሚናገረው፥ ስለ እምነት እርምጃ፥ ይልቁንም ያለማመን ውጤቶችን በሚመለከት ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ፥ በእምነትና በመታዘዝ ከመኖር ይልቅ፥ ባለመታዘዝና ባለማመን የመመላለስ ዝንባሌ ነበራቸው። ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ያለማቋረጥ በመንፈሳዊ ብስለት ያድጉ ዘንድ አባሎቻቸውን ሊያበረታቱ ይገባል። እኛ ወይ እያደግን ነው፥ አልያም አለማመንና አለመታዘዝ ወዳለበት ሥጋዊ ሕይወት እየተንሸራተትን ነው። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ቤተ ክርስቲያን ጥልቅ የሆነ መንፈሳዊ ሞገስዋን ትታ፥ እግዚአብሔርን በግማሽ ልብ ማምለክ እንዳትጀምር መጠንቀቅ አለባቸው። አምልኮ ሥነ-ሥርዓት ብቻ ከሆነና በቤተ ክርስቲያን አባሎች ሕይወት ውስጥ ዕለታዊ መታዘዝ እንዲኖር የማያደርግ ከሆነ፡ በመጨረሻ ያቺ ቤተ ክርስቲያን ትሞታላች።
የውይይት ጥያቄ፥ እነዚህን የኦሪት ዘኁልቁ መሠረታዊ ትምህርቶች ስትመለከት፥ ክርስቲያን ይህን መጽሐፍ ማጥናት የሚያስፈልገው ለምንድን ነው ብለህ ታስባለህ?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)