መጽሐፈ ዜና መዋዕል የተጻፈባቸው ዓላማዎች

  1. መጽሐፍ ቅዱስ የሚያተኩረው በእግዚአብሔር ላይ ነው። እርሱ የፍጥረታትና የሁሉ ጌታ እንዲሁም ታሪክን የሚመራና የሚወስን ነው። የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ትኩረትም በእግዚአብሔር ላይ ነው። ጸሐፊው ከምርኮ የተመለሱ እስራኤላውያን አሁንም እግዚአብሔር ለእነርሱ እንዴት እንደሚሠራ እንዲያዩ ይፈልግ ነበር፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በእስራኤል ሕዝብ ታሪክ ውስጥ ያለውን ሚና በመናገር ላይ አተኮረ፡፡ እስራኤልን ከዓለም ሕዝብ ሁሉ መካከል የመረጠው እግዚአብሔር ነበር (1ኛ ዜና 16፡13)። እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን መካከል በታቦቱ ፊት የሚያገለግሉ ሰዎችን ማለት ሌዋውያንን መረጠ (1ኛ ዜና 15፡2)። ዳዊትን ለንጉሥነት መረጠው (1ኛ ዜና 28፡4)። ሰሎሞንን ቤተ መቅደሱን ለመሥራት መረጠው (1ኛ ዜና 28፡5-6)። እንደዚሁም ኢየሩሳሌምን የልዩ ክብሩ መኖሪያ እንድትሆን የመረጣትና (2ኛ ዜና 6፡6) ስሙንና ክብሩን በቤተ መቅደሱ ውስጥ ያኖረው እግዚአብሔር ነው (2ኛ ዜና 7፡12፥16)።

ጸሐፊው የነገሥታትን ዘመን ታሪክ የከለሰው፥ እግዚአብሔር ዓላማውን ከዚህ በፊት በነበሩት ዘመናት እንደ ፈጸመ ለእስራኤላውያን ያለውንም ዓላማ እንደሚፈጽም ለማስተማር ነበር። እግዚአብሔር አሁንም ቢሆን ዓላማና ዕቅድ አለው። እግዚአብሔር ሕዝቡን አልተወም፥ አልረሳምም (1ኛ ዜና 17፡16-27)። ለአይሁድ የመጽሐፈ ዜና መዋዕል መልእክት የተስፋ መልእክት ነበር። እግዚአብሔር ለዳዊትና ለሰሎሞን እንዳደረገ አንድ ቀን ለእስራኤላውያን ሁሉ ያደርጋል (ዘካ. 14፡12-21)። 

የውይይት ጥያቄ፡ ሮሜ 8፡29-30 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ በአንድነት እንደመረጠ፥ እኛንስ በግል የመረጠን እንዴት ነው? ለ) እግዚአብሔር በቀድሞ ዘመን የሠራቸውን ነገሮች ማወቅ ዛሬ እኛን እንዴት ያነቃቃናል? 

  1. ጸሐፊው ዳዊትና ሰሎሞን በእስራኤል ሕዝብ ላይ ንጉሥ ይሆኑ ዘንድ እግዚአብሔር የገባላቸው ቃል ኪዳን ትክክለኞች ወራሾች መሆናቸውን በማሳየት ላይ ሊያተኩር ፈልጓል። «እውነተኞች እስራኤላውያን» በይሁዳ የነበሩትና በተለይ ደግሞ ከምርኮ የተመለሱት ነበሩ። የይሁዳ ነገድ አንድነቱን መጠበቅ አስፈላጊው ነበር፤ ምክንያቱም አንድ ቀን እግዚአብሔር በይሁዳ ሕዝብ መካከል በኃይል ለመሥራት ስለሚፈልግ ይመለሳል፤ ነገር ግን ጸሐፊው በተጨማሪ ሊያስተምር የፈለገው የእስራኤልን አንድነት በተመለከተ ነበር፡፡ በዜና መዋዕል መጽሐፍ ብዙ ጊዜ በእሥራኤል ይኖሩ የነበሩ አይሁዳውያን ወደ ይሁዳ በመምጣት እውነተኛውን እግዚአብሔርን ማምለክ እንዴት እንደቀጠሉ ተጽፏል። ከይሁዳ ነገድ የሆነው መሢሑ የዳዊት ልጅ ይመጣና ዳዊት ከዚህ ቀደም እንደነገሠው ይነግሣል። ዳዊትና ሰሎሞን በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ለሚነግሡ ሌሎች መሪዎች ሁሉ ምሳሌ ነበሩ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ከዳዊትና ከሰሎሞን ሕይወት ጥናትህ፥ ለቤተ ክርስቲያን አመራር መልካም ምሳሌዎች የሚሆኑ ነገሮች የትኞቹ ናቸው?

  1. ለእግዚአብሔር ንጹሕ የሆነ አምልኮ አስፈላጊ መሆኑን ለሕዝቡ ለማስታወስ ነበር። ከምርኮ የተመለሱት አይሁድ የቀድሞ አባቶቻቸው እንዳደረጉት የአሕዛብን የአኗኗር ዘይቤና አምልኮ የመልመድ ፈተና ደርሶባቸው ነበር። አሁን ያንን ወደ መሰለ ሁኔታ ውስጥ ለመግባት ተቃርበው ነበር፤ ስለዚህ ጸሐፊው ለሕዝቡ ስለ ንጹሕ አምልኮ ለማስተማር የቀድሞውን ነገር ተጠቀመበት። ትንሽና ኢምንት ቢመስላቸውም እንኳ በመካከላቸው ያለውን ቤተ መቅደስ ማክበር ነበረባቸው። አምልኮአቸውንም በቤተ መቅደስ ውስጥ ብቻ መፈጸም ነበረባቸው። ለእግዚአብሔር የሚሆነውን አምልኮ ለመምራት የተመረጡትን የካህናትና የሌዋውያንን ትምህርትም መታዘዝ ነበረባቸው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬስ የክርስቲያኖች አምልኮ ሊበላሽ የሚችለው እንዴት ነው? ለ) አምልኮአችን ንጹሕና እግዚአብሔርን የሚያከብር መሆኑን ለማረጋገጥ፥ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ዛሬም ማድረግ የሚችሉት ነገር ምንድን ነው? 

  1. በረከት እንዲኖር መታዘዝ መኖር እንዳለበት ለሕዝቡ ለማስታወስ ነበር። ሕዝቡ እግዚአብሔር ለሰጣቸው ሕግጋት መታዘዝ ነበረባቸው። የእግዚአብሔር መልእክተኞች የሆኑት ነቢያት፥ የእግዚአብሔርን ቃል ወደ እነርሱ ይዘው ሲመጡ ሊታዘዙአቸው ይገባ ነበር። ጸሐፊው ኃጢአት በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ የእግዚአብሔርን ፍርድ እንደሚያመጣ ሊያስታውሳቸው ይፈልግ ነበር (1ኛ ዜና 28፡9)። በተጨማሪ ደግሞ ንስሐ፥ ለእግዚአብሔር መታዘዝና በእርሱ መታመን ካለ፥ እግዚአብሔር ሰላምን፥ ድልንና ብልጽግናን እንደሚሰጣቸው ለመግለጽም ፈልጎ ነበር (2ኛ ዜና 7፡14)።

የውይይት ጥያቄ፥ ) ዛሬስ ይህ ትምህርት ለእኛ የሚያስፈልገው እንዴት ነው? ለ) አለመታዘዝ ፍርድን፥ መታዘዝ ደግሞ በረከትን ወደ ክርስቲያን ሕይወት እንዴት እንደሚያመጣ ምሳሌዎችን ዘርዝር። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading