የመጽሐፈ መሳፍንት መግቢያ

የመጽሐፈ ኢያሱ ታሪክ የደስታና የድል ታሪክ ነው። የእግዚአብሔር ሰዎች በእርሱ ርዳታ በቃል ኪዳኑ ተስፋ መሠረት ጠላቶቻቸውን አሸንፈው የከነዓንን ምድር ወርሰዋል። እስራኤላውያን በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል ለተገባው ቃል ኪዳን ለመታዘዝ የሰጡትን ቃል እንደገና አደሱ። የሚገርመው ግን የዚህ ሕዝብ ታሪክ በድል አልተደመደመም። ታሪኩ በመጽሐፈ መሳፍንት ይቀጥላል።

የመጽሐፈ መሳፍንት ታሪክ የኃዘንና የሽንፈት ታሪክ ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ ለእርሱ ለመታዘዝ እምቢ አሉ። ቃል ኪዳኑንም አላከበሩም፤ ስለዚህ ለቃል ኪዳኑ መታዘዝ እንዳለባቸው ለማስተማር እግዚአብሔር በጠላቶቻቸው እንዲሸነፉ ፈቀደ። እግዚአብሔር ሕዝቡን ለማስተማርና ለማስጠንቀቅ ችግርንና ሽንፈትን በመሣሪያነት ተጠቀመ። ይህም ሆኖ ግን ሕዝቡ ለእግዚአብሔር መታዘዝን አልተማሩም።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የእግዚአብሔር ሕዝብ እግዚአብሔርን ለማክበርና ለእርሱም ለመታዘዝ የገቡትን ቃል ለመጠበቅ የሚከብዳቸው ለምንድን ነው? ለ) ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች ለኢየሱስ ያላቸውን የመጀመሪያ ፍቅራቸውን የሚተዉትና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እየቀዘቀዙ የሚሄዱት ለምንድን ነው? ) ክርስቲያኖች ለእግዚአብሔር ያላቸውን ፍቅርና መታዘዝ ሕያውና ጠንካራ አድርገው እንዲጠብቁ ቤተ ክርስቲያን ምን ማድረግ ትችላለች

የውይይት ጥያቄ፥ ስለ መጽሐፈ መሳፍንት በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ውስጥ አንብብ። ሀ) ጸሐፊው ማን ነው? ለ) የመጽሐፉ ዓላማ ምንድን ነው? ሐ) የመጽሐፉ አስተዋጽኦስ ምንድን ነው? 

የመጽሐፈ መሳፍንት ርእስ

የዚህ መጽሐፍ ርእስ የተገኘው ከኢያሱ ሞት ጀምሮ እስከ መጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ እስከ ሳኦል ድረስ የነበሩ ጊዜያዊ የአገሪቱ መሪዎች በነበሩ ሰዎች የሥልጣን ስም ነው። እነዚህ መሪዎች መሳፍንት (ፈራጆች) ተብለው የሚጠሩ ሲሆን፥ ከአስተዳዳሪነት ወይም ከፈራጅነት ይልቅ ሥራቸው ወደ ጦር መሪነት ያደላ ነበር። ለእስራኤላውያን ነፃነትን ለማምጣት እግዚአብሔር በግል የሚመርጣቸውና ኃይልን የሚያስታጥቃቸው ሰዎች ነበሩ። መሳፍንት የእስራኤልን ሕዝብ ከሚያስጨንቁአቸው ጠላቶቻቸው ነፃ ካወጡዋቸው በኋላ በነገዶቻቸው ላይ መጠነኛ የሆነ ሥልጣን ይኖራቸዋል፡፡ አንዳንዶቹ መሳፍንት ወይም ነፃ አውጪዎች በበርካታ ነገዶች ላይ ሥልጣን የነበራቸው ቢሆንም፥ ብዙ ጊዜ ግን በተወሰኑ ነዶች ላይ ብቻ ሥልጣን የነበራቸው የአካባቢ መሪዎች ነበሩ።

እግዚአብሔር በሕዝቡ ሁሉ ላይ ገዥ የሚሆን መሪን ያላስነሣው ሆን ብሎ ነበር፤ ይኸውም እግዚአብሔር ራሱ ንጉሣቸው ነበርና ነው (መሳ. 8፡23)። የተለያዩት ነገዶች በእግዚአብሔር የሚገዙና በቃል ኪዳኑ ውስጥ የሚገኙ ሕግጋትን በመታዘዝ ሊኖሩ ይገባ ነበር። እግዚአብሔር ንጉሣቸው ስለነበር ንጉሥ አያስፈልጋቸውም ነበር። በኋላ በመጽሐፈ ሳሙኤል ውስጥ እንደምንመለከተው፥ እስራኤላውያን እንደ አሕዛብ ንጉሥ እንዲኖራቸው በጠየቁ ጊዜ ድርጊታቸው በእግዚአብሔር ላይ እንደሚፈጸም ዓመፅ ተቆጥሮባቸው ነበር (1ኛ ሳሙ. 8፡5-8)።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ይህ ከእግዚአብሔርና ከመንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ከሚኖረን ግንኙነት ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ለ) የሚለየውስ እንዴት ነው?

የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ 

የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ ማን እንደሆነና እነዚህ የተለያዩ ተግባራትን አሰባስቦ በአንድ ላይ ያቀናበራቸው ማን እንደሆነ የሚያመለክት ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አናገኝም። ዓለማውያን ምሁራን መጽሐፉ የተጻፈበትን ጊዜ በማዘግየት በዚህ መልክ የጻፈው ኦሪት ዘዳግምን የጻፈውና ከኢያሱ እስከ 2ኛ ነገሥት ያለውን የታሪክ ዘገባ ያቀናበረው ሰው ነው ይላሉ። ሆኖም ለዚህ ሁሉ አንዳችም ማረጋገጫ የለም።

አይሁድ ጸሐፊው ሳሙኤል ነው ብለው ያምናሉ። ይሁን እንጂ ይህን በሚመለከት ማረጋገጫ የለንም። በዘመነ መሳፍንት የተለያዩ መሳፍንትን በሚመለከት አጫጭር ታሪኮች ሳይጻፉ አልቀሩም። በኋላ አንድ ጸሐፊ፥ ምናልባትም ሳሙኤል እነዚህን ታሪኮች ሰብስቦ በአንድ መጽሐፍ አቀነባብሮአቸው ይሆናል። 1ኛ ዜና 29፡29 እንደሚናገረው ሳሙኤል፥ ናታንና ጋድ የተባሉት ነቢያት የተለያዩ ታሪኮችን ዘግበዋል። ከብሉይ ኪዳን ጥናት እንደምንረዳው በዚሁ ጊዜ የተጻፉ ሌሎች መጻሕፍትም ነበሩ። ለምሳሌ፥ የያሻር መጽሐፍ (ኢያሱ 10፡13)፥ የእስራኤል ነገሥታት ታሪክ መጽሐፍ (2ኛ ነገ. 15፡31) እና የይሁዳ ነገሥታት ታሪክ መጽሐፍ (2ኛ ነገ. 16፡19) ይገኛሉ። እንደዚሁም በመሳፍንት መጻሕፍት ውስጥ ንጉሥ አልነበረም የሚለው ቃል ተደጋግሞ መጠቀስ የሚያመለክተን መጽሐፈ መሳፍንት ተቀናብሮ በተጻፈበት ጊዜ በእርግጥም በእስራኤል ላይ የነገሡ ነገሥታት መኖራቸው ነው።

መጽሐፈ መሳፍንትን ማን እንደጻፈው ለመናገር አስቸጋሪ ቢሆንም የተጻፈው ግን በ1000 ዓ.ዓ. ገደማ በዳዊት ዘመን እንደነበር መገመት ይቻላል። የመጽሐፈ መሳፍንት ታሪካዊ ሥረ – መሠረት ባለፈው ሳምነት የጸለስጢና ምድር የተለያዩ ትላልቅ መንግሥታት የጦርነት ሜዳ እንደነበረች ተመልክተናል። የከነዓን ምድር ከእነዚህ ትላልቅ መንግሥታት ጋር ከሚተባበሩ ከተለያዩ የከተማ መንግሥታት የተዋቀረች ነበረች። በደቡብ በኩል የሚገኘው ትልቁ መንግሥት ግብፅ ነበር። በሰሜን በኩል በኢያሱና በመሳፍንት ዘመን የነበረው ትልቅ መንግሥት የኬጢያውያን መንግሥት ነበር። እነዚህ ትላልቅ መንግሥታት በጳለስጢና ውስጥ ብዙ ጊዜ ጦርነት ይገጥሙ የነበሩ ቢሆንም፥ ይህ ጦርነት እስራኤላውያንን በከፍተኛ ሁኔታ መንካቱ አጠራጣሪ ነው። እስራኤላውያን የሚኖሩት በተራራማዎቹ ስፍራዎች ነበር እንጂ ከዋናዎቹ የንግድ መተላለፊያዎች አጠገብ አልነበረም። በአብዛኛው መሳፍንት ግብፃውያንም ሆኑ ኬጢያውያን አንዱ ሌላውን ለማሸነፍ አልቻሉም ነበር፤ ስለዚህ ከነዓን በየትኛውም መንግሥት ቀጥተኛ በበላይ ተቆጣጣሪነት ሥር አልነበረችም። በዚህም ምክንያት ብዙ ትናንሽ መንግሥታት ከነዓንን ለመቆጣጠር ወይም ለመውረርና አደጋ ለመጣል ይሞክሩ ነበር። ይህ በከነዓን ምድር ላይ የተደረገ ጦርነት በውጤቱ የተለያዩ ሕዝቦች እስራኤላውያንን ለመቆጣጠርና ለመግዛት እንደቻሉ በሚያንፀባርቅ መንገድ በመጽሐፈ መሳፍንት ተገልጧል። ከኢያሱ ሞት ጀምሮ ሳኦል እስከ ነገሠበት ጊዜ ድረስ የነበረው ሁኔታ የተለያዩ መንግሥታት እስራኤልን ያጠቁበትና የጨቆኑበት ዘመን ነበር። በእነዚህ ዓመታት ነበር የባሕር ሕዝቦች ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ፍልስጥኤማውያን በመባል የሚታወቁ አዲስ ነገዶች ወደ ከነዓን የባሕር ዳርቻ ተሰደው የመጡት። ወዲያውኑ አብዛኛውን የከነዓንን ምድር ተቆጣጠሩና ለብዙ ዓመታት የአይሁድ ሕዝብ ዋና ጠላት ሆኑ።

የእስራኤል ሕዝብ የተለያዩ ነገዶች በየራሳቸው ክልል መኖር ከጀመሩ ወዲህ የሕዝቡ አንድነት እየቀነሰ መጣ። በአንድነት እንዲቆዩ የሚያደርግ እንደ ሙሴ ወይም እንደ ኢያሱ ያለ ጠንካራ መሪ አልተገኘም፤ ስለዚህ ጎሰኝነት ወይም የዘር ልዩነት እየጠነከረ መጣና ነገዶቹ በየራሳቸው ሽማግሌዎች ወይም የነገድ አለቆች መተዳደር ጀመሩ። 12ቱን ነገዶች እጅግ በላላ መንገድ (ፈዴራላዊ አስተዳደር) እንዲቆዩ ያደረጉ ሁለት ነገሮች ነበሩ። የመጀመሪያው፥ ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡት የጋራ የሆነ አምልኮአቸው ነበር። የከነዓናውያንን አማልክት ሳይሆን እግዚአብሔርን እስካመለኩ ድረስ የተባበሩ ነበሩ። የእውነተኛውን አምላክ አምልኮ በሚተዉበት ጊዜ የጋራ የሆነ ሃይማኖት አይኖራቸውም ነበር። ሁለተኛው፥ ሁሉም የያዕቆብ ልጆች መሆናቸውና ይኸውም የጋራ ውርስ መያዛቸው ነበር፤ ስለሆነም አንድ ነገድ በውጫዊ ጠላት በሚጠቃበት ጊዜ ሌሎቹ ነገዶች ለእርዳታ መድረሳቸው የተለመደ ነበር፤ ነገር ግን ብዙ ጊዜ ይህንን አንድነት በሚረሱበት ጊዜ በ12ቱ ነገዶች መካከል የሚደረግ ጦርነትም የተለመደ ነበር።

የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ ስለ ዘመነ መሳፍንት ዝርዝር የሆነ መግለጫ የመስጠት አሳብ አልነበረውም። ለምሳሌ፡- በግብፃውያንና በኬጢያውያን መካከል ስለተደረገ ጦርነት የሚጠቅሰው አንዳችም ነገር የለም። የጸሐፊው ዋና አሳብ በዚህ ዘመን ይኖሩ የነበሩ አይሁዳውያን ላይ ለደረሰው ከፍተኛ ችግር የሥነ – መለኮታዊ ትምህርት ትንተና መስጠት ነበር። የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ትኩረት በቀድሞ ዘመናት ሁኔታ ላይ ሰፊ ገለጻ መስጠት ሳይሆን የአይሁድ መጨቆን ለምን እንደሆነ መናገር ነበር። 

የዘመነ መሳፍንት የጊዜ ቅደም ተከተል

የመጽሐፈ መሳፍትን የጊዜ ቅደም ተከተልን በተመለከተ ብዙ ክርክርና ጥርጣሬ አለ። ይህም በሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች ነው። የመጀመሪያው፥ የእስራኤል ሕዝብ ነፃ የወጡበትና ከነዓንን የወረሱበት ጊዜ ጉዳይ በሊቃውንቱ ዘንድ አከራካሪ መሆኑ ነው። ይህ ነገር የሆነው በ15ኛው ክፍለ ዘመን (1400 ዓ.ዓ.)? ነው ወይስ በ13ኛው ክፍል ዘመን (በ1280 ዓ.ዓ.)? ወግ አጥባቂ የሆኑ ምሁራን፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው መረጃ የሚስማማው ለ15ኛው ክፍለ ዘመን ቀረብ ላለው ጊዜ ነው ወደ ማለት ያዘነብላሉ።

ሁለተኛው ጥያቄ፥ መሳፍንት የገዙት በአንድ ጊዜ ነው ወይስ በተከታታይ? የሚለው ነው። እያንዳንዱ መስፍን የገዛበትን ጊዜ በተናጠል ወስደን ከደመርነው አጠቃላዩ 410 ዓመታት ይመጣል። ሁሉም ምሁራን እንደሚስማሙበት ከሆነ ይህ ጊዜ ለዘመነ መሳፍንት እጅግ ብዙ ነው፤ ስለዚህ እነዚህ የመሳፍንትን ዘመን የምናይባቸው ሁለት አማራጮች አሉን። የመጀመሪያው፥ የእስራኤል ሕዝብ የወጡበትና ሰዎች ማስታወስ ይችሉ ዘንድ ቀላል ለማድረግ የተሰጠ አጠቃላይ ጊዜ ተደርጎ የተሰጠ ነው የሚል ሲሆን፥ ሁለተኛው ግን፥ አንዳንዶቹ መሳፍንት ሌሎቹ መሳፍንት በሌላ ስፍራ በገዙበት ጊዜ የነበሩ የአንድ የተወሰነ ክልል ገዥዎች ነበሩ የሚል ነው። ለምሳሌ፡- ሶሜጋር፥ ቶላ፥ ኦጢር፥ ኢብሃን፥ ኤሉንና አብዶን ሌሎች መሳፍንት በሚገዙበት ጊዜ የተነሡ የአንድ ክልል መሪዎች ነበሩ፤ ስለዚህ የመሳፍንት የጊዜ ቅደም ተከተል በቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ካለው የጊዜ ቅደም ተከተል ጋር የሚስማማ ነው።

ዘመነ መሳፍንት ከ (1380-1050) ዓ.ዓ. ድረስ 300 ዓመታት ያህል የፈጀ ሳይሆን አይቀርም።

ቀጥሎ ለዘመነ መሳፍንት የተሰጠ የጊዜ ቅደም ተከተል እናገኛለን፡፡ 

1, ኢያሱ 1406-1376 ዓ.ዓ. 

  1. የሽማግሌዎች አገዛዝ 1376-1366 ዓ.ዓ
  2. የመስጴጦምያ የጭቆና ዘመን 1366-1358 ዓ.ዓ. 
  3. የጎቶንያል አገዛዝ የ40 ዓመት ሰላም 1358-1318 ዓ.ዓ. 
  4. በሞዓብ የመጨቆን ዘመን 1318-1301 ዓ.ዓ. 
  5. የናዖድ አገዛዝና የ80 ዓመት ሰላም 1301-1221 ዓ.ዓ. 
  6. በከነዓናውያን የመጨቆን ዘመን 1221-1201 ዓ.ዓ. 
  7. የዲቦራና የባርቅ አገዛዝ የ40 ዓመት ሰላም 1201-1161 ዓ.ዓ.
  8. በምድያን የመጨቆን ዘመን 1161-1154 ዓ.ዓ. 
  9. የጌዴዎን አገዛዝና የ40 ዓመት ሰላም 1154-1114 ዓ.ዓ. 
  10. የአቤሜሌክ- የ3 ዓመታት ንጉሥ 1114-1111 ዓ.ዓ. 
  11. የዮፍታሔ አገዛዝ -6 ዓመት 1111-1105 ዓ.ዓ.

      የሶምሶን አገዛዝ – 20 ዓመት 

  1. የዔሊ አገዛዝ 1066-1046 ዓ.ዓ. 
  2. የሳሙኤል አገዛዝ 1046-1026 ዓ.ዓ. 
  3. የሳኦል አገዛዝ 1026-1011 ዓ.ዓ. 

** እነዚህ ጊዜያት በጣም ያልተረጋገጡ እንደሆኑና የተለያዩ ምሁራን መሳፍንት የገዙበት ዘመን ብለው የሚሰጡት ጊዜ የተለያየ መሆኑን ማስታወስ አስፈላጊ ነው።

የመጽሐፈ መሳፍንት አወቃቀርና አስተዋጽኦ 

መጽሐፈ መሳፍንት ሦስት ዋና ዋና ክፍሎች አሉት፡-

  1. የዘመነ መሳፍንት መግቢያ (1፡1-3፡6)
  2. የገዙ የተለያዩ መሳፍንት (3፡7-16፡31)
  3. የዘመነ መሳፍንት አጠቃላይ የሥነ – ምግባር ባሕርያት (17-21)

የሚከተለው ጠለቅ ተደርጎ የተዘረዘረ የመጽሐፈ መሳፍንት አስተዋጽኦ ነው፡-

  1. የመጽሐፈ መሳፍንት መግቢያ(1፡1-3፡6)

ሀ. የእስራኤላውያን ከነዓናውያንን የማስወጣት ተግባራቸውን በሚገባ አለማከናወን (1፡1-2፡5) 

ለ. የእስራኤል የክሕደት ዑደት መግቢያ (2፡6-3፡6) 

  1. ስድስቱ የእስራኤላውያን የክሕደት ዑደቶች «የእስራኤል ልጆች በእግዚአብሔር ፊት እንደገና ክፉ ሥራ ሠሩ» (3፡7-16፡31)። 

ሀ. ጎቶንያል (3፡7-11) 

ለ. ናዖድ (3፡12-31) 

ሐ. ዲቦራና ባርቅ (4-5) 

መ. ጌዴዎን (6-8)

1)አቤሜሌክ (9)

2) ቶላዕና ኢያዕር (10፡1-5) 

ሠ. ዮፍታሔ (10፡6-12፡7)

1) ኢብጻን (12፡8-10) 

2) ኤሎም (12፡11-12)

3) ዓብዶን (12፡13-15) 

ረ. ሶምሶን (13-16) 

  1. እስራኤላውያን በዘመነ መሳፍንት ያሳዩት የሥዓ-ምግባር ብልሹነት፡- «ሰውም ሁሉ በፊቱ መልካም መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር» (17-21)። 

ሀ. የዳን ነገድ ታሪክ (17-18) 

ለ. የብንያም ነገድ ታሪክ (19-21) 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

2 thoughts on “የመጽሐፈ መሳፍንት መግቢያ”

  1. Tesfahun Sharifo

    Thank you

    On Thu, Feb 13, 2020, 8:49 PM ወንጌል በድረ-ገፅ አገልግሎት wrote:

    > tsegaewnet posted: “የመጽሐፈ ኢያሱ ታሪክ የደስታና የድል ታሪክ ነው። የእግዚአብሔር ሰዎች በእርሱ ርዳታ
    > በቃል ኪዳኑ ተስፋ መሠረት ጠላቶቻቸውን አሸንፈው የከነዓንን ምድር ወርሰዋል። እስራኤላውያን በእነርሱና በእግዚአብሔር
    > መካከል ለተገባው ቃል ኪዳን ለመታዘዝ የሰጡትን ቃል እንደገና አደሱ። የሚገርመው ግን የዚህ ሕዝብ ታሪክ በድል
    > አልተደመደመም። ታሪኩ በመጽሐፈ መሳፍንት ይቀጥላል። የመጽሐፈ መሳፍንት ታሪክ የኃዘንና”
    >

Leave a Reply

%d bloggers like this: