የሕይወት እንጀራ

ኦሪት ዘፍጥረት

ዘፍጥረት 37-50 የዮሴፍ ታሪክ

የዚህ የኦሪት ዘፍጥረት የመጨረሻ ክፍል ዓላማ የእስራኤል ሕዝብ የከነዓንን ምድር ይወርሱ ዘንድ ቃል የተገባላቸው ሆነው ሳሉ፥ እንዴት ወደ ግብፅ እንደወረዱ ማሳየት ነው። ለኦሪት ዘጸአትም በመግቢያነት የሚያገለግል ነው። ምክንያቱም ኦሪት ዘጸአት እስራኤላውያን በግብፅ 400 ዓመታት ከቆዩ በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመመለስ እንዴት እንደወጡ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው። ታሪኩ የተፈጸመው በሙሴ ዘመን ገደማ ስለሆነ፥ ከሌሎቹ የእስራኤል አባቶች ታሪክ ይልቅ የዮሴፍን ታሪክ በዝርዝር ይነግረናል። በተጨማሪ ኃጢአታቸው የሚያስከትለውን ችግር ጨምሮ እግዚአብሔር በሕዝቡ ሕይወት የሚመጣውን ነገር ሁሉ እየተቆጣጠረ እንዴት ያለማቋረጥ እንደመራቸው እንመለከታለን። የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍጥ. 37-50 አንብብ። ሀ) ዮሴፍ ያያቸውንና የተረጎማቸውን ልዩ ልዩ ሕልሞች ዘርዝር። እያንዳንዳቸው እንዴት ተፈጸሙ? ለ) ዮሴፍ በምሳሌነት ሊቀርብ የሚችል ታላቅ የእግዚአብሔር ሰው የሆነው እንዴት ነው? ሐ) በዮሴፍ ሕይወት ውስጥ የእግዚአብሔር ቁጥጥር የታየባቸውን መንገዶች ዘርዝር። መ) በስደት ውስጥ ይቅርታንና ትዕግሥትን ስለማሳየት ከዮሴፍ ሕይወት የምንማረው ነገር ምንድን ነው?  ከብዙ ዓመታት በፊት፥ እግዚአብሔር በሌላ ምድር መጻተኞች ሆነው እንደሚኖሩና ለ400 ዓመታት በባርነት እንደሚገዙ ለአብርሃም ተናግሮት ነበር (ዘፍጥ. 15፡13)። በዮሴፍ ታሪክ ይህ ትንቢት መፈጸም ጀመረ። እግዚአብሔር የገባውን ቃል ኪዳንና የሰጠውን ተስፋ እኛ በምንፈልገው ፍጥነት ባይፈጽምም፥ ለሰጠው ተስፋና ቃል ኪዳን ግን ሁልጊዜ ታማኝ ነው። ዮሴፍ ወደ ግብፅ የሄደበት ምክንያት (ዘፍጥ. 37):- ከዘፍጥረት ምዕራፍ 37 ጀምሮ የእግዚአብሔርን እጅ በሥራ ላይ እናያለን። እግዚአብሔር አንድ ዓይነት ትርጉም ያላቸውን ሁለት ሕልሞች ለዮሴፍ ሰጠው። በመጀመሪያ፥ የወንድሞቹ ነዶዎች ለእርሱ ሲሰግዱ ያያል። በሁለተኛው ሕልም ደግሞ ፀሐይ፥ ጨረቃና አሥራ አንዱ ከዋክብት ለእርሱ ሲሰግዱለት አየ። ይህ ሕልም በወንድሞቹ ላይ ገዥ እንደሚሆንና እነርሱም እንደሚሰግዱለት ማለትም እንደ መሪያቸው ተቆጥሮ እንደሚያከብሩት የተሰጠ ትንቢት ነበር። ይህም ትንቢት ከብዙ ዓመታት በኋላ ዮሴፍ የግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ ወንድሞቹ ምግብ ፍለጋ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ተፈጸመ። ትዕማር የይሁዳን ዘር አዳነች (ዘፍጥ. 38)፡- በዮሴፍ ታሪክ አጋማሽ ላይ በሌሉች ወንድሞቹ በተለይም በይሁዳ ሕይወት ኃጢአትና ክፋት መኖሩን የሚያሳይ አሳዛኝ ታሪክ እንመለከታለን። የይሁዳ ትልቁ ልጅ ዔር ትዕማር የምትባል ከነዓናዊት አገባ፤ ነገር ግን አንድም ልጅ ሳይወልድ ሞተ። በዚያ ዘመን በነበረው ወግ መሠረት ይሁዳ የሚቀጥለውን ልጁን አውናንን ከትዕማር ጋር ማጋባት ነበረበት። በባሕሉ መሠረት የሚወለደው የመጀመሪያ ልጅ የሟቹ ወንድም የዔር እንደሆነ ይቆጠር ነበር። የቀሩት ልጆች ደግሞ የአውናን ይሆኑ ነበር። የመጀመሪያው ልጅም የብኩርናን መብት ያገኝ ነበር። በሞተውም ልጅ ምትክ ከአያቱ ርስት ይወርስ ነበር። ይህ ማለት ይሁዳ ለበኩር ልጁ ያወርሰው የነበረው ነገር የመጀመሪያ ልጁ ከሞተ በኋላ የሚተላለፈው ለሁለተኛ ልጁ ሳይሆን ከትዕማር ለተወለደው ለልጅ ልጁ ይሆናል ማለት ነው። አውናን በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ስላደረገ እግዚአብሔር ቀሠፈው። ባሕሉን ለማክበርና ለወንድሙ ልጅ ለማሳደግ ያልፈለገ ይመስላል። ምናልባት ምንም ልጅ ሳይወልዱ በሞተው ወንድሙ ምትክ የብኩርናን መብት እንደሚወርስ ሳይገምት አልቀረም። አውናን ከሞተ በኋላ ይሁዳ በባሕሉ መሠረት ሦስተኛ ልጁን ለትዕማር ለመዳር ፈቃደኛ ሳይሆን ቀረ። ግዴታውን ለእርሷና ለመጀመሪያ ልጁ ሳይፈጽም ቀረ፤ ስለዚህ እርሷና ልጆችዋ የብኩርና መብት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ይሁዳን አታለለችው። ራሷን ሴተኛ አዳሪ አስመስላ በማቅረብ አማችዋ የሆነው ይሁዳ ከእርሱ ጋር እንዲተኛ አደረገችው። ከእርሱም ፋሬስና ዛራ ብላ የጠራቻቸውን መንታ ልጆች ወለደች። ይህን በማድረግዋ የይሁዳን ዘር ከመጥፋት አዳነች። የብኩርናን መብትም በቤተሰቧ በማስቀረት ልጇ ለይሁዳ የተሰጠውን የተስፋ ቃል ወራሽ እንዲሆን አደረገች። የሚያስደንቀው ነገር ንጉሡ ዳዊትና የዳዊት ልጅ ተብሎ የሚጠራው የኢየሱስ ክርስቶስ ዘር የመጣው ከትዕማር ልጅ ከፋሬስ መሆኑ ነው(ማቴ. 1፡3)። እግዚአብሔር ዮሴፍን በግብፅ ጠብቆ አከበረው (ዘፍጥ. 38-40)። ሀ. እግዚአብሔር ዮሴፍን በጲጥፋራ ቤት አከበረው፡- ዮሴፍ በዚህ ሰው ቤት ባሪያ ቢሆንም፥ ከእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝቦች አንዱ ነበር። እስራኤላውያንን ከራብ በማዳን የተሰጣቸው ቃል ኪዳን ከፍጻሜ እንዲደርስ ለማድረግ በእግዚአብሔር የተመረጠው ሰው ዮሴፍ ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር ዮሴፍን አከበረውና በግብፅ ውስጥ ባለውና መሪ በነበረው በጲጥፋራ ቤት አገልጋዮች ሁሉ አለቃ እንዲሆን አደረገ። ከጲጥፋራ ሚስት ጋር ዝሙት ፈጽሞ ሕይወቱ ሁሉ እንዲበላሽና እንዲጠፋ ለማድረግ ሰይጣን ሞከረ። ዮሴፍ ግን በዚህ መንገድ እግዚአብሔርንና ጲጥፋራን ላለመሳደብ ወስኖ የሰይጣንን ሙከራ ተቃወመ። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ለዮሴፍ ከጲጥፋራ ሚስት ጋር ዝሙት መፈጸም በጣም ቀላል የነበረው ለምንድን ነው? ለ) በዚህ ዘመን ብዙ ክርስቲያኖች በዚህ ኃጢአት የሚወድቁት ለምንድን ነው? ሐ) ይህንን ፈተና ስለማሸነፍ ከዮሴፍ ሕይወት የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ለ) እግዚአብሔር ዮሴፍን በወኅኒ ቤት አከበረው፡- ምንም ጥፋት ያልነበረበት ንጹሕ የነበረው ዮሴፍ ወደ ወኅኒ ቤት ከገባ በኋላ በዚያ ለብዙ ዓመታት ቆየ። እግዚአብሔር በዚያም ቢሆን ሞገስን ሰጠውና በወኅኒ ቤቱ የእስረኞች አለቃ አደረገው። የወኅኒ ቤቱ የእስረኞች አለቃ ስለነበር እዚያ ታስረው ከነበሩት ከፈርዖን ጠጅ አሳላፊና የእንጀራ አበዛ ጋር ለመገናኘት ቻለ። እነዚህ ሁለት ሰዎች በግብፅ ቤተ መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች ነበሩ። ጠጅ አሳላፊው ንጉሡ ወይን ጠጅ ከመጠጣቱ በፊት የሚቀምስለት ሰው ነበር። ይህም ንጉሡን ማንም ሰው በመርዝ ሊገድለው እንዳይችል የተደረገ ዘዴ ነበር። ብዙውን ጊዜ የጠጅ አሳላፊው የንጉሡ ምሥጢረኛና የቅርብ ጓደኛ ነበር። የእንጀራ አበዛውም ንጉሡ ለሚበላቸው ነገሮች ሁሉ ኃላፊነት ስለ ነበረበት በጣም ከፍተኛ ስፍራ የነበረው ሰው ነው። እነዚህ ሁለት ሰዎች በእስር ቤት በነበሩ ጊዜ ዮሴፍ ሊተረጉምላቸው የቻለውን ሁለት ሕልሞች አዩ። የጠጅ አሳላፊው ሕልም ትርጓሜ ንጉሡን ያገለግልበት ወደነበረው ወደ ቀድሞ ሥፍራው መመለሱ ነበር። የእንጀራ አበዛው ሕልም ትርጓሜ ደግሞ የንጉሡን ምሥጢር ስላባከነ በስቅላት እንደሚገደል ነበር። እነዚህ ሕልሞች በኋላ የፈርዖንን ሕልም ለመተርጎም ወደ ቤተ መንግሥት እንዲጠራ ያደረጉት ስለነበሩ በጣም ጠቃሚ ሕልሞች ነበሩ። እግዚአብሔር ዮሴፍን በፈርዖን ፊት አከበረውና ጠቅላይ ሚኒስትር አደረገው (ዘፍጥ. 40-45)። ዮስፍ የፈርዖንን ሕልም ከተረጐመ በኋላ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ እንደደረሰ ይታወቃል። እግዚአብሔር በዮሴፍ በኩል ለፈርዖን ሰባት የጥጋብና ሰባት የረሃብ ዓመታት እንደሚመጡ በሕልሙ አሳወቀው። ዮሴፍ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደመሆኑ መጠን ለረሀቡ ጊዜ የሚሆነውን እህል በጥጋቡ ጊዜ አዘጋጀ። እግዚአብሔር ዮሴፍን ያን ወደ መሰለ ከፍተኛ የሥልጣን ቦታ ያመጣው ለምንድን ነው? ሀ) የግብፅን ሕዝብ ከራብ ለማዳን፥ ለ) የተመረጠውን የእስራኤልን ሕዝብ ከራብ ለማዳንና፥ ሐ) ለአብርሃም የገባውን የተስፋ ቃል ለመፈጸም ይችል ዘንድ የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ግብፅ ለማምጣት ነው።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ዕቅዱን ለመፈጸም ሲል ዮሴፍን በዚህ ዓይነት ካከበረው፥ ዛሬም ለእኛ እንዴት እንደሚሠራ ይህ ምን ያስተምረናል? ለ) እግዚአብሔር በዮሴፍ ሕይወት እንዳደረገው በአንተ ወይም በሌላው ክርስቲያን ሕይወት ያደረገውን ተመሳሳይ ነገር የሚገልጹ ምሳሌዎችን ዘርዝር። ዮሴፍ ለባርነት የሸጡትን ወንድሞቹን ለመፈተን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንዲያልፉ አደረጋቸው። እርሱን ለባርነት ስለሸጡበት ኃጢአት በእርግጥ መፀፀታቸውን ማየት ፈለገ። ይሁዳ ራሱን በብንያም ምትክ ለመስጠት የተዘጋጀ መሆኑንና ወንድሞቹም እንደዚያ የተቀጡበት ምክንያት እግዚአብሔር ራሱ ስለቀጣቸው እንደሆነ መቀበላቸውን ሲያይ ከኃጢአታቸው በእርግጥ መመለሳቸውን አወቀ። ከዚያ በኋላ ራሱን ገለጠላቸው። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዮሴፍ ወንድሞቹ እንደተለወጡና በእርግጥ ከኃጢአታቸው እንደተመለሱ ማወቅ ለምን አስፈለገው? ለ) ክርስቲያኖች በእውነት ከኃጢአታቸው መመለሳቸውን በምን እናውቃለን? የያዕቆብ ትውልድና ትንሹ የእስራኤል ጎሳ ወደ ግብፅ መውረድ (ዘፍጥ. 46-50)። ዮሴፍ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሆነ በኋላ ቤተሰቡ ወደ ግብፅ መጥተው እንዲኖሩ አደረገ። የእስራኤል ሕዝብ አባት የሆነው ያዕቆብም ወደ ግብፅ ወረደ። የዮሴፍን ልጆች ጨምሮ ወደ ግብፅ የመጡት እስራኤላውያን ጠቅላላ ቁጥር 70 ነበር። ከ400 ዓመታት በኋላ 70 የነበረው የእስራኤላውያን ቁጥር 2 ሚሊዮን ደርሶ ነበር። ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ለልጆቹ ለእያንዳንዳቸው በረከቱን አስተላለፈ። እነዚህ በረከቶች የትንቢት መልክ ሲኖራቸው የተሰጡትም በቀጥታ ከእግዚአብሔር እንደመጡ ተደርገው ነበር። የያዕቆብ በረከቶችና ትንቢት የእግዚአብሔር ቃል ነበሩ፤ እግዚአብሔርም ፈጸማቸው። ሀ) ያዕቆብ የዮሴፍን ሁለት ልጆች ኤፍሬምና ምናሴን ባረካቸው (ዘፍጥ. 48)። ይህንን በማድረግ ያዕቆብ የበኩር ልጅን መብት ለዮሴፍና ለልጆቹ ሰጠ። ደግሞም የብኩርናን መብት ከዮሴፍ ልጆች ለታናሹ ለኤፍሬም ሰጠ።

ዘፍጥረት 37-50 የዮሴፍ ታሪክ Read More »

ዘፍጥረት 25-36 የይስሐቅና የያዕቆብ ታሪክ

እስካሁን ድረስ በኦሪት ዘፍጥረት ጥናታችን ውስጥ ሁለት ዋና ዋና ክፍሎች እንዳሉ ተመልክተናል። በመጀመሪያ፥ ከአይሁድ ሕዝብ አጀማመር በፊት ያሉትን ጊዜያት በአጭሩ የሚያካትተውን – ከዘፍጥ. 1-11 ያለውን ክፍል፥ በሁለተኛ፥ ደረጃ ደግሞ የአይሁድ ሕዝብ ራስ የሆነውን የአብርሃምን ታሪክ የሚያሳየውን – ከዘፍጥ. 12-24 ተመልክተናል። በተጨማሪ ለአብርሃም በተአምራት የተወለደለትን ይስሐቅ የተባለውን ልጁን ታሪክ መመልከት ጀምረናል። ዛሬ ደግሞ የአብርሃም ልጅና የልጅ ልጅ ስለሆኑት ስላ ይስሐቅና ስለ ያዕቆብ መመልከት እንጀምራለን።  የውይይት ጥያቄ፥ ከዘፍጥረት 25-36 ያለውን ክፍል አንብብ። ሀ) ከእነዚህ ምዕራፎች ስለ ይስሐቅ የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ለ) ከእነዚህ ምዕራፎች ስለ ያዕቆብ የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ሐ) በእነዚህ ምዕራፎች ውስጥ ቃል ኪዳኑን አደጋ ላይ ጥለውት የነበሩት ነገሮች ምንድን ናቸው? መ) በእነዚህ ምዕራፎች እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ያስተላለፈውና የጠበቃቸው እንዴት ነው? ሠ) የዚህ ክፍል ዋና ዋና ትምህርቶችን ዘርዝር። ረ) ከእነዚህ ምዕራፎች ስለ እግዚአብሔር የምንማራቸውን አንዳንድ ነገሮች ጥቀስ። ሰ) ከእነዚህ ምዕራፎች በእምነት ስለ መራመድ የምንማራቸው ነገሮች ምንድን ናቸው? ኦሪት ዘፍጥረት የአብርሃም ልጅ ስለሆነው ስለ ይስሐቅ ብዙ ነገሮችን አይነግረንም። እጅግ በጣም ታዛዥ ልጅ እንደነበረ የምናውቀው አብርሃም ሊሠዋው በነበረ ጊዜ በፈቃደኝነት በአባቱ ላይ በመታመን ሲታዘዝ በማየታችን ነው። የይስሐቅ ታሪክ ለያዕቆብ ታሪክ እንደመግቢያ ሆኖ የሚያገለግለን ነው። ያዕቆብ የ12ቱ የእስራኤል ነገዶች አባት በመሆኑ፥ ለአይሁድ ሕዝብ በጣም አስፈላጊ ሰው ነበር። ሙሴ፥ የአብርሃምን ታሪክ በመንገር የእስራኤልን ሕዝብ እንዴት እንደነበር ካሳየን በኋላ አሁን ደግሞ 12ቱ የእስራኤል ነገዶች እንዴት እንደተመሠረቱ ሊጠቁመን ይጀምራል። የፔንታቱክ ታሪክ እምብርት እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር በራሱ አነሣሽነት የመሠረተው ቃል ኪዳን መሆኑን አስታውስ። ይስሐቅ ከዘፍጥረት 25-36 ድረስ ቃል ኪዳኑ አደጋ ላይ ወድቆ የነበረባቸውን የሚከተሉትን ሁኔታዎች ተመልከት፡ ሌሎቹ የአብርሃም ልጆች ለይስሐቅ መተላለፍ የነበረበትን ቃል ኪዳን አደጋ ላይ ጥለውት ነበር። ቃል ኪዳኑ መተላለፍ ያለበት በተአምራት ለተወለደው በተስፋው ልጅ፥ ለይስሐቅ እንጂ ለሌሎቹ አልነበረም (ዘፍጥ. 25፡1-18)። አብርሃም ሌሎች ልጆችም ነበሩት። የአብርሃምና የአጋር የመጀመሪያ ልጅ እስማኤል ነበር። ለይስሐቅ የተሰጡት የቃል ኪዳን ተስፋዎች ችግር እንዳይገጥማቸው አብርሃም እስማኤልን አስቀድሞ ከቤቱ አስወጥቶት ነበር (ዘፍጥ. 21፡8-21)። ሁለተኛ፥ ከሣራ ሞት በኋላ አብርሃም ካገባት ኬጡራ ከምትባል ሴት የወለዳቸው 6 ወንዶች ልጆች ነበሩት። አብርሃም፥ ከመሞቱ በፊት ስጦታ በመስጠት እነዚህን ስድስት ልጆቹን አሰናበታቸው። ይህም በርስት ጉዳይ ከይስሐቅ ጋር እንዳይጣሉ ታስቦ የተደረገ ነው።  የይስሐቅ ልጅን ያለ መውለድ አደጋ፡- ይስሐቅ ቃል ኪዳኑን የሚያስተላልፍለትና ርስቱን የሚወርሰው ልጅ እንደማይኖረው ያስመሰሉ ሁለት ምክንያቶች ነበሩ። በመጀመሪያ፥ እንደ ሣራ ሁሉ ርብቃም መካን ነበረች፤ ነገር ግን በኋላ እግዚአብሔር ዔሳውና ያዕቆብ የተባሉ ሁለት ልጆችን ሰጣት። ሆኖም እነዚህ ልጆች በሚወለዱበት ጊዜ እንኳ ሲጣሉ የነበሩና በሕይወታቸው ዘመንም ሁሉ እየተጣሉ የሚኖሩ ሆኑ። ከመወለዳቸው አስቀድሞ እግዚአብሔር የቃል ኪዳኑን መስመር የሚቀጥለው ሰው ታናሹ (ያዕቆብ) እንጂ ታላቁ (ዔሳው) አይሆንም በማለት ተንብዮ ነበር። እግዚአብሔር አሁንም ዓላማውን ከግቡ ለማድረስ ከሕዝቡ ባሕልና ከወላጆቻቸው ፍላጎት ተቃራኒ በሆነ መንገድ ተጓዘ (ዘፍጥ. 25፡ 19-23)። ሁለተኛው አደጋ ደግሞ ርብቃ የሌላ ሰው ሚስት ልትሆን ነበር (ዘፍጥ. 26)። የዘፍጥረት 26 ታሪክ ከዘፍጥ. 25፡19-21 በፊት የተፈጸመ ሳይሆን አይቀርም። አብርሃምና ይስሐቅ ተመሳሳይ ድክመት ነበራቸው። ይስሐቅም በባዕድ አገር በተገኘ ጊዜ እግዚአብሔር ሕይወቱን ሊጠብቅለት እንደሚችል ማመንና በእግዚአብሔር መደገፍ አቃተው። ይስሐቅ በፍልስጥኤማውያን ምድር ለመኖር ሄደ። ልክ እንደ አብርሃም የሚስቱን ማንነት ላለመናገር ዋሸ። ሣራ፥ ታራ ከሌላ ሴት የወለዳት የአብርሃም ግማሽ እኅቱ ስለነበረች፥ እኅቴ ናት ብሎ በከፊል ዋሽቶ ነበር። ይስሐቅ ግን ርብቃ የአጎቱ የልጅ ልጅ ስለነበረች እኅቴ ናት ብሎ ሲናገር ሙሉ በሙሉ ዋሸ። ርብቃ የሌላ ሰው ሚስት ትሆን ዘንድ ተወስዳ ቢሆን ኖሮ ይስሐቅ ቃል ኪዳኑን ሊያስተላልፍለት የሚችል አንዳችም ልጅ አይኖረውም ነበር። እግዚአብሔር ግን በዚህ ድርጊት መካከል ጣልቃ ገባና ርብቃን የሌላ ሰው ሚስት ከመሆን አዳናት። የውይይት ጥያቄ፥ ስሕተት ብንሠራም እንኳ እግዚአብሔር እንደሚረዳንና የተስፋ ቃሉንም እንደሚጠብቅልን መገንዘባችን በዚህ ዘመን ላለን ለእኛ ምን ያህል ማበረታቻ ይሆነናል? ዘፍጥ. 26 እጅግ ጠቃሚ ክፍል የሆነበት ሌላ ምክንያት አለ። በዘፍጥ. 26 ሁለት ስፍራዎች ላይ እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠውን የተስፋ ቃል በማረጋገጥ፥ እነዚያው ተመሳሳይ ተስፋዎች ለይስሐቅ እንደተላለፉለት ያሳየዋል (ዘፍጥ. 26፡3-5፥ 23-24)።  የተስፋው ወራሽ የሆነው ያዕቆብ በዔሳው የመገደል አደጋ (ዘፍጥ.25፡19-34፥27፡1-4)፡- ያዕቆብና ዔሳው በሚወለዱበት ጊዜ ባሕርያቸው ተወስኖ ነበር። ያዕቆብና ዔሳው ሲወለዱ እንኳ እየተጋፉ ነበር የተወለዱት። ያዕቆብ የኖረው ልክ እንደስሙ ትርጉም ነው። ያዕቆብ ማለት «አታላይ» ወይም «አደናቃፊ» ማለት ነው። ያዕቆብ በሚወለድበት ጊዜ እንኳ የወንድሙን ተረከዝ ይዞ በመውጣት ሊያደናቅፈው ሞክሮ ነበር። በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ለወጣለት ስም በመኖር ዔሳውን ኋላም ላባን ሲያታልልና ሲያደናቅፍ ኖሯል። በጊዜው በነበረው ባሕል መሠረት ታላቁ ልጅ ዔሳው የይስሐቅ ወራሽ መሆን ነበረበት። በእግዚአብሔር ዓላማ መሠረት ግን ያዕቆብ ወራሽ ሆኗል። ያዕቆብ ወራሽ መሆኑን ያውቅ እንደ ነበር አንዳችም ጥርጥር የለም፤ ነገር ግን ያዕቆብ እግዚአብሔር ይህንን በረከት እስኪሰጠው ድረስ እንደመታገሥ የዔሳውን ብኩርናን ለመስረቅ ዓቀደ። በመጀመሪያ፥ ያዕቆብ የዔሳውን ራብ ተጠቅሞ በጥቂት ምግብ ብኩርናውን ማለትም የይስሐቅ ወራሽ የመሆን መብት ገዛ። ሁለተኛ፥ ዔሳውን መስሉ አባቱን በመቅረብ ለወንድሙ የሚገባውን በረከት በመረከብ የማታለል ተግባር ፈጸመ፤ (ዘፍጥ. 27)። በረከቱ እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባለትን ቃል ኪዳን ሁሉ የመውረስ መብትን ይጨምራል። በረከቱን ለያዕቆብ መስጠት የእግዚአብሔር ዕቅድ መሆኑን ይስሐቅና ርብቃ ቢያውቁም፥ እርሱን ከመታዘዝና ከመደገፍ ይልቅ ይስሐቅ የብኩርና መብትን ለሚወደው ልጁ ለዔሳው ለመስጠት ሞከረ። ርብቃ ደግሞ ባሏ የሚታለልበትን መንገድ በማዘጋጀት የብኩርናውን መብት እርሷ ለምትወደው ልጇ- ለያዕቆብ ለማድረግ ፈለገች። እግዚአብሔር ግን ሁኔታዎቹን ሁሉ በመቆጣጠር የራሱ ዕቅድ እንደተፈጸመ አየ። በረከቱና የቃል ኪዳኑ በረከቶች በሙሉ ለያዕቆብ ተላለፉ። የውይይት ጥያቄ፥ የወላጆች አንድ ልጃቸውን ከሌላው አስበልጠው መውደድ በቤተሰብ ውስጥ ሊፈጥር ስለሚችለው አደጋ ይህ ታሪክ ምን ያስተምረናል? ዔሳው መታለሉን በተገነዘበ ጊዜ፥ ያዕቆብን ለመግደል ወሰነ። ይህም ነገር ያዕቆብ ከከነዓን ወደ ካራን እንዲሸሽ አደረገው። ከ20 ዓመት በኋላ ያዕቆብ ወደ ከነዓን ሲመለስ፥ ዔሳው እርሱን የመግደል አሳቡን ለመፈጸም ጥሩ አጋጣሚ ሆነለት። እግዚአብሔር ግን የዔሳውን ልብ ለወጠና ያዕቆብን እንደ ወንድም ተቀበለው፤ (ዘፍጥ. 33)።  ያዕቆብ በካራን ምድር በነበረበት ጊዜ የገጠመው አደጋ፡- የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን እንዳይፈጸም ዕንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉ ሁለት ዋና ዋና አደጋዎች ያዕቆብን በካራን ምድር ገጥመውት ነበር። የመጀመሪያው፥ ያዕቆብ ወደ ተስፋይቱ ምድር ወደ- ከነዓን እንዳይመለስ የከለከለው አደጋ ነበር፤ (ዘፍጥ. 28-30)። በካራን ምድር ባለጸጋ ሆነ። ያዕቆብ ከከነዓን ወደ ካራን በሚጓዝበት ጊዜ እግዚአብሔር በቤቴል ተገናኘው። በሕልሙም እግዚአብሔር ሁለት ነገሮችን አሳውቆት ነበር፡-  i) እግዚአብሔር በረከቱን የሚፈጽምለት በተስፋይቱ ምድር እንደሚሆን አስታወሰው። 2) የቃል ኪዳኑን በረከት አስቀድሞ ለአብርሃምና ለይስሐቅ እንደሰጠ አሁን ለያዕቆብ አስተላለፈለት፤ (ዘፍጥ. 28፡12-15)። በባዕድ አገር በሚኖርበት ጊዜም ከእርሱ ጋር እንደሚሆን በመንገር አበረታታው። ያዕቆብ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዳይመለስ ሊያደርገው የሚችለው አደጋ ካራን በደረሰ ጊዜ እየጨመረ መጣ። በመጀመሪያ ለሁለቱ ሚስቶቹ – ለልያና ለራሔል ሲል 14 ዓመታት ተገዛ። ሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ለአማቹ ለላባ ቁሳቁሳዊ የሆነ ሀብትና ንብረት ለማስገኘት ብሎ ተጨማሪ 6 ዓመታት ተገዛ። እግዚአብሔር ግን አታላዩን ያዕቆብን መለወጥ የጀመረው በካራን ምድር ነበር። ያዕቆብ ከእርሱ የባሰ አታላይ የሆነ አጎት አጋጠመው፥ እርሱም ላባ ነበር። እግዚአብሔር ሌላውን ሰው ለማጭበርበርና ቁሳቁሳዊ በረከት ለማግኘት የራስን ጥበብና የማታለል ዘዴ መጠቀም ከንቱ ጥረት መሆኑን ለያዕቆብ ለማሳየት ሲል ላባን ተጠቀመበት። ከ12ቱ የያዕቆብ ልጆች 11ዱ የተወለዱት በካራን ነበር። ብንያም ግን የተወለደው ቆይቶ በከነዓን ምድር ነበር። ሀ. የልያ ልጆች፡- ሮቤል፥ ስምዖን፥ ሌዊ፥ ይሁዳ፥ ይሳኮር፥ ዛብሉን  ለ. የራሔል አገልጋይ የሆነችው የባላ ልጆች፡- ዳን፥ ንፍታሌም  ሐ. የልያ አገልጋይ የሆነችው የዘለፋ ልጆች፡- ጋድ፥ አሴር  መ.

ዘፍጥረት 25-36 የይስሐቅና የያዕቆብ ታሪክ Read More »

የአብርሃም ታሪክ (ዘፍጥረት 12-24)

ዛሬ የኦሪት ዘፍጥረትን ሁለተኛ ዋና ክፍል ማጥናት እንጀምራለን። ዘፍጥረት በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች እንደሚመደብ መመልከታችንን ታስታውሳለህ። ዘፍ. 1-11 የሚያተኩረው ከእስራኤል አባቶች በፊት በነበረው ዘመን ላይ ሲሆን፥ ዘፍ. 12-50 ደግሞ አራቱን የእስራኤል ዋና ዋና አባቶች ታሪክ ያሳየናል። እነርሱም፡- አብርሃም፥ ይስሐቅ፥ ያዕቆብና ዮሴፍ ናቸው። በዛሬው ትምህርታችን የአይሁድ ሕዝብና በእግዚአብሔር ላይ እውነተኛ እምነት ያላቸው ሰዎች ሁሉ አባት የሆነውን የአብርሃምን ታሪክ እንመለከታለን። በዓለም ታሪክ ውስጥ እንደ አብርሃም እጅግ ጠቃሚ የሆኑ ሰዎች በጣም ጥቂቶች ናቸው። አይሁድም ሆኑ ዐረቦች ሁለቱም በሥጋ አባታችን አብርሃም ነው ይላሉ። እንዲሁም ክርስቲያኖችም አብርሃም መንፈሳዊ አባታችን ነው ይላሉ። የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍ. 12-24 አንብብ። ሀ) ከዘፍ. 12፡1-3) እግዚአብሔር ለአብርሃም ተስፋ የሰጠውን ሰባት በረከቶች ዘርዝር። ለ) በዘፍ. 15 እና 17 ወዘተ እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠውን ተጨማሪ የተስፋ ቃላት ዘርዝር። ሐ) እነዚህ ቃል ኪዳኖች በብሉይ ወይም በአዲስ ኪዳን የተፈጸሙት እንዴት ነው? መ) አብርሃም በሕይወት ዘመኑ የሄደባቸውን ከተማዎች ወይም ቦታዎች ዘርዝር። ሠ) የአብርሃምን ሕይወት በአጭሩ አጠቃለህ አቅርብ። በእግዚአብሔር ላይ ያለውን እምነት እንዴት እንደገለጸ አስረዳ። በእምነት ስላልተራመደባቸው ጊዜያት ግለጥ ወዘተ። ረ) አብርሃም በእምነት የመኖር ጥሩ ምሳሌ የሆነው ለምንድን ነው? ሰ) የራስህን የእምነት ጉዞ ከአብርሃም ሕይወት የእምነት ጉዞ ጋር አወዳድረህ የሚመሳሰልባቸውንና የሚለያይባቸውን ነገሮች ጥቀስ። ዘፍጥረት 11ን ባጠናንበት ጊዜ ከአብርሃም ቤተሰብ ጋር ተዋውቀናል። የአብርሃም ታሪክ የሚጀምረው በመስጴጦምያ በዑር ከተማ ነው። ዑር በመስጴጦምያ ከሚገኙ ታላላቅ ከተሞች አንዷ ስትሆን፥ የከፍተኛ ሥልጣኔ ማዕከልም ነበረች። ደግሞም ዑር የጣዖት አምልኮ ማዕከል ነበረች፤ ምክንያቱም ሰዎቹ የጨረቃን አምላክ ያመልኩ ነበርና ነው።  የውይይት ጥያቄ፥ ኢያሱ 24፡2-3 አንብብ። በእነዚህ ቁጥሮች በዑር ስለ ነበረው የአብርሃም ቤተሰብ ሃይማኖታዊ ሕይወት የተጻፈው ምንድን ነው? ስለ አብርሃም ቤተሰብ ምንም የተለየ ነገር አልነበረም። በዑር እንደነበሩ ሰዎች የአብርሃም አባት ታራና ቤተሰቡም የጨረቃና የከዋክብት አማልክትን የሚያመልኩ ይመስላል። ዳሩ ግን እግዚአብሔር ሉዓላዊ በሆነው ምርጫው የሥልጣኔና የሃይማኖት ብልሹነት ይታይባት የነበረችውን የዑር ከተማ ትቶ ሁሉንም ነገር እንደ አዲስ ወደሚጀምርበት ምድር እንዲሄድ አብርሃምን ጠራው። የአብርሃምን ሕይወት ለመረዳት የኦሪት ዘፍጥረትን የመጀመሪያ ክፍል ማስታወስ አለብን። እግዚአብሔር የአሠራር መንገዱን የለወጠበት ምክንያት ምንድን ነው? ከሰዎች ሁሉ ጋር በእኩልነት ከመሥራት ይልቅ ከአንድ ሰውና ከአንድ ሕዝብ ጋር ለመሥራት ለምን መረጠ? መልሱ ያለው በዘፍጥረት የመጀመሪያ 11 ምዕራፎች ውስጥ ነው። በአብርሃም ዘመን የዓለም ሁሉ መሠረታዊ ባሕርይ በእግዚአብሔር ላይ ማመፅ እንደነበር ታስታውሳለህ። እንዲከተሉት ለማድረግ እግዚአብሔር ለብዙ ዓመታት ከሰዎች ሁሉ ጋር ለመሥራት ሞክሯል። አሁንም በቀረው የብሉይ ኪዳን ክፍል እግዚአብሔር ዘዴውን ለወጠ። እግዚአብሔር አንድ ሰውና አንድ አነስተኛ ሕዝብ ለዓለም ብርሃን እንዲሆኑ ወሰነ። እግዚአብሔር ከሰዎች ሁሉ ጋር ሊኖረው የሚፈልገውን ግንኙነት በምሳሌነት እንዲያሳዩ የተመረጡ ነበሩ። ሌሎች ሕዝቦች እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን ጋር ያለውን ልዩ ኅብረት እንዲመለከቱና ይህ ኅብረት በመንፈሳዊና በሥጋዊ መንገድ የሚያስገኘውን ሽልማት (በረከት) እንዲያዩ ዐቅዶ ነበር። እነዚህ ሕዝቦች ይህን ኅብረት አይተው ከእግዚአብሔር ጋር ወዳለው ልዩ ኅብረት እንዲመጡ የእግዚአብሔር አሳብ ነበር። እስራኤላውያን በዓለም ላይ የእግዚአብሔር ተወካዮች ነበሩ። የሚያሳዝነው ግን የብሉይ ኪዳን ታሪክ እስራኤል ይህን ኃላፊነቷን መፈጸም አቅቷት መውደቋን የሚያሳይ መሆኑ ነው። በእግዚአብሔር ላይ ዓመፀች። ከዓለም ከመለየት ይልቅ እንደ ዓለም ተመላለሰች። እግዚአብሔር ዓለምን ለእርሱ ትማርክለት ዘንድ ያሰበውን ዕቅድ ልታሟላ ስላልቻለች፥ ሥራውን ከቤተ ክርስቲያን ጋር በሚሠራበት በአዲስ ኪዳን ዘመን ለጊዜው ገለል ተደረገች። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ለእስራኤል የነበረው ዓላማ ዛሬ እግዚአብሔር እኛ እንድሆን ከሚፈልገው ነገር ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ለ) እስራኤል በወደቀችበት መንገድ ቤተ ክርስቲያን ብዙ ጊዜ የምትወድቀው እንዴት ነው? ሐ) አንተና ቤተ ክርስቲያንህ በኅብረተሰቡ ውስጥ ይህንን ዓላማ የምታሟሉት እንዴት ነው? በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር የግንኙነት መስመር ተለውጦአል። ከዓለም ጋር በስፋት አልሠራም። ከአንድ ሕዝብም ጋር አልሠራም። ይልቁን ከተለያዩ ሕዝቦች መካከል ራሳቸውን ከዓለም ከለዩ ሰዎች ጋር መሥራት ጀመረ። ይህችም ቤተ ክርስቲያን ናት። ክርስቲያኖች የእርሱ ብርሃን እንዲሆኑና ለዓለም እንዲመሰክሩ ነበር። በሕይወታቸው በሚታየው ለውጥ ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር መንግሥትና ቤተሰብ ሊስቡ ያስፈልግ ነበር። የእርሱ ልጆች ነን ብለን ከምናስበው፥ ከእኛ እግዚአብሔር የሚፈልገው ይህንን ነው። ይህንን ዓላማ ለሕይወታችን እያሳካን ነውን? ሀ) ከላይ የተጠቀሰውን የቤተ ክርስቲያን ዓላማ አንተና ቤተ ክርስቲያንህ የምታሟሉባቸውን መንገዶች ጥቀስ። ለ) የተሻለ «የዓለም ብርሃንና ጨው» (ማቴ. 5፡13-16) ለመሆን እንድትችሉ አሁን ከምትሠሩበት መንገድ በተለየ ሁኔታ ልታከናውኑ የምትችሏቸውን አንዳንድ ነገሮች ዘርዝሩ። እግዚአብሔር በመጀመሪያ ዑርን እንዲለቅ የጠራው ታራን ይሁን ወይም አብርሃምን የምናውቀው ነገር የለም። ጥሪው የመጣው ግን ለአብርሃም ሳይሆን አይቀርም። አብርሃምም በዕድሜ የገፋ አባቱንና የወንድሙን ልጅ ሎጥን ከራሱ ጋር ይዞ ወጣ። የአብርሃም ወንድም የሆነው ናኮር ለጊዜው በዑር የቆየ ቢሆንም በኋላ ግን ወደኖረበት ወደ ካራን ሄደ። አብርሃምና ሣራ፥ ታራና ሎጥ ወደ ከነዓን ለመሄድ 1000 ኪሎ ሜትር ያህል ከተጓዙ በኋላ ወደ ካራን ከተማ ደረሱ። ወደ ከነዓን በሚወስደው መንገድ ላይ የነበረችው የመጨረሻዋ ዋና ከተማ ካራን ነበረች። ከግብፅ በመነሣት በከነዓን በኩል ወደ መስጴጦምያ በሚወስደው መንገድ ላይ ነበረች። ደግሞም የጨረቃ አምላክ የሚመለክባት ከተማ ነበረች። ታራ ምናልባት በእድሜ ስለገፋ፥ ወይም የለመደውን ባሕልና ሃይማኖትን ትቶ ለመሄድ ባለመፈለጉ ከአብርሃም ጋር በካራን ሰፈረ። በዚህ ስፍራ የኖሩት ለምን ያህል ጊዜ እንደሆነ አይታወቅም፤ ነገር ግን ከታራ ሞት በኋላ አብርሃም የእግዚአብሔርን ጥሪ እንደገና ተቀበለና ወደ ከነዓን ሄደ።  የአብርሃም መጠራት  ዘፍጥ. 12፡1-3 በመጽሐፍ ቅዱሳችን ከሚገኙ በጣም አስፈላጊና ጠቃሚ ክፍሎች አንዱ ነው። በብሉይና በአዲስ ኪዳን የነበረው የእግዚአብሔር ዕቅድ የተሠራበት መሠረት ነው። በእግዚአብሔርና በአብርሃም መካከል ለተደረገው ቃል ኪዳንም መሠረት ነው። አብርሃም በሕይወት እስከ ኖረበት ዘመን ድረስ እግዚአብሔር በመጀመሪያ በሰጠው የተስፋ ቃል ላይ በየጊዜው ይጨመርለት ነበር፤ ነገር ግን እግዚአብሔር አብርሃምን መጀመሪያ ሲጣራው የሰጠው ሰባት ተስፋዎች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለሚገኙ ተስፋዎች ሁሉ መሠረት ናቸው።  ከዚህ በታች እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባውን ሰባት የተስፋ ቃሎች እንዴት እንደፈጸመ እናያለን።  ለአብርሃም የተሰጡ ተስፋዎች              የተስፋዎቹ መፈጸም  «ታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ።»              የእስራኤል ሕዝብ («እባርክሃለሁ።»                             አብርሃም ባለጠጋ ሆነ። «ስምህን አከብረዋለሁ፡፡»                  አይሁድ፥ ዐረቦችና ክርስቲያኖች ሁሉም አብርሃምን እንደ                                                  አባታቸው ያከብሩታል። «በረከትም ትሆናለህ።»                    በአብርሃምና በዘሩ መጽሐፍ ቅዱስ ተጻፈ፤ ጌታ ኢየሱስ                                                 ተወለደ፥ ድነት ወደ ዓለም መጣ። («የሚባርኩህን እባርካለሁ፡፡»)          በዘመናት ሁሉ አይሁድን የሚባርኩ ሰዎችንና መንግሥታትን                                                 እግዚአብሔር ባርኮአቸዋል። «የሚረግሙህን እረግማለሁ።»           በመናት ሁሉ አይሁድን የሚያሳድዱ ሰዎችንና መንግሥታትን                                                 እግዚአብሔር በተራው አጥፍቷቸዋል። (ምሳሌ፡- ባቢሎን፣ አሦር)  «የምድር ነገዶች ሁሉ ባንተ ይባረካሉ።» በአብርሃምና በዘሩ ዓለም ሁሉ ተባርኳል። ይህ በተለይ እውን የሆነው እግዚአብሔር እራሱን ለዓለም የገለጠው በአይሁድ በኩል ስለሆነና የዓለም

የአብርሃም ታሪክ (ዘፍጥረት 12-24) Read More »

ዘፍጥረት 4-11 የኃጢአት በመላው ዓለም መሠራጨት

ከዘፍጥረት 4-11 ባለው ክፍል ውስጥ ሦስት ዋና ዋና ክንዋኔዎች አሉ። አንደኛ፥ አዳምና ሔዋን የመጀመሪያውን ክፋትና ኃጢአት ከሠሩበት ሰዓት ጀምሮ መስፋፋቱንና ከእነርሱ በኋላ የሚመጡትን ዝርያዎቻቸውን በሙሉ ማጥፋቱን ቀጠለ። ሁለተኛ፥ ከአዳም ጀምሮ እስከ አብርሃም ድረስ ያለውን የድነት (ደኅንነት) መስመር ማሳየት ነው። ሦስተኛው፥ እንደ ዓለም ፈቃድ መኖርን ትተው በእግዚአብሔር ፊት በጽድቅ የኖሩ የተለያዩ ሰዎችን ማሳየት ነው።  ፩. ኃጢአትና ፍርድ በሰው ዘር ላይ እንዴት እንደመጣ ተጠቅሶ እናገኛለን። በእነዚህ ምዕራፎች ሁሉ የኃጢአትና የሞት ዋና አሳብ እንዴት እንደተጠቀሰ አስተውል። ሀ. በዘፍ. 4 ቃየን በተገቢው መንገድ ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን ማቅረብ እንዴት እምቢ እንዳለ እናነባለን። አንዳንዶች እግዚአብሔር ያልተቀበለው ደም የሌለበት ስለ ነበረ ነው ይላሉ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር የቃየንን መሥዋዕት ያልተቀበለበት መሠረታዊ ምክንያት እርሱን የማምለኪያ ትክክለኛ መንገድ ስላልነበረው ነው። እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት አምልኮውን አላቀርብም አለ። ይህም የመጀመሪያውን ነፍስ ግድያ አስከተለ። ቃየን ወንድሙ አቤልን ገደለ። የውይይት ጥያቄ፥ ዛሬ እግዚአብሔርን በተሳሳተ ዝንባሌ ወይም ውስጣዊ አሳብ ማምለክ እንዴት ይቻላል? ለ. የቃየንን ዝርያዎች የማያቋርጥ ዓመፅ እንመለከታለን። የቃየን ዝርያዎች ለሥልጣኔ ለእድገትና ለበርካታ ከተሞች መቆርቆር ምክንያት የሆኑ ቢሆንም፥ ብዙ ሚስቶችን ማግባት ጀመሩ። እንዲያውም ላሜሕ አንድ ወጣት ሰው በመግደሉ ጉራውን ነዛ (ዘፍ. 4፡23-24)። ** ማስታወሻ፡- (ብዙ ሰዎች ቃየን እና ሴት ከየት ሚስት እንዳገኙ በማሰብ ይደነቃሉ። የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ብዙ ጊዜ ትኩረት የሚያደርገው በወንዶች ልጆች እንጂ በሴቶች ልጆች ላይ በደረሰው አይደለም፡፡ ከዘፍ. 5፡4 እንደምንረዳው አዳምና ሔዋን ወንዶች ልጆች ብቻ ሳይሆኑ፥ ሴቶች ልጆችም ነበሯቸው፤ ስለዚህ ቃየንና ሴት የራሳችውን እኅቶች እንዳገቡ መገመቱ ትክክል ነው። ይህ ነገር ከብዙ ዓመታት በኋላ ከግብፅ እስከ ወጡበት ጊዜ ድረስ በእግዚአብሔር የተከለከለ አልነበረም [ዘሌ. 18])። ሐ. ከአዳም እስከ ኖኅ ያለው የትውልዶች ታሪክ በተተነተነበት በዘፍ. 5 በተደጋጋሚ የሚነገር አንድ ቃል አለ። ይህም ቃል «ሞት» የሚል ነው። ለበርካታ ዓመታት ቢኖርም እንኳ የሰው ልጅ መጨረሻው ያው ሞት ነው። መ. በዘፍጥረት 6 የእግዚአብሔር ልጆች የሰውን ሴቶች ልጆች በማግባት ኃጢአት እንደሠሩ እንመለከታለን። ይህ ለመረዳት በጣም አስቸጋሪ የሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው፤ ስለዚህ ጉዳይ ምንነት የሚቀርቡ በርካታ አሳቦች አሉ፡- 1) «የእግዚአብሔር ልጆች» የሚለው ቃል ተፈጥሮአዊ ደረጃቸውን ትተው የሰውን ሴቶች ልጆች ስለ አገቡ መላእክት የሚናገር ሊሆን ይችላል። ይህንን አመለካከት ለመቀበል በጣም አስቸጋሪ የሚያደርገው መላእክት እንደማያገቡ ኢየሱስ ማስተማሩ ነው (ማር. 12፡25)። ሥጋዊ አካል የሌላቸው መንፈሳዊ ፍጥረታት ስለሆኑ ሴቶችን እንዴት ሊያገቡ ይችላሉ? «የእግዚአብሔር ልጆች» የሚለው ቃል የፖለቲካ መሪዎችን ያመለክታል የሚሉም አሉ። (የጥንት ሰዎች መሪዎቻቸውን «አምላክ» ብለው ይጠሩ ነበር።) ኃጢአቱም፡- እነዚህ መሪዎች ከሴቶች ጋር የፍትወተ ሥጋ ፍላጎታቸውን ለመፈፀም የጋብቻን ቅድስና በመተላለፍ ብዙ ሴቶችን ማግባት መጀመራቸው ነው። በዚህም የሕዝቡን የሥነ- ምግባር መሠረት አበላሹት። 3) «የእግዚአብሔር ልጆች» ፈሪሃ-እግዚአብሔር ያላቸው፥ የተለዩና ሴት የተባለው ሰው ዘሮች ነበሩ። «የሰዎች ሴቶች ልጆች» የቃየን ዝርያዎች ነበሩ። ኃጢአቱ፡- ዛሬ ክርስቲያኖች የማያምኑትን እንዳያገቡ እንደተነገራቸው ሁሉ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች እግዚአብሔርን ከማይፈሩት ጋር ጋብቻ መመሥረታቸው ነበር (1ኛ ቆሮ. 7፡39፤ 2ኛ ቆሮ. 6፡14)። ይህ ነገር የእግዚአብሔር ቤተሰቦች የሆኑ ሰዎች ምግባረ ብልሹ እንዲሆኑና ብዙ ሰዎች በእግዚአብሔር ላይ ካላቸው እምነት እንዲርቁ መንገድ ከፍቷል። ከእነዚህ አመለካከቶች የትኛው እንደሚሻል ማወቅ በጣም አስቸጋሪ ነው። ከሁሉ የሚሻለው ምርጫ 1ኛው ወይም 3ኛው አመለካከት ይመስላል። እያንዳንዱ አመለካከት የራሱ ችግር አለው። ዛሬም ቢሆን ከኃጢአታቸው በስተኋላ ያለው አሳብ ግልጥ ነው። እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ከሚያገቡአቸው ሴቶች መንፈሳዊ መመዘኛን ከመፈለግ ይልቅ፥ ስለ አካላዊ ውበትና ስለ ፍትወተ ሥጋ ፍላጎት ብቻ ያስባሉ። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬ ሰዎች የትዳር ጓደኛ በሚመርጡበት ጊዜ ያላቸው ተመሳሳይ አመለካከት ምንድን ነው? ለ) አንድ ክርስቲያን የሚያገባው በመልክ ቁንጅናና ከጥሩ ቤተሰብ በመገኘት ብቻ ከሆነ ስሕተት የሚሆነው ለምንድን ነው? ሐ) የትዳር ጓደኛን የመምረጫ እጅግ ጠቃሚ መመዘኛዎች የትኞቹ ናቸው? በኦሪት ዘፍጥረት 6 የሚገኘው ታሪክ በተፈጸመ ጊዜ ክፋትና ኃጢአት እጅግ ተስፋፍቶ ስለ ነበር እግዚአብሔር ሰውን በመፍጠሩ ተጸጸተ። ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ በሆነ ግንኙነት ይኖር የነበረ አንድ ሰው ኖኅ ብቻ ነበር፤ ስለዚህ ከዘፍ. 6-9 ባለው ክፍል እግዚአብሔር የሰውን ዘር ለማጥፋት ስለተጠቀመበት የጥፋት ውኃ እናነባለን። የጥፋት ውኃ ዓላማ በክፉው የሰው ልጅ ላይ ለመፍረድና የእግዚአብሔር ሰው የሆነው ኖኅ በአዲስ መልክ እንዲጀምር ለማድረግ ነበር። ልክ እንደ አዳም ኖኅ የሰው ዘር ሁሉ ራስ ሆነ። ዛሬ በምድር ላይ ያሉ ሰዎች በሙሉ የተገኙት ከኖኅ ነው። ሠ. ከዘፍ. 10-11 ክፍል ክፋት በጥፋት ውኃ ሊጠፋ እንዴት እንዳልቻለ እናያለን። ኖኅ የእግዚአብሔር ሰው ቢሆንም፥ እርሱና ቤተሰቡ የክፋት ባሕርይ ነበረባቸው። በመጀመሪያ፥ ኖኅ ጠጥቶ ሰከረና ጨዋነት በጎደለው መንገድ እራቁቱን ሆነ። ከዚያም የኖኅ ልጆች ከነበሩት አንዱ የሆነው ካም የአባቱን እርቃነ-ሥጋ አየ። ከዚህ የተነሣ የካም ልጅ የነበረውና የእስራኤል ሕዝብ ጠላት የሆኑት የከነዓናውያን አባት ከነዓን በኖኅ ተረገመ።  ** (ማስታወሻ፡- አንዳንድ ሰዎች የተረገመው ከነዓን እንጂ ካም ስላልሆነ ከነዓንም በኖኅ ላይ ኃጢአት ሠርቷል የሚል አስተሳሰብ አላቸው። በምንም ሁኔታ ይሁን ኖኅ በነቢይነት የከነዓን ዘር የሴምና የያፌት ዘሮች ባሪያ እንደሚሆን አስቀድሞ ተናገረ፤ ነገር ግን ይህን ታሪክ ነጮች ጥቁሮችን ለመግዛት ሊጠቀሙበት አይገባም)። ሁለተኛ፡- የኖኅ ዝርያዎች በሙሉ ብዙ ሳይቆዩ በኃጢአት ውስጥ ተዘፈቁ። በትዕቢታቸውና ሐሰተኞች አማልክትን ለማምለክ በመፈለጋቸው የባቢሎንን ግንብ ለመሥራት ተነሡ። ይህም ምድርን እንዲሞሉ ያዘዛቸውን እግዚአብሔር በተዘዋዋሪ መንገድ አንታዘዝም ማለት ነበር፤ ዳሩ ግን ለመበታተን አልፈለጉም ነበር (ዘፍ. 9፡7፤ 11፡4 ተመልከት)። አሁን ደግሞ እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ደባልቆ እንዲበተኑ በማድረግ በሰው ልጆች ላይ ፈረደባቸው። በዘፍ. 10 በምድር የሚገኙ የሰው ዝርያዎች ሁሉ ከየት እንደመጡ ተጽፏል። ነጮችና የምሥራቅ ሰዎች የመጡት ከያፌት ዘር ነው። ዓረቦችና አይሁድ የመጡት ከሴም ዘር ነው። አፍሪካውያን ደግሞ የመጡት ከካም ዘር ነው።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ኃጢአት በኖኅና በቤተሰቦቹ የመቀጠሉ እውነታ ኃጢአት ከትውልድ ወደ ትውልድ ስለ መተላለፉ ምን ይነግረናል? ለ) ዛሬ የኃጢአት ባሕርይ ከወላጆች ወደ ልጆች የመተላለፉን እውነታ እንዴት እናየዋለን?  ፪. ከአዳም እስከ አብርሃም ያለው እግዚአብሔርን የሚፈራው ትውልድ።  የእነዚህ ምዕራፎች ሁለተኛ ዓላማ ደግሞ የአብርሃምን የዘር ሐረግ ወደ ኋላ በመመለስ እስከ መጀመሪያው ሰው እስከ አዳም ድረስ ማሳየት ነው። በዘፍጥረት 5 ሙሴ አሥር ትውልዶችን በመዘርዘር ከአዳም እስከ ኖኅ ድረስ ያለውን የትውልድ አመጣጥ አሳይቷል። በዘፍ. 11፡10-32 ደግሞ ሙሴ የአዳምን የዘር ሐረግ የኖኅ ልጅ እስከሆነው እስከ ሴም ከዚያም እስከ አብርሃም ድረስ ያሳያል። እርሱም የተመረጡና እሥራኤል ተብሎ የተጠራው የእግዚአብሔር ሕዝብ ራስ ነው። «አባት» የሚለው የዕብራይስጥ ቃል አያትን ወይም ቅድመ አያትን የሚያሳይ ስለሆነ እነዚህ ቁጥሮች አሥር ትውልዶችን ይሁን ወይም አንዱ የሌላው ዘር መሆኑን ብቻ የሚያሳዩ ይሆኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ከስምምነት ላይ መድረስ አልቻሉም። ፫. የዓለምን መንገድ ለመከተል እምቢ ያሉና ጻድቃን የሆኑ ሰዎች ምሳሌ፡፡ አብዛኛው የዚህ ክፍል ታሪክ ትኩረት በዓለም ላይ ኃጢአት እየተስፋፋ ስለመምጣቱ ቢሆንም፥ ስለ ኃጢአትና ፍርድ በሚናገሩ ታሪኮች ውስጥ የተለዩ ሕዝቦች ታሪኮች ተሰውረው እናገኛለን። እነዚህም ሦስት የተለያዩ ሰዎች በብዙኃኑ ሕዝብ መካከል ያለውን ኃጢአት ተቋቁመው በእግዚአብሔርም ፊት የጽድቅን ሕይወት የኖሩ ናቸው። የመጀመሪያው ሄኖክ ነበር። ስለ ሄኖክ ሕይወት የተጻፈልንና የምናውቀው ነገር «አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር ማድረጉ» ነው፤ ስለዚህም እግዚአብሔር ሞትን ሳያይ ወደ ሰማይ ወሰደው። እርሱም ሞትን ሳያይ ወደ መንግሥተ ሰማያት የተወሰደ የመጀመሪያ ሰው ነው። ሁለተኛ፥ ኖኅን እናገኛለን። ስለ ኖኅ «በትውልዱ ጻድቅ ፍጹምም ሰው ነበር» ተብሎላታል (ዘፍ. 6፡9)። ስለሆነም ቀሪውን የሰውን ዘር በሙሉ ካጠፋው ውኃ እግዚአብሔር እርሱንና ቤተሰቡን አድኖአል። የጥፋት ውኃንና እግዚአብሔር ኖኅን እንዴት እንደጠበቀው የሚናገረውን ታሪክ ከዘፍጥረት 6-9 ባለው ክፍል እናገኛለን። በታሪኩ ውስጥ የሚከተሉትን ነገሮች

ዘፍጥረት 4-11 የኃጢአት በመላው ዓለም መሠራጨት Read More »

የአዳምና የሔዋን ኃጢአት (ከዘፍ. 3)

የውይይት ጥያቄ፥ ከዘፍ. 3 በሰው መጀመሪያ ኃጢአት በተሳተፉት ላይ የደረሰባቸውን እርግማን ዘርዝር። ዘፍ. 3 ስለ ሰው የመጀመሪያ ኃጢአት ይናገራል። ይህም በእግዚአብሔር ላይ የፈጸመው የመጀመሪያው ዓመፅ ነበር። እግዚአብሔር በመጀመሪያ አዳምና ሔዋንን ሲፈጥር፥ በሥነ- ምግባር ፍጹም ነበሩ። የኃጢአት ተፈጥሮ ስለሌላባቸው ኃጢአት ሊያደርጉ የሚችሉበት ምክንያት አልነበረም። ምሁራን ይህንን «የንጽሕና ደረጃ» ብለው ይጠሩታል፤ ምክንያቱም በዚህ ጊዜ አዳምና ሔዋን ኃጢአት ምን እንደሆነ እንኳ አያውቁም ነበር። እግዚአብሔር አዳምና ሔዋንን በዔደን ገነት ባኖረ ጊዜ ከፍሬው እንዳይበሉ የከለከላቸው አንድ ዛፍ ነበር። ይህ ፍሬ «መልካሙንና ክፉውን ከሚያስታውቅ ዛፍ» የሚገኝ ነበር። ሰይጣን በእግዚአብሔር ላይ ያመፀው አስቀድሞ ነበር። አዳምና ሔዋንም በእግዚአብሔር ላይ እንዲያምፁ በማድረግ ፍጥረታትን ሁሉ ሊያበላሽ ቆረጠ፤ ስለዚህ ሰይጣን ወደ ሔዋን ቀረበ። ስለ እግዚአብሔር ትእዛዝ የተምታታ አሳብ እንዲኖራት አደረገ። ከዚህም በኋላ ሔዋንን ትእዛዙን በሰጣት በእግዚአብሔር ዓላማና ባህርይ ላይ እንድትጠራጠር አደረጋት። አዳምና ሔዋን ሁለቱም የተከለከለውን ፍሬ በሉ። በመጀመሪያ የተታለለችውና በኃጢአት በመውደቅ ለእግዚአብሔር ያልታዘዘችው ሔዋን ብትሆንም አዳምም በኃጢአት የወደቀው እያወቀ ነው። እግዚአብሔርን በመታዘዝ ፈንታ ሔዋንን መከተል መረጠ። አንዳንድ ምሁራን፡ – ሔዋን በተታለለች ጊዜ አዳም አብሮአት ነበር፤ ሆኖም ከስሕተት እንድትርቅ ሊያደርጋት አልፈለገም ይላሉ። የውይይት ጥያቄ ፥ ኃጢአት በምናደርግበት ጊዜ አዳምና ሔዋን ከሠሩት ኃጢአት ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው? የመጀመሪያው የሰው ልጅ ኃጢአት ፈጣሪ በሆነው እግዚአብሔር ላይ ማመፅ ነበር። ፈጣሪያቸው የሆነው ጌታ ፍሬውን እንዳይበሉ የመከልከል ሙሉ መብት ነበረው፤ ነገር ግን የራሳቸውን ፍላጎት ለማድረግ ስለፈለጉ ዓመፁ። በእያንዳንዱ ኃጢአት ውስጥ ያለው ተመሳሳይ ዝንባሌ ይህ ነው። እያንዳንዱ ኃጢአት በእግዚአብሔር ላይ የሚደረግ ዓመፅ ነው። ለእግዚአብሔር ራስን ባለመስጠት ለትእዛዙ አልገዛም ማለት ነው። ፈጣሪያችን ለሆነው ለእግዚአብሔር ትእዛዛት ራሳችንን ከማስገዛት ይልቅ በራሳችን ሕይወት ላይ ለመሠልጠን የምናደርገው ጥረት ነው።  የመጀመሪያው የአዳምና ሔዋን ኃጢአት ለብዙዎች የሚደርሱ አስጨናቂ ውጤቶችን አስከተለ። አዳምና ሔዋን ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ወዲያውኑ አቋርጦ ከእግዚአብሔር እንዲደበቁ አደረገ።  በአራት ነገሮች ላይ ቅጽበታዊ ፍርድ አመጣ፡- ሀ. በእባቡ ላይ አካላዊና ተምሳሌታዊ ፍርድን አመጣ። እባብ ተፈጥሮው ተለውጦ በሆዱ የሚሳብ እንስሳ ሆነ። በእባብ ተመስሎ የቀረበው ሰይጣን ተፈርዶበት የመጨረሻ ሽንፈቱ ተነገረ።  ለ. ሔዋንና ሴቶች ሁሉ ተፈረደባቸው። ከዚህ የተነሣ ልጅ መውለድ አስጨናቂ ሂደት ሆነ። ሴቶች ከባሎቻቸው ጋር የነበራቸው የእኩልነት ግንኙነት ተለውጦ ለባሎቻቸው የሚገዙ ሆኑ።  ሐ. አዳምና ወንዶች ሁሉ ተፈረደባቸው። ሥራቸው ቀላልና የሚያስደስት መሆኑ ቀረና የቤተሰቦቻቸውን ሁሉ ፍላጎት ለማርካት በማያቋርጥ ፍልሚያ ውስጥ ገቡ።  መ. ፍጥረት ተረገመ። የሰው ልጅ ወዳጅ መሆኑ ቀረና ጠላት ሆነ። ለእሾህ፥ አሜከላ፥ ራብ፥ የመሬት መንቀጥቀጥና ሌሎች አጥፊ ነገሮች መከሰቻ ሆነ።  የመጀመሪያውን እንስሳ መገደልና በመጨረሻም የሰዎች ሁሉ ሞትን አስከተለ። አንዳንድ ሰዎች እግዚአብሔር «ደም ሳይፈስ ስርየት የለም» (ዕብ. 9፡22) የሚለው መንፈሳዊ መመሪያ የጀመረው በዚህ ጊዜ ነው ይላሉ። እግዚአብሔር ለአዳምና ለሔዋን ራቁትነታቸውን ለመሸፈን ቁርበት ማልበስ ብቻ ሳይሆን፥ ለኃጢአታቸውም እንስሳን ሠዋ። በብሉይ ኪዳን ለጊዜውም ቢሆን ኃጢአቱን ይሸፍን የነበረው የእንስሳ ደም ነበር። በአዲስ ኪዳን ግን ኢየሱስ ለኃጢአት የሚሆን የመጨረሻ መሥዋዕት ሆነ (ዕብ. 9፡22፥ 26-27 ተመልከት)። ከእነርሱ በኋላ በሰው ልጆች ሁሉ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ አስከተለ። አዳምና ሔዋን ከእነርሱ በኋላ ለሚወለዱ ሰዎች በሙሉ ራስ በመሆናቸው በሰው ልጆች ላይ ፍርድን አመጡ። ይህ ፍርድ የሰዎችን ሕይወት በምድር ላይ አስቸጋሪ ከማድረጉ ሌላ ሥጋዊ ሞት የሰው ልጆች ሁሉ የመጨረሻ ዕጣ መሆኑን እርግጠኛ አደረገው። ይህም ማለት ልጆቻቸው ሁሉ በእግዚአብሔር ላይ ያለማቋረጥ ወደማመፅ የሚወስዳቸውን የኃጢአት ባሕርይ ጭምር ወረሱ ማለት ነው። አዳምና ሔዋንን ከዔደን ገነት እንዲባረሩ አደረጋቸው። ይህ እርምጃ የጸጋም የፍርድም እርምጃ ነው። ከሕይወት ዛፍ ፍሬ ወስደው በመብላት በኃጢአት ለዘላለም እንዳይኖሩ እግዚአብሔር በጸጋና በፍርድ ከዔደን ገነት አባረራቸው።  የውይይት ጥያቄ፥ የእነዚህ ኃጢአቶች ውጤት ዛሬ በሕይወትህ እንዴት ይታያል? በአዲስ ኪዳን፥ ክርስቶስ ኃጢአት ያመጣቸውን ነገሮች ማስወገድ ጀምሮ እናያለን። በባልና በሚስት መካከል የነበረው ግንኙነት መስተካከል ነበረበት። በመጨረሻም ዘላለማዊ መንግሥቱ ሲጀመር ይህንን እርግማን ሁሉ እግዚአብሔር እንደሚያስወግድ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ እንመለከታለን (ራእ. 21-22)። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የአዳምና የሔዋን ኃጢአት (ከዘፍ. 3) Read More »

ዘፍጥረት 1-2 የዓለም አፈጣጠር

መጽሐፍ ቅዱስ የሳይንስ ማስተማሪያ ወይም የታሪክ መጽሐፍ አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ ሳይንስንም ሆነ ታሪክን የሚመለከት መረጃ የያዘ ቢሆንም ዓላማው ግን ይህ አይደለም። የመጽሐፍ ቅዱስ ዓላማ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰው ልጅ መግለጥ ነው። እግዚአብሔር ዛሬም ቢሆን ለሰው ልጆች የሚናገርበት ዋናው መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። አንዳንዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መረጃ ሳይንስንና ታሪክን የሚመለከት ጉዳይ ቢኖረውም፥ ሳይንስና ታሪክ መርምረው ያገኙት አብዛኛው ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ አልተካተተም። ሆኖም መጽሐፍ ቅዱስ የገለጠው ነገር ሁሉ በሳይንቲስቶችና በታሪክ አዋቂዎች ዛሬ ባይታመን እንኳ፥ ሊታመንና ተቀባይነት ሊያገኝ ይገባል። ክርስቲያኖች እንደመሆናችን ከሰዎች አስተሳሰብና አመለካከት ይልቅ የእግዚአብሔርን ቃል መምረጥ አለብን።  እንደምናውቀው ዘፍጥረት 1፡1 እንደ ዮሐ. 1፡1 ወደ ጊዜና ወደ ታሪክ መጀመሪያ ይመልሰናል። ይህ የእግዚአብሔር መጀመሪያ ሳይሆን፥ የተፈጠሩ ነገሮች ሁሉ መጀመሪያ ነው። እግዚአብሔር ዘላለማዊ ስለሆነ መጀመሪያ የለውም።  ዘፍጥረት 1-2 የፍጥረታት ታሪክ አጠር ባለ መልክ አጠቃልሉ ያቀርበዋል። ዘፍጥረት 1 ፍጥረትን ሁሉ በመገምገምና በእያንዳንዱ ቀን የተፈጠረውን ነገር በመናገር የፍጥረታትን ታሪክ ያሳየናል። ከፍጥረታት ሁሉ በመጨረሻ የተፈጠረው የሰው ልጅ ምን ያህል ከሁሉ የላቀ ፍጡር መሆኑንም ያመለክታል። ዘፍጥረት 2 የሚያተኩረው ወንድና ሴት ሆኖ በተፈጠረው በሰው ልጅ ላይ ሲሆን፥ ይኖርበት ዘንድ ስለተዘጋጀለት ዔደን ተብሎ ስለሚጠራው ስፍራም ይናገራል። በዘፍጥረት 1 እግዚአብሔር ነገሮች ሁሉ እንዴት እንደተፈጠሩ ለማሳየት አይፈልግም። ለምሳሌ መላእክት ወይም ሰይጣን የተፈጠሩት እንዴትና መቼ እንደሆነ የሚናገር ነገር የለም። ይልቁንም በቀላል ቋንቋ እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ፈጣሪ እንደሆነ ተገልጧል። ስለዚህ የተፈጠሩ ነገሮች በሙሉ የፈጣሪያቸው የእግዚአብሔር ንብረት ናቸው። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ፈጣሪያችን ስለሆነ ስለ እርሱ ሊኖረን የሚገባ አመለካከት ምን ዓይነት ነው? ለ) እግዚአብሔር ፈጣሪያችንን ልናከብር የምንችልባቸውን መንገዶች ግለጥ።  በዓለም ላይ የምናያቸው ነገሮች በሙሉ ስለተገኙባቸው መንገዶች የሚናገሩ አምስት የተለያዩ አመለካከቶች አሉ። ከእነዚህ መካከል ሁለቱ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን የማይቀበሉ ክርስቲያን ያልሆኑ ሰዎች አመለካከቶች ናቸው። ክርስቲያን ባልሆኑ ሰዎች የሚንፀባረቁ ሁለት አመለካከቶች  የተፈጠሩ ነገሮች በሙሉ ፈጣሪዎቻቸው የሆኑ የተለያዩ አማልክት የሥራ ውጤቶች ናቸው። ይህ አመለካከት እውነተኛውን አምላክ የማያውቁ የጥንት ሰዎች የሚያንፀባርቁት ነው። ለምሳሌ፡- በብዙ አማልክት የሚያምኑ አንዳንድ ጣዖት አምላኪዎች፡- ምድር የፀሐይ አምላክና የሴት ጨረቃ አምላክ ልጅ ነው ብለው ያምኑ ነበር። በተጨማሪም የሰው ልጅ ከአማልክት መካከል የአንዱ ዝርያ ነው ብለው ያምኑ ነበር። ይህም የቀድሞዎቹ ባቢሎናውያን፥ ግሪኮች፥ ሮማውያንና ከነዓናውያን አመለካከት ነበር። ዛሬም የብዙ አፍሪካውያን አመለካከት ሲሆን ሂንዱይዝም በተባለው በምሥራቃውያን እምነት ውስጥም የሚታይ ነው። እግዚአብሔር የፍጥረታትን ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዲካተት ያደረገበት አንዱ ምክንያት እርሱ ብቻ የሁሉ ነገር ፈጣሪ እንደሆነ ለማሳየት ነው። ዛሬ እግዚአብሔር እስራኤላውያንንና እኛን አንድ እውነተኛ አምላክ ብቻ እንዳለ ሊያስተምረን ይፈልጋል። እግዚአብሔር «በምድርና በሰማይ ያሉ» ነገሮች ሁሉ ፈጣሪ ነው። ለሰው ልጅ ትክክለኛ ቦታው ራሱን ለእግዚአብሔር አሳልፎ በመስጠት ፈጣሪውና ጌታው መሆኑን ተረድቶ እርሱን በማክበር መኖር ነው።  የተፈጠሩ ነገሮች በሙሉ የተፈጥሮ «አዝጋሚ ለውጥ» (ኢቮሉሽን) ውጤቶች ናቸው። ይህ ፅንሰ አሳብ ብዙዎቻችን በመንግሥት ትምህርት ቤት የተማርነው ነው። አዝጋሚ ለውጥ እንዴት እንደተፈጸመ የሚያስረዱ በርካታ የተለያዩ ንድፈ አሳቦች ቢኖሩም፥ ይህ አመለካከት የሚያስተምረው ከብዙ ቢሊዮን ዓመታት በፊት አንድ ታላቅ ፍንዳታ ተፈጽሞ ፀሐይ፥ ከዋክብት፥ ሌሉች ፕላኔቶች፥ ወዘተ. ተፈጠሩ። በአንድ ባልታወቀ ምክንያት ሕይወት መጀመሪያ ከተፈጠረው ፕላኔት ይወጣ ጀመር። ከዚያም በመጀመሪያ ዕፀዋት፥ ቀጥሉም እንደ አሜባ ያሉ በጣም ጥቃቅን እንስሳት ተገኙ። እነርሱም ቀስ በቀስ እንቁራሪት ወደ መሳሰሉ እንስሳት ተለወጡ። እነዚያ ደግሞ ቀስ በቀስ ወደ ጡት አጥቢ እንስሳት ተለወጡ በማለት ነው፤ ስለዚህ በቀላል አማርኛ ሰው ከፍተኛው የአዝጋሚ ሂደት ለውጥ ውጤት ነው። ይህ አመለካከት ለእግዚአብሔርና እርሱ ለፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ ምንም ቦታ አይሰጥም። ሕዝ. 28፡11-17። በእግዚአብሔርና በሰይጣን መካከል በተደረገው ጦርነት የመጀመሪያዋ ምድር ወደ ባዶነትና ጨለማ ተለወጠች በማለት ግምታዊ አስተሳሰባቸውን ይሰጣሉ። ስለዚህ ይህ አመለካከት ያላቸው ሰዎች ዘፍጥረት ምዕራፍ አንድን ምርኩዝ በማድረግ እግዚአብሔር ዓለምን እንደገና ጠግኖአል ወይም አድሶአል በማለት ያስተምራሉ። ይህ አመለካከት ሙሉ በሙሉ እንደማይሆን አድርጎ ለመቃወም ባይቻልም ሁለት ዓለማት ስለ መፈጠራቸው መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው ማስረጃ የለም።  ዘፍጥረት 1 የሚናገረው እግዚአብሔር ዛሬ በዓለም ላይ የሚገኙትን ነገሮች ሁሉ እንዴት እንደፈጠረ ነው። ቁሳዊ የሆኑትን ነገሮች በሙሉ እግዚአብሔር በስድስት ቀናት ውስጥ የፈጠራቸው ናቸው። የተፈጠሩትም ከምንም ነው (ዕብ. 11፡3 ተመልከት)። ይህ አመለካከት በዘመናት ሁሉ አብዛኛዎቹ ክርስቲያኖች ያመኑበት ሲሆን ከሌሎች ሁሉ በተሻለ ሁኔታ ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ጋር የሚስማማ ነው። ማንም ሰው እነዚህን አመለካከቶች «ማረጋገጥ» አይችልም። ይልቁንም ክርስቲያኖችም ሆኑ ክርስቲያን ያልሆኑ ሰዎች የሚከተሉአቸው እነዚህ አመለካከቶች እምነትን ወይም ሊያዩ የማይችሉትን ነገር መቀበልን ይጠይቃል። የማያምኑ ሰዎችን ሁሉ ማርካት በሚቻልበት መንገድ ክርስቲያኖች ሊገልጹዋቸው የማይችሉዋቸው አንዳንድ ነገሮች ቢኖሩም፥ በዕብ. 11፡3 እንደምናነበው እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ፈጣሪ መሆኑን የምንቀበለው «በእምነት» ነው። ይህ ማለት እኛ የእርሱ ፍጥረት ነን። እርሱ ፈጣሪ በመሆኑ በእኛ ላይ ሙሉ ሥልጣን አለው። እኛም ለእርሱ በመገዛት መኖር አለብን። የውይይት ጥያቄ፥ ሕይወታችንን በሙሉ ለእግዚአብሔር ለመስጠትና እርሱን ሙሉ በሙሉ ለመታዘዝ የምንቸገረው ለምንድን ነው? እስካሁን ባለን እውቀት አንጻር እግዚአብሔር ዓለምን በስድስት ቀናት እንደፈጠረ ማመን ከሁሉም የሚሻል ነገር ይመስላል። እግዚአብሔር እንደሌለና ነገሮች ሁሉ የአዝጋሚ ለውጥ ውጤቶች እንደሆኑ የሚያምኑ ሰዎችን አጥብቀን መቃወም ያለብን ቢሆንም፥ እኛ ስለ ፍጥረታት አፈጣጠር ካለን አመለካከት ለየት ያለ እምነት ያላቸውን ክርስቲያኖች መቀበል አለብን። ደኅንነታችን የተመሠረተው ስለ ፍጥረታት ባለን ትክክለኛ አመለካከት ሳይሆን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ባለን እምነት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ፍጥረት የሚናገረው ታሪክ እኛ ለማወቅ የምንፈልገውን ነገር ሁሉ የሚያብራራ ሳይንሳዊ ዘገባ አይደለም። የፍጥረት ታሪክ የተገለጠበት ዓላማ እግዚአብሔር ፈጣሪ እንደሆነና እኛ የእርሱ ልዩ ፍጥረቶች እንደሆንን በግልጥ ለማስተማር ነው። ይሁን እንጂ የእግዚአብሔርን ቃል ትክክለኛነት በምንም ዓይነት ሁኔታ ከመጠራጠር መጠንቀቅ አለብን። የእግዚአብሔርን ቃል ከለወጥንና እርሱ በግልጽ ከሚያስተምረን ነገር የተለየ አመለካከት ካለን፥ መሠረታችንን አጣን ማለት ነው። ስለ ፍጥረት አፈጣጠር መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠው ትምህርት የተሳሳተ ከሆነ ስለ እግዚአብሔር ማንነት፥ ስለ ኢየሱስ ማንነትና እኛን እንዴት እንዳዳነን፥ ወዘተ. የሚሰጠው ትምህርትም የተሳሳተ ሊሆን ይችላል ማለት ነው። እኛም ሆንን ሌሉች ክርስቲያኖች የምንከተለው ማንኛውም አመለካከት በእግዚአብሔር ቃል ላይ በሚገባ የተመሠረተ መሆን አለበት። ዘፍ. 1፡1-2 የፍጥረት ታሪክ መግቢያ ነው። በመግቢያው ውስጥ እግዚአብሔር የፍጥረት ሁሉ ምንጭ እንደሆነ ይገልጻል። የቀረው የፍጥረት ሥራም እንዴት እንደተከናወነ የሚገልጽ አስተዋጽኦ ይሰጣል። እግዚአብሔር ምንም ቅርፅ የሌላትን ዓለም ወስዶ ቅርፅ ሰጣት። እንዲሁም ባዶና አንዳች ያልነበረባትን ዓለም ወስዶ በተለያዩ ነገሮች ሞላት።  ከዘፍጥረት ታሪክ የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡. አንደኛ፥ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር የፈጠረባቸው ስድስት ቀናት ነበሩ። ሁለተኛ፥ የፍጥረትን ሥራ የሚመለከቱ ሁለት ዋና ዋና ክፍሎች አሉ። የመጀመሪያው ክፍል እግዚአብሔር ለምድር ቅርፅን እንደሰጠ የሚናገር ሲሆን፥ ሁለተኛው ክፍል ደግሞ እግዚአብሔር የፈጠረውን ነገር በተለያዩ ነገሮች እንደሞላ ይናገራል። ሦስተኛው፥ የሁለቱ ክፍሎች እያንዳንዱ ቀን የተያያዘ ነው። ለምሳሌ፡- 1ኛና 4ኛ ቀናት በሰማይ ስላሉ ብርሃናት መፈጠር ይናገራሉ። 2ኛና 5ኛ ቀናት እግዚአብሔር ባሕርንና ጠፈርን ሲያዘጋጃቸውና ሲሞላቸው እናያለን። 3ኛና 6ኛ ቀናት ደረቅ ምድርን የማዘጋጀትና የመሙላት ሥራ የተከናወነባቸው ቀናት ናቸው። ይህም ዓለምን የመፍጠር ሥራ ግልጥ የሆነ ቅንብር ተደርጎለት እንደ ነበር ያሳየናል። እግዚአብሔር ሰውን በፈጠረ ጊዜ ይህ ሥራ የሥላሴ ተግባር ነበር። በዘፍ. 1፡2 እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ ሥራ አማካይነት የመፍጠርን ተግባር እንዳከናወነ እናነባለን። እግዚአብሔር «እንፍጠር» እያለ ራሱን በብዙ ቁጥር ሲጠራ እንመለከታለን (ዘፍ. 1፡26)። ይህንን በተለያዩ መንገዶች መረዳት ቢቻልም፥ እግዚአብሔር ሦስት አካላት አሉት። እነርሱም እግዚአብሔር አብ፥ እግዚአብሔር ወልድ፥ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሲሆኑ፥ አዲስ ኪዳን በሚሰጠው በዚህ ትምህርት መሠረት ሥላሴ ፍጥረትን በሚመለከት አብረው እንደወሰኑና ሦስቱም በመፍጠር ሥራ ውስጥ እንደተሳተፉ እናያለን። 

ዘፍጥረት 1-2 የዓለም አፈጣጠር Read More »

የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ቅደም ተከተልና አስተዋጽኦ፣ ልዩ ባሕሪያት እና ዓላማ

የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ቅደም ተከተልና አስተዋጽኦ የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት ዘፍ. 2፡4፤ 5፡1፤ 6፡9፣ 10፡1፤ 11፡10፤ 11፡27፤ 25፡12፤ 25፡19፤ 36፡1፥ 9፤ 37፡2። ሙሴ፡- «የ…..ታሪክ ይህ ነው» የሚላቸውን የተለያዩ ነገሮችን ዘርዝር። ሙሴ ኦሪት ዘፍጥረትን በሚጽፍበት ጊዜ ግልጽ የሆነ አስተዋጽኦ ነበረው። መጽሐፉን ያቀናበረው «የ…ይህ ነው» በሚሉት ቃላት ዙሪያ ነበር። ብዙ ምሁራን ይህንን አከፋፈል የኦሪት ዘፍጥረትን አስተዋጽኦ ለመንደፍ ይጠቀሙበታል። መግቢያ፡- የነገሮች ሁሉ አፈጣጠር (ዘፍጥ. 1፡1-2፡3)  ከአይሁድ አባቶች በፊት የነበረው ዘመን (ዘፍ. 2፡4-11፡26) ሀ) የሰማይና የምድር መፈጠር ታሪክ (ዘፍ. 2፡4-4፡26)  ለ) የአዳም ትውልድ እና የልጆቹ ታሪክ (ዘፍ. 5፡1-6፡8)  ሐ) የኖኅ ታሪክ (ዘፍ. 6፡9-9፡29)  መ) የሴም፥ የካምና የያፌት ታሪክ (ዘፍ. 10፡1-11፡9) ሠ) የሴም ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 11፡10-26)  የአይሁድ አባቶች ዘመን (ዘፍ. 11፡27-50) ሀ) የታራ ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 11፡27-25፡1)  ለ) የእስማኤል ትውልድ (ዘፍ. 25፡12-18)  ሐ) የይስሐቅ ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 25፡19-35፡29) መ) የዔሳው ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 36፡1-37፡1)  ሠ) የያዕቆብ ትውልድ ታሪክ (ዘፍ. 37፡2-50፡26) ሙሴ ኦሪት ዘፍጥረትን በዚህ ዓይነት ቢያቀናብረውም ለማስታወስ ቀላል የሆነ ሌላ የቅንብር መንገድ አለ። የሚከተለውን አስተዋጽኦ እየደጋገምህ አጥና ወይም በቃልህ ያዝ፡- ከአይሁድ አባቶች በፊት የነበረው ዘመን (ዘፍ. 1-11)  ሀ. ፍጥረት (ዘፍ. 1-2)  ለ. የሰው ልጅ በኃጢአት መውደቅ (ዘፍ. 3-5)  ሐ. የጥፋት ውኃ በዓለም ላይ (ኖኅ) (ዘፍ. 6-9) መ. የባቢሎን ግንብና የሰው ዘር መለያየት (ዘፍ. 10-11)  የአይሁድ የእምነት አባቶች ዘመን (ዘፍ. 12-50) ሀ. አብርሃም (ዘፍ. 12-25)  ለ. ይስሐቅ (ዘፍ. 24-26) ሐ. ያዕቆብ (ዘፍ. 27-36)  መ. ዮሴፍ (ዘፍ. 37-50) ከዚህ በላይ ባለው አስተዋጽኦ ውስጥ ሁለት ነገሮችን ልብ በል፡- – በመጀመሪያ፥ ዘፍጥረት በሁለት ዓበይት ክፍሎች፥ ማለትም በዘፍጥረት 1-11 እንዲሁም በዘፍጥረት 12-50 እንደተከፈለ ልብ በል። የመጀመሪያው ክፍል የሚናገረው ስለ ጥንት ዘመን ሲሆን፥ ፍጥረታትን የመፍጠር ተግባር የተፈጸመው መቼ እንደሆነና ይህ ክፍለ ዘመን ምን ያህል ዓመታት እንደፈጀ ለማወቅ አንችልም። ዘፍ. 12-50 ደግሞ የሚናገረው ስለ አይሁድ ሕዝብ መመሥረትና ያንን ሕዝብ ስለ ጀመሩት አራቱ የእስራኤል አባቶች ታሪክ ነው። ሁለተኛ፥ እያንዳንዱ ክፍል በአራት ንዑሳን ክፍሎች መከፈሉን ልብ ሰል። ከዘፍ. 1-11 ያለው የመጀመሪያው ክፍል ፍጥረትን፥ ውድቀትን፥ የጥፋት ውኃንና የባቢሎንን ግንብ የሚያጠቃልሉ አራት ክፍሎች አሉት። ከዘፍ. 12-50 ባለው ክፍል ደግሞ ትኩረት የተሰጣቸው አራት ዋና ዋና ሰዎች አሉ። ይህንን የዘፍጥረትን አስተዋጽኦ ብትከተል በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኘውን ታሪክ ለማስታወስ ይረዳሃል። የኦሪት ዘፍጥረት ልዩ ባሕርያት በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ መጽሐፉን የበለጠ ለመረዳት ማዕከላዊ የሆኑና ሙሴ ያካተታቸው አንዳንድ ልዩ ነገሮች አሉ። ዘፍጥረት፥ እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር ባለው ግንኙነት ዓላማውን ወደ ፍጻሜ ብዙ ጊዜ ለማድረስ ከተለመደው ባሕላዊ ሁኔታና ተግባር ተቃራኒ በሆነ አቅጣጫ እንደሚጓዝ ያሳያል። ይህ በተለይ የታየው እግዚአብሔር ከበኩሩ (ከመጀመሪያው ልጅ) ይልቅ ሁለተኛውን በመምረጡ ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ እንዳሉት በርካታ ባሕሉች አይሁድ የመጀመሪያ ልጅ ልዩ እንደሆነ በማመን፥ ከአባቱ ንብረት የሚበዛውን ክፍል መውረስ እንዳለበት ይስማሙ ነበር። እግዚአብሔር ግን በዚህ ሰው ሠራሽ ባሕል ራሱን አልወሰነም። ለምሳሌ፡- በዘፍጥረት ውስጥ እግዚአብሔር ከቃየን ይልቅ ሴትን፥ ከያፌት ይልቅ ሴምን፥ ከእስማኤል ይልቅ ይስሐቅን፥ ከዔሳው ይልቅ ያዕቆብን፥ ከቀሩት ወንድሞቻቸው ይልቅ ይሁዳንና ዮሴፍን፥ ከምናሴ ይልቅ ኤፍሬምን ሲመርጥ እንመለከታለን። ይህ ሁሉ የሚያስተምረን እግዚአብሔር በእኛ ባሕላዊ ግንዛቤ መሠረት ብቻ ለመሥራት የሚወሰን አለመሆኑን ነው። ይልቁንም ከእኛ ጋር ባለው ግንኙነት ሉዓላዊ ነው። የተለያዩ ግለሰቦችን የሚመርጠውና በአንዳንዶቹ በኃይል የሚሠራው በሌሉቹ ደግሞ ያንኑ ያህል በኃይል የማይሠራው እግዚአብሔር ራሱ ነው። ይህም እግዚአብሔር በሕይወታችን ላይ ባለው ኃይልና የበላይ ተቆጣጣሪነት ከፍተኛ አድናቆትን እንድንሰጠው የሚያደርግ እንጂ በአእምሮአችን ውስጥ ቅንዓትን የሚፈጥር መሆን የለበትም።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች ሌሉች ክርስቲያኖች ባለጸጎች መሆናቸውን ወይም እግዚአብሔር ከእነርሱ ይልቅ በኃይል እየተጠቀመባቸው መሆኑን ሲገነዘቡ የሚቀኑት ለምንድን ነው? ለ) ሕይወታችንን ለእግዚአብሔር ዕቅድ አሳልፎ ስለመስጠት የሚያስተምረን ነገር ምንድን ነው? ሐ) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በጣም አስፈላጊው ነገር፥ እግዚአብሔር ለሰጠን ስጦታዎችና ችሉታዎች ወይም ሥራዎች ታማኝ መሆን ነው፥ ወይስ በሰዎች ላይ ታላቅ መሪ መሆን? መልስህን አብራራ። በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ ተምሳሌታዊ ትርጉም ያላቸው አንዳንድ ቁጥሮች ይገኛሉ። የሚከተሉትን ቁጥሮች ተመልከት፡-  ሀ) አሥር – በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ አሥር ዋና ዋና ክፍሎች አሉ፤ (አሥር ጊዜ «የ … ይህ ነው» ታሪኮች) እንዲሁም በዘፍጥረት 5 ና 11 «አሥር» ትውልዶችን የሚጠቅሱ ትንተናዎች እናገኛለን»። ለአይሁድ አሥር የምሉዕነት ተምሳሌት ነው። ለ) ሰባት – ሰባት የፍጥረታት ሥራ የተከናወኑባቸው ቀናት ከመኖራቸውም፥ በምዕራፍ 4 ውስጥ በሚገኘው የትውልዶች ታሪክ ውስጥ የሚገኙ ሰባት ስሞች፥ በጥፋት ውኃ ታሪክ ውስጥ የሚገኙ በርካታ ሰባት ቁጥሮች፣ ለአብርሃም የተገቡ ሰባት ቃል ኪዳኖች፥ በግብፅ ውስጥ የደረሱ ሰባት የጥጋብና ሰባት የራብ ዓመታት እናገኛለን፡፡ እንዲሁም 70 (7 ጊዜ 10) የኖኅና የያዕቆብ ዝርያዎች ናቸው። ሰባት ብዙ ጊዜ የፍጹምነት ምሳሌ ነው። ሐ) አሥራ ሁለት – የያዕቆብና የእስማኤል ነገዶች እያንዳንዳቸው አሥራ ሁለት ነገዶች ነበሩ (ዘፍ. 25፡16፤ 49፡28)።  መ) አርባ፡- በጥፋት ውኃ ታሪክ ውስጥ የተለያዩ የ40 ቁጥር ክፍፍሎች እናያለን (ዘፍ. 6-9)። በኋላም እስራኤላውያን 40 ዓመታት በምድረ በዳ እንደተንከራተቱ እናነባለን። አንድ ሰው ብሉይ ኪዳንን በሚያጠናበት ጊዜ እነዚህ ቁጥሮች ለአይሁድ የተለዩ እንደሆኑ ግልጽ እየሆነለት ይመጣል። ለምሳሌ 40 ቁጥር የፍርድና የፈተና ጊዜ ይመስላል (ለምሳሌ፡- ኢየሱስ በምድረ በዳ ለ40 ቀናት ተፈትኖአል)። ሰባት ማለት ደግሞ የተሟላ ወይም ፍጹም ማለት ነው፤ (ለምሳሌ፡- በዮሐንስ ራእይ መንፈስ ቅዱስ ሰባቱ የእግዚአብሔር መናፍስት ተብሎ ተጠርቷል)። በዮሐንስ ራእይ የመጨረሻ ምዕራፎች የሚገኙት በተለይም መንግሥተ ሰማያትን የሚገልጡት ሥዕላዊ መግለጫዎች ከኦሪት ዘፍጥረት የመጀመሪያ ሦስት ምዕራፎች ስለ ዔደን ገነት ከተነገሩ መግለጫዎች የተወሰዱ መሆናቸው ትኩረትን የሚስብ ነው። እነዚህ መጻሕፍት የተጻፉት በ1500 ዓመታት ልዩነት መካከል ቢሆንም ይህን የመሰለ ግንኙነት በመካከላቸው መታየቱ፥ እግዚአብሔር የመጽሐፍ ቅዱስ ሁሉ ጸሐፊ መሆኑን የሚያሳይ ነው።  የኦሪት ዘፍጥረት ዋና ዓላማ የመጽሐፍ ቅዱስን አጠቃላይ ዓላማ ብንመለከት፥ ኢየሱስ ክርስቶስን መግለጥ ነው ለማለት እንችላለን። እርሱ «የእግዚአብሔር ቃል» ነው ( ዮሐ. 1፡1-4፤ ዕብ. 1፡1-3)። «ኢየሱስ ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ተሰውሮአል፤ በአዲስ ኪዳን ግን ተገልጦአል» የሚል አንድ አባባል አለ። በሌላ አባባል የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በትንቢቶች አማካይነት የኢየሱስን መምጣት አሻግረው ተመለከቱ። እንዲሁም በሰዎች፥ በድርጊቶችና በነገሮች ሁሉ ውስጥ የመሢሑ መምጣት ሥዕላዊ መግለጫ ነበር። ስለሆነም ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ የኢየሱስ ክርስቶስን መገለጥ አጀማመር እናያለን። በዘፍጥረት ስለ ኢየሱስ የተነገሩ ትንቢቶችን አጀማመር እንመለከታለን። በአንዳንድ ታሪኮች ውስጥም የተደበቁ የኢየሱስ ተምሳሌቶች ወይም ሥዕላዊ መግለጫዎች አሉ። ብሉይ ኪዳንን ስናጠና እነዚህም ትንቢቶችና አምሳያዎች መፈለግ አለብን። ይህ ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ እስከ ዮሐንስ ራእይ የሚቀጥል «የድነት (ደኅንነት) መስመር» በመባል ይታወቃል። ነገር ግን ሙሴ ፔንታቱክን የጻፈበት ዋና ዓላማ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ያደረገውን «ቃል ኪዳን» ለመግለጥ ነበር። ፔንታቱክና መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት መሠረታዊ የሆነው አሳብ ይህ ቃል ኪዳን ነው፤ ስለዚህ የኦሪት ዘፍጥረት ማዕከላዊ እውነቶች የሚያተኩሩት ቃል ኪዳንን በሚመለከት አሳብ ላይ ነው። ዘፍጥረት 1-11 ከተለዩ ሕዝቦች ጋር ቃል ኪዳን ያስፈለገበትን ምክንያት ይናገራል። የሰው ልጅ በአጠቃላይ ፈጣሪውን ክዶ ኃጢአትን እንዴት እንደመረጠ ይናገራል። ዘፍ. 12-50 ደግሞ እግዚአብሔር ከአንድ ሰውና ከቤተሰቡ ጀምሮ አይሁድ ተብሎ የተጠራ አንድን የተለየ ሕዝብ እንዴት እንደመረጠ ይገልጻል። እግዚአብሔር ዓለምን ወደ ራሱ ለመመለስ የፈለገው በእነርሱ በኩል ነበር። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ያለው የቃል ኪዳን አሳብ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ወይም በአዲስ ኪዳን የሚታየው እንዴት ነው? ለ) የእስራኤል ሕዝብና የቤተ ክርስቲያን ዓላማ የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ሐ) እግዚአብሔር አብርሃምን በመረጠው ጊዜ የነበረውን ዓላማ ዛሬ ቤተ ክርስቲያንህ እንዴት እየፈጸመችው ነው? (ማብራሪያው የተወሰደው በ

የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ቅደም ተከተልና አስተዋጽኦ፣ ልዩ ባሕሪያት እና ዓላማ Read More »

የኦሪት ዘፍጥረት መግቢያ

የውይይት ጥያቄ፥ «ዘፍጥረት» የሚለውን ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ውስጥ ተመልከት። ስለ ጸሐፊው፥ ስለ ተጻፈበት ዓላማና ስለ መጽሐፉ አስተዋጽኦ ያገኘኸው ነገር ምንድን ነው? ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ ልናጠናቸውና ልንረዳቸው ከሚገቡን እጅግ ጠቃሚ መጻሕፍት አንዱ ዘፍጥረት ነው። ብዙ ክርስቲያኖች በዘፍጥረት ውስጥ የሚገኙትን ታሪኮች ቢያውቁም እንኳ አብዛኛዎቹን ጥልቅ ትምህርቶች ግን አያጠኗቸውም። የዚህ መጽሐፍ ዓላማ ዘፍጥረትን በጥልቀት ማጥናት ባይሆንም፥ በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኛቸውንና የተተኮረባቸውን ዋና ዋና የሥነ- መለኮት ትምህርቶች ለመመልከት እንሞክራለን።  የኦሪት ዘፍጥረት ስያሜ  ለኦሪት ዘፍጥረት የተሰጠው ስም የመጣው ከግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሆነ ቀደም ሲል አጥንተናል። ዘፍጥረት የሚለው ቃል በመጽሐፉ የመጀመሪያ ሁለት ምዕራፎች ላይ እግዚአብሔር ነገሮችን ሁሉ ስለ መፍጠሩ በሚናገረው መሠረተ አሳብ ላይ ያተኩራል። እንደግሪኩ ስያሜ መጽሐፉ የሚያተኩረው በተለያዩ ነገሮች «አጀማመር» ላይ ነው። የውይይት ጥያቄ፥ ከዚህ ቀደም ኦሪት ዘፍጥረትን በግል ካነበብከው በመነሣት አጀማመራቸው በመጽሐፉ የሆነ የተለያዩ ነገሮችን ዘርዝር። በዘፍጥረት ውስጥ የቀረውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍላችንን ለመረዳት በጣም ጠቃሚ የሆኑ የብዙ ነገሮችን አጀማመር እንመለከታለን። ለምሳሌ፡- የፍጥረታትን አጀማመር እንመለከታለን። እግዚአብሔር ፈጣሪ ስለሆነ እርሱ የፍጥረታት ሁሉ ባለቤትና ተቆጣጣሪ ነው። በዘፍጥረት ውስጥ የወንድና የሴትን፥ የጋብቻን፥ የኃጢአትን፥ ስለ ኃጢአት የሚቀርብ መሥዋዕት፥ የተለያዩ ከተሞችን፥ የነፍስ ግድያን፥ የሥልጣኔ፥ የነገድና የጎሣዎችን፥ የተለያዩ ቋንቋዎችን አጀማመር፥ ወዘተ እናያለን። አብዛኛዎቹም በኦሪት ዘፍጥረት በመጀመሪያዎቹ 11 ምዕራፎች ውስጥ ይገኛሉ። ከብሉይ ኪዳን ታሪክ አንጻር ስናየው ግን በጣም አስፈላጊ ክስተት የሆነው የእስራኤል ሕዝብ አጀማመር ነው። የኦሪት ዘፍጥረት አብዛኛው ክፍል (ምዕራፍ 12-50) ስለ እስራኤል ሕዝብ አጀማመር የሚናገር ነው። ይህም ሕዝብ እግዚአብሔር የመረጠው ነው።  የኦሪት ዘፍጥረት ጸሐፊ የውይይት ጥያቄ፡ሀ) የኦሪት ዘፍጥረት ጸሐፊ እንደሆነ በይበልጥ የሚገመተው ማን ነው? ለ) እንደ አንዳንድ ምሁራን አስተሳሰብ ዘፍጥረት የተጻፈው እንዴት ነው? ሐ) ሙሴ የሚለውን ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ተመልክተህ ስለ ሕይወቱ በአጭሩ ጻፍ። መ) ኦሪት ዘፍጥረትን ለመጻፍ ሙሴ የተለየ ብቃት ያገኘው እንዴት ነው? በዘመናት ሁሉ ሙሴ ዘፍጥረትን ጨምሮ የፔንታቱክ ጸሐፊ መሆኑ ይገመት እንደነበር ቀደም ሲል ተመልክተናል። ጸሐፊው ሙሴ እንደሆነ በዘፍጥረት ባይጠቀስም እንኳ የቀሩቱ የፔንታቱክ መጻሕፍት ግን ሙሴ እንደጻፈው ያሳያሉ። አምስቱ የሙሴ መጻሕፍት በሙሉ እንደ አንድ ክፍል ስለሚቆጠሩ፥ ዘፍጥረትንም የጻፈው ሙሴ መሆን አለበት። ሙሴ ዘፍጥረትን አልጻፈውም ብለን የምናምንበት አንዳችም ምክንያት የለም። ይልቁንም ሙሴ በዘፍጥረት ውስጥ የምናገኘውን ነገር ለመጻፍ በተለየ ሁኔታ ተዘጋጅቶ ነበር። ለአይሁድ በብሉይ ኪዳን ዘመን ከነበሩ እጅግ ታላላቅ ሰዎች አንዱ ሙሴ ነበር። ከግብፅ ባርነት አውጥቶ ወደ ተስፋይቱ ምድር የመራቸው ሙሴ ነበር። ለእስራኤል ሕዝብ ሕግን ለመስጠት እግዚአብሔር የተጠቀመበት ሰው ሙሴ ነበር። አይሁድ የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ዘወትር «የሙሴ ሕግ» ብለው የሚጠሩት ስለዚህ ነበር። ሙሴ ነቢይ፥ ካህን፥ ሕግ ሰጭ፥ ፈራጅ፥ አማላጅ፡ እረኛ፥ ተአምራት አድራጊና የአይሁድ ሕዝብ የፖለቲካ መሥራች ነበር። ሙሴ የተወለደው ሌዊ ከተባለው የእስራኤል ነገድ እግዚአብሔርን ከሚፈሩ ወላጆች ነበር። ነገር ግን የተወለደው እጅግ አስቸጋሪ በሆነ ጊዜ ነበር። የእስራኤል ሕዝብ በግብፃውያን ባርነት ሥር ወድቆ፥ ግብፃውያንም እስራኤላውያን የሆኑ ወንዶች ልጆች ሁሉ በሚወለዱበት ጊዜ እንዲገደሉ ሕግ ያወጡበት ጊዜ ነበር። ግብፃውያን ይህንን ያደረጉበት ምክንያት እስራኤላውያን በቁጥር እጅግ ብዙ ይሆኑና ከዚህ ቀደም ሐይክሶሳውያን እንዳደረጉት ሊገለብጡን ይሆናል ብለው ፈርተው ስለ ነበር ነው። በእምነታቸው ጽናት የሙሴ ወላጆች ሊደብቁት እስከሚችሉበት ጊዜ ድረስ አሳደጉት። ሊደብቁት ከማይችሉበት ጊዜ ላይ ሲደርሱ ግን እግዚአብሔር እንደሚታደገው በመተማመን በዓባይ ወንዝ ዳር አስቀመጡት። የግብፅ መሪ የነበረው የፈርዖን ሴት ልጅ ባገኘችው ጊዜ ወደ ቤቷ ወስዳ እንደ ግብፃዊ አሳደገችው። የሙሴ ሕይወት እያንዳንዳቸው 40 ዓመታት በሆኑ ሦስት ክፍሎች ሊከፈል ይችላል። 40 ዓመታት በግብፅ – በፈርዖን ቤት ውስጥ፡- በእነዚህ 40 ዓመታት ውስጥ ሙሴ በሁለት የተለያዩ ባሕሎች ትምህርት አደገ። በመጀመሪያ፥ በአይሁድ ሃይማኖትና ከአባቶች በተወረሰ ትምህርት አደገ። ይህ የሆነው ለጊዜውም ቢሆን ያሳድጉት ዘንድ ኃላፊነቱ በተሰጣቸው በእኅቱ ማርያምና በእናቱ ነበር (ዘጸ. 2፡7-10)። ሁለተኛ፥ ሙሴ እንደፈርዖን ልጅ ሆኖ የማደግ ዕድል በማግኘቱ በዚያ ዘመን ሊኖር የሚችለውን ትምህርት ሁሉ ቀስሞ ነበር (የሐዋ. 7:22 ተመልከት)። ግብፅ በዚያን ዘመን እጅግ የሠለጠነች አገር ስለነበረች፥ ሙሴ እጅግ የተማረ ሰው ነበር ማለት ነው። እስጢፋኖስ ሙሴ «በቃልና በሥራው ሁሉ የበረታ ሆነ» ይላል። ሙሴ ይህንን ሁሉ ትምህርት በመቅሰሙ፥እግዚአብሔር በኋላ ዘፍጥረትን ጨምሮ የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እንዲጽፍ ተጠቀመበት። አይሁዳውያን ከነበሩት ወላጆች ስለ ወገኖቹ እንደሰማ ጥርጥር የለውም። ወደ ኋላ ተመልሶ እስከ አዳምና ሔዋን፥ ኖኅ፥ በተለይም አብርሃም፥ ይስሐቅ፥ ያዕቆብና ዮሴፍ ያለውን የሕዝቡን አፈ ታሪኮችን ያውቅ ነበር። በግብፅ ታላላቅ ቤተ መጻሕፍት ስለአለፈው ጊዜ የሚናገሩ ታሪኮችን የማየት ዕድልም ገጥሞት ነበር። ይህ ታሪክ የዓለምን አፈጣጠር፥ በኖኅ ዘመን የነበረውን የጥፋት ውኃ፥ የዓለምን መከፋፈል ወዘተ የሚጨምር ነው። ሙሴ ዘፍጥረትን ለመጻፍ በጣም ብቁ ሰው ነበር። በእነዚህ 40 ዓመታት ሙሴ እስራኤላዊ እንጂ ግብፃዊ እንዳልሆነ አልዘነጋም ነበር። ካደገ በኋላ አንድ ውሳኔ ለማድረግ ተገደደ። ውሳኔውስ ዓለማዊ የሆነ ዕድል ባለበት በፈርዖን ቤት ለመቆየት? ወይስ እግዚአብሔር የተለዩ የቃል ኪዳን ሕዝቡ አድርጎ ከመረጣቸውና አሁን ባሮች ከሆኑት ሕዝብ ጋር ማበር ይሆን?  የውይይት ጥያቄ፥ ዕብ. 11፡24-26 አንብብ። ሀ) ሙሴ ያደረገው ምርጫ ምን ነበር? ለ) ዛሬ ይህንን ምርጫ ማድረግ ያለብን እንዴት ነው? ምሳሌ ስጥ። ሙሴ እስራኤልን ከግብፅ ባርነት ነፃ ለማውጣት የተመረጠ መሪ እንደነበር ተረድቶ ነበር (የሐዋ. 7፡25)። ነገር ግን የእግዚአብሔርን ጊዜ ከመጠበቅ ይልቅ በራሱ ኃይል ነፃ ሊያወጣቸው ሞከረ። ስለዚህ አንድን ሰው ከገደለ በኋላ የፈርዖንን ቤት ትቶ ከግብፅ መሸሽ ግድ ሆነበት። 40 ዓመታት በምድያም ምድረ በዳ፡- በሰው አመለካከት የሚቀጥሉት 40 ዓመታት የባከኑ ይመስላሉ። ሙሴ በጣም የተማረ ሰው ቢሆንም በግ ማገድ ጀመረ። በእግዚአብሔር አመለካከት ግን በሙሴ ሕይወት ይህ በጣም አስፈላጊ ጊዜ ነበር። ምድረ በዳውና በግ ማገዱ እግዚአብሔር ሙሴን የእስራኤል ሕዝብ መሪ ወይም እረኛ ለማድረግ የሚያስተምርበት ቦታና ሥራ ነበር። በምድረ በዳው እግዚአብሔር በትምህርቱና በችሎታው የነበረውን ትምክሕት በማስወገድ ሙሴን ትሑት አደረገው። ሙሴ ትሑት ከሆነና እግዚአብሔር በሕይወቱ እንዲሠራ በእርሱ ብቻ ከታመነ፥ ታላቅ ሥራን ይሠራ ዘንድ የእግዚአብሔር መገልገያ ለመሆን ተዘጋጅቷል ማለት ነው።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ሙሴን በኃይል ይገለገልበት ዘንድ ትሑት ሊያደርገው ያስፈለገበት ምክንያት ምንድን ነው ብለህ ታስባለህ? ለ) የእግዚአብሔርን ሕዝብ በምንመራበት ጊዜ በችሎታችንና በእውቀታችን ስለ መመካት ይህ ምን ያስተምረናል? ሐ) ከሙሴ ለ40 ዓመታት በምድረ በዳ መኖር ስለ ቤተ ክርስቲያን አመራር ምን ለመማር ትችላለህ? 40 ዓመታት የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከግብፅ ወደ ከነዓን መምራት፡- አንድ ቀን እግዚአብሔር ሙሴን በሚቃጠል ቁጥቋጦ ውስጥ ተገናኘውና ወደ ግብፅ ተመልሶ እስራኤላውያንን ከግብፅ ነፃ በማውጣት እንዲመራቸው ጠራው። ሙሴ ወደ ግብፅ ለመመለስ ቢፈራም፥ በመጨረሻ ከእግዚአብሔር ጋር ተስማማ። እግዚአብሔር ሙሴን በፈርዖን ፊት ስለ እርሱ ሆኖ ይናገር ዘንድ ተገለገለበት። ሙሴ ያደረገው በፈርዖን ቤተ መንግሥት በመሆኑ በፈርዖን ዘንድ እውቅናን ማትረፉ አያጠራጥርም። አሥር ታላላቅ ተአምራዊ መቅሠፍቶችን በግብፅ ላይ በማምጣት እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ነፃ አውጥቶ በሙሴ አማካይነት 40 ዓመታት በምድረ በዳ መራቸው። በእነዚህ 40 ዓመታት ውስጥ እግዚአብሔር ሙሴን ፊት ለፊት ተገናኘው። እግዚአብሔር ለሙሴ ከዘጸአት እስከ ዘዳግም ድረስ የተጻፈውን ሕግ ሰጠው። ሙሴን ኦሪት ዘፍጥረትን፥ ዘጸአትን፥ ዘሌዋውያንን፥ ዘኁልቁንና ዘዳግምን እንዲጽፍ እግዚአብሔር ተጠቅሞበታል። ይህ ሁሉ ቢሆንም እንኳ ሙሴ ለእግዚአብሔር ስላልታዘዘ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዳይገባ ታገደ (ዘኍ. 20፡1-13)። ሕዝቡን እስከ ከነዓን ድንበር ድረስ አደረሳቸው። የተስፋይቱን ምድር በተራራ ጫፍ ላይ ሆኖ ከተመለከታት በኋላ ሞተ። የውይይት ጥያቄ በቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሕይወት ውስጥ እግዚአብሔር እንዴት ኃጢአትን አክብዶ እንደሚያየው ይህ ምን ያስተምረናል? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ

የኦሪት ዘፍጥረት መግቢያ Read More »