የዜና መዋዕል ታሪካዊ ሥረ መሠረት 

የዜና መዋዕልን ዓላማ ለመረዳት መቼ እንደተጻፈና ለምን እንደተጻፈ መረዳት ያስፈልጋል። መጽሐፈ ዜና መዋዕል የተጻፈው የይሁዳ ሕዝብ በባቢሎን ከተደመሰሱ በኋላ ነበር። የይሁዳን ሕዝብ ታላቅና ልዩ ያደረጓቸው ያለፉ ነገሮች ሁሉ ጠፍተዋል። ቤተ መቅደሱ ተደምስሷል። የኢየሩሳሌም ቅጥርም ፈርሷል። ማንኛውም የዳዊት ዘር አሁን በዙፋን ላይ የለም። ከ70 ዓመታት በኋላ በ538 ዓ.ዓ. አንዳንድ ሰዎች ወደ ኢየሩሳሌም ቢመለሱም፥ የይሁዳ ሕዝብ በቁጥር ጥቂትና በፖለቲካም ደካማ ነበሩ። ይሁዳ የፋርስ መንግሥት አንደ ክፍለ ሀገር ነበረች። ሕዝቡም ራሳቸውን የቻሉ ሕዝብ ሳይሆኑ በፋርስ መንግሥት ቁጥጥር ሥር ነበሩ፡፡ ቤተ መቅደሱ የተሠራ ቢሆንም ከቀድሞው የሰሎሞን ቤተ መቅደስ ጋር ሲወዳደር በጣም ትንሽና ከመኖር የሚቆጠር አልነበረም። የኢየሩሳሌም ቅጥሮች በነህምያ መሪነት እንደገና ቢሠሩም፥ የታላቁ የዳዊት መንግሥት ዋና ከተማ የነበረችው ኢየሩሳሌም ትንሽና ደካማ ነበረች። 

ከዚህም የተነሣ የይሁዳ ሕዝብ ተስፋ ቆረጡ። «እግዚአብሔር አሁንም ከእኛ ጋር ነውን?» ብለው ጠየቁ። ከባቢሎን መፍረስ በኋላ ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረን ግንኙነት ምንድን ነው? እግዚአብሔር ከአብርሃምና ከዳዊት ጋር የገባቸው ቃል ኪዳኖች አሁንም ይሠራሉ ወይስ ቀርተዋል? ከባቢሎን ውድቀት በኋላ ለብዙ ዓመታት ስለኖሩ እግዚአብሔር የመረጠን ሕዝብ ከሆንን የይሁዳ ሕዝብ እንዲጠፉ ለምን ፈቀደ? እግዚአብሔር ስሙንና ክብሩን ለማድረግ የመረጣት ከተማ ኢየሩሳሌም ለምን ጠፋች? እነዚህና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ስለነበሩዋቸው፥ የሕዝባቸውን ታሪክ መማር ነበረባቸው። እግዚአብሔር በዓለም ሕዝብ ሁሉ ላይና በይሁዳም ላይ ያለውን የሉዓላዊነት ቁጥጥር መማር ነበረባቸው። እግዚአብሔር ከአብርሃም፥ ከእስራኤልና ከዳዊት ጋር ለገባው ቃል ኪዳን በመታዘዝ ታማኝ የመሆናቸውን አስፈላጊነት መማር ነበረባቸው። የኃጢአት ውጤት ምን እንደሆነና የእግዚአብሔርን ፍርድ እንዴት እንደሚያመጣ መረዳት ነበረባቸው። እግዚአብሔር አንድ ቀን የእስራኤልን መንግሥት ለመመለስ ጻድቅ የሆነውን ንጉሥ እንደሚያስነሣ ሊነገራቸው ይገባ ነበር። መጽሐፈ ዜና መዋዕል የማስጠንቀቂያና የማበረታቻ መጽሐፍ ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የቤተ ክርስቲያናችንን ታሪክ መረዳት የሚያበረታታን እንዴት ነው? ለ) የቤተ ክርስቲያናችንን ታሪክ መረዳት ከእውነት እንዳንርቅ የሚያስጠነቅቀን እንዴት ነው?

መጽሐፈ ዜና መዋዕል የታሪክ ዘገባውን የጀመረው ከፍጥረት መጀመሪያ ነው። ከአዳም ይጀምራል። የተለያዩ ሰዎችን የዘር ሐረግ በመመልከት፥ የእምነት መስመር ከአዳም ጀምሮ በተለያዩ የእምነት አባቶች ወደ ዳዊት እንዴት እንደደረሰ ያሳየናል። ጸሐፊው የዘር ሐረጎችን በመዘርዝር፥ የአመራር ሥልጣን ወደ ሌዋውያንና ካህናት፥ ደግሞም ወደ ዳዊትና ልጆቹ እንዴት እንደደረሰ ያሳየናል። 

በመጽሐፈ ዜና መዋዕል ውስጥ የተተነተኑት ታሪኮች ግን ዳዊት ከነገሠበት ከ 1020 ዓ.ዓ. የባቢሎን ምርኮ እስከ ሆነበት እስከ 538 ዓ.ዓ. ጊዜ ያለውን የሚያካትቱ ናቸው። ይህም ማለት ሁለቱ መጻሕፍት ከ2ኛ ሳሙኤል እስከ 2ኛ ነገሥት መጨረሻ ድረስ ያለውን ጊዜ የሚያካትቱ ናቸው ማለት ነው። 

ጸሐፊው የሚገልጸው የእነዚህን ጊዜያት ታሪክ ቢሆንም የሚያተኩረው ግን በተለዩ እውነቶች ላይ መሆኑ ግልጽ ነው። የሚከተሉትን ነገሮች ልብ ብለህ ተመልከት፡-

  1. ጸሐፊው የእግዚአብሔርን ሕልውናና ቤተ መቅደሱን በሚያመለክተው በቃል ኪዳኑ ታቦት ላይ ያተኩራል። 
  2. ጸሐፊው በሰሜኑ የእስራኤል መንግሥት ላይ ከማተኮር ይልቅ፥ በይሁዳ ላይ በነገሡት በዳዊት ልጆች ላይ ያተኩራል። በተለይ ደግሞ የዳዊት መንፈሳዊ ልጆች በመሆን በይሁዳ ምድር ሃይማኖታዊ መነቃቃትን ባመጡ ሰዎች ላይ ያተኩራል (ምሳሌ፡- አሳ፥ ሕዝቅያስ፥ ኢዮስያስ ወዘተ)።

እነዚህ ሁለት እውነቶች በጣም ጠቃሚ የሆኑት ለምንድን ነው? መጽሐፈ ዜና መዋዕል የተጻፈው ኢየሩሳሌም ከፈረሰችና ባቢሎንም ከወደቀች በኋላ መሆኑን ማስታወስ ያስፈልጋል። በእርግጥ የተጻፈው አንዳንድ የአይሁድ ቅሬታዎች ለመኖር ወደ ኢየሩሳሌም በተመለሱበት ጊዜ ነበር። ቤተ መቅደሱን ሲገነቡም እንኳ፥ ሰሎሞን የሠራው ዓይነት ቤተ መቅደስ አልነበረም። የኢየሩሳሌምን ቅጥሮች ሠርተዋል። በፖለቲካ አንጻር ግን አሕዛብ በሆነው በፋርስ መንግሥት ቁጥጥር ሥር ነበሩ። በይሁዳ ሕዝብ የቀድሞ የፖለቲካ አመራር ታላቅነት ላይ ከማተኮር ይልቅ፥ የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ጸሐፊ የፖለቲካ ታላቅነት የመንፈሳዊ ታላቅነትን ያህል አስፈላጊ እንዳልሆነ ሊያስገነዝባቸው ፈለገ። ዳዊትና ሰሎሞን ሌሉችም የቀድሞ ነገሥታት ዕቅዳቸው በከፍተኛ ደረጃ ሊከናወንላቸው የቻለው፥ በነበራቸው የግል ኃይልና ሥልጣን ሳይሆን ለእግዚአብሔርና ለሕጉ በነበራቸው ታዛዥነት ምክንያት ነበር። ስለዚህ ጸሐፊው የፖለቲካ ታላቅነት ከመንፈሳዊ ታላቅነት ቀጥሎ የሚመጣ ነገር መሆኑን ሊያሳያቸው ፈልጎ ነበር። ይሁዳ በፖለቲካ ወደ ታላቅነት ልትመጣ የምትችለው፥ በመንፈሳዊ ነገር ታላቅ ከሆነች በኋላ ብቻ ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፥ ይህ እውነት ዛሬም በዚህ ዘመን በመንፈሳዊ ነገር ታላቅ ሳይሆኑ፥ በቁጥር ሊበዙና በልማት ተግባር የታወቁ ለመሆን ለሚፈልጉ አብያተ ክርስቲያናት ጠቃሚ የሚሆነው እንዴት ነው? 

ከ500-300 ዓ.ዓ. የይሁዳ መንግሥት፥ በተለይ በስተሰሜን በኩል በሰማርያ የሐሰት ትምህርት መስፋፋት አጋጥሞት ነበር። በቀድሞው ሰሜናዊ እስራኤል ከነበሩ አይሁድና አሕዛብ የመጡ እነዚህ ድብልቅ ሳምራውያን፥ የራሳቸውን የተበላሸ አምልኮ ከመጀመራቸው እንዲያውም የረከሰ ቤተ መቅደስ በመሥራት አሁራ ማዝዳ የሚባለውን አምላካቸውን ማምለክ ጀምረው ነበር፤ ከዚያም በኋላ የግሪክ ሃይማኖት የመስፋፋት አደጋም ነበር። ስለዚህ የዜና መዋዕል ጸሐፊ፥ ለእግዚአብሔር ያላቸውን አምልኮ በንጽሕና የመጠበቅ አስፈላጊነትን ለአይሁድ ያስታውሳቸዋል። ጊዚያዊ የሆኑ ተሐድሶዎች በዕዝራና በነህምያ አልፎ አልፎ ሲደረጉም ለረጅም ጊዜ ግን አልቆዩም። ሕዝቡ ወዲያውኑ ወደ ጣዖት አምልኮ ይመለሰ ነበር፡፡

የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) የእግዚአብሔር ሕዝብ ዓለምን መምሰል እንደሌለባቸውና የሐሰት ትምህርት ገብቶ እውነተኛ እምነታቸውን እንዲያጠፋ መፍቀድ እንደሌለባቸው ማስታወስ የሚያስፈልገው ለምንድን ነው? ለ) የሐሰት ትምህርትን ቤተ ከርስቲያንህን እንዴት እንደ ጎዳት ምሳሌ ስጥ። ሐ) የቤተ ክርስቲያንህ መሪዎች ሐሰተኛ ትምህርት ለመዋጋት ምን ያደርጋሉ? መ) የሐሰት ትምህርትን በተሻለ ሁኔታ ለመዋጋት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ምን ማድረግ ይችላሉ? ሠ) የሐሰት ትምህርትን ለመዋጋት፥ ታሪክን በተሻለ ሁኔታ መረዳት ለምን ይጠቅማል?

አይሁድ ሌላ ንጉሥ በእነርሱ ላይ እንደሚነግሥ ተስፋ ቢያደርጉም ከዳዊት ዘር የሆን ንጉሥ ከዚያ በኋላ አልተነሳም። ከረጅም ጊዜ ጀምሮ ተስፋ የተሰጣቸውን መሢሕ ሲጠብቁ ቢቆዩም ነጻ ሊያደርጋቸው ገና ወደ እነርሱ አልመጣም ነበር።

የመጽሐፈ ዜና መዋዕል ጸሐፊ ሌላ ታሪክ እንዲጽፍ ያስፈለገበት ምክንያት ይህ ነበር። ሕዝቡን ሊያስታውስ የፈለገው አንድ ቀን እስራኤል ተመልሶ እንደሚቋቋም ነበር። እንደ ዳዊት ያለ እጅግ መልካም መሪ አንድ ቀን ሕዝቡን እንደገና ይመራል። በእርሱም መሪነት እውነተኛ ሃይማኖታዊ ተሐድሶ ይኖርና ሕዝቡ እግዚአብሔርን ይወዳሉ፤ ይታዘዙታልም። ይህ ሰው እስኪደርስ ድረስ ሕዝቡ ለእግዚአብሐር ታማኞች እንዲሆኑና በኃጢአታቸው ምክንያት የእግዚአብሔርን ፍርድ እንዳይቀምሱ ያስጠነቅቃቸዋል፤ ያበረታታቸዋልም።

መጽሐፈ ዜና መዋዕልን ከሌሎች መጻሕፍት ጋር ስናወዳድረው፥ ጸሐፊው በውስጡ ያቀረባቸውን ነገሮች በመምረጥና በማደራጀት ከሌሎቹ የተለየ ነው። በተጨማሪም በአንዳንዶቹ የዜና መዋዕል ታሪኮች ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ ታሪኮችና ቁጥሮች በሌሉች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ከሚገኙት የተለዩ ናቸው። የእነዚህ ልዩነቶች ምክንያቶች ምን እንደሆኑ ሙሉ በሙሉ ባናውቅም የሚከተሉት ነገሮች ለልዩነቶቹ መከሰት ምክንያት ከሆኑት አንዳንዶቹ ናቸው፡-

  1. በመጽሐፈ ሳሙኤልና ነገሥት ውስጥ ምን እንደተጻፈ ይህ ጸሐፊ ያውቅ ስለነበር በድጋሚ ሊጽፈው አልፈለገም፤ ነገር ግን ዜና መዋዕልን ለመጻፍ የተነሣበትን የሥነ-መለኮት ዓላማ ለመደገፍ የሚያስችሉትን ነገሮች ብቻ መረጠ። 

የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ክፍሎች አወዳድር። በዜና መዋዕልና በሌሎቹ ክፍሎች መካከል ያለውን የቁጥር ልዩነት ዘርዝር (2ኛ ሳሙ. 23፡8 እና 1ኛ ዜና 11፡11፤ 2ኛ ሳሙ. 24፡9 እና 1ኛ ዜና 21፡5)። 

  1. በመጽሐፈ ዜና መዋዕል፥ ሳሙኤልና ነገሥት መካከል ባሉ ተመሳሳይ ታሪኮች አንዳንድ የቁጥር ልዩነቶች አሉ። በተመሳሳይ ታሪክ ውስጥ ካሉ 213 ቁጥሮች፥ 19ኙ ልዩነት አላቸው። ይህንን አንዳንዶቹ ጸሐፊዎች በሚገለብጡበት ጊዜ የሠሩት ስሕተት ነው ለማለት እንችላለን። ሌሎቹ ደግሞ ቀጥተኛ ቁጥሮች ሳይሆኑ ግምታዊ ወይም የተጠጋጉ ናቸው።

ለእነዚህ ልዩነቶች ምክንያቶቹ ምን እንደሆኑ ሙሉ ለሙሉ ባናውቅም፥ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ስለ መሆኑና ስሕተትም እንደሌለበት ያለንን መረዳት አይለውጠውም። ቀደም ሲል እንደተማርነውና ክርስቲያኖችም እንደመሆናችን መጽሐፍ ቅዱስ በመጀመሪያ ጽሑፎቹ ምንም ስሕተት እንደሌለበት ቢገኝበትም እንኳ በቅጂዎች ምክንያት ስሕተት እንደሚፈጥር እናምናለን። ለዚህ ልዩነት አሁን ግልጽ የሆነ ምክንያት ባይኖረንም፥ መጽሐፍ ቅዱስ ሐቀኛና አንዳች ስሕተት የሌለበት ለመሆኑ እርግጠኞች መሆን እንችላለን። አንድ ቀን ያ ልዩነት ከምን እንደመጣ እንገነዘባለን።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading