ዘፍጥረት 37-50 የዮሴፍ ታሪክ
የዚህ የኦሪት ዘፍጥረት የመጨረሻ ክፍል ዓላማ የእስራኤል ሕዝብ የከነዓንን ምድር ይወርሱ ዘንድ ቃል የተገባላቸው ሆነው ሳሉ፥ እንዴት ወደ ግብፅ እንደወረዱ ማሳየት ነው። ለኦሪት ዘጸአትም በመግቢያነት የሚያገለግል ነው። ምክንያቱም ኦሪት ዘጸአት እስራኤላውያን በግብፅ 400 ዓመታት ከቆዩ በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመመለስ እንዴት እንደወጡ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው። ታሪኩ የተፈጸመው በሙሴ ዘመን ገደማ ስለሆነ፥ ከሌሎቹ የእስራኤል አባቶች ታሪክ ይልቅ የዮሴፍን ታሪክ በዝርዝር ይነግረናል። በተጨማሪ ኃጢአታቸው የሚያስከትለውን ችግር ጨምሮ እግዚአብሔር በሕዝቡ ሕይወት የሚመጣውን ነገር ሁሉ እየተቆጣጠረ እንዴት ያለማቋረጥ እንደመራቸው እንመለከታለን። የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍጥ. 37-50 አንብብ። ሀ) ዮሴፍ ያያቸውንና የተረጎማቸውን ልዩ ልዩ ሕልሞች ዘርዝር። እያንዳንዳቸው እንዴት ተፈጸሙ? ለ) ዮሴፍ በምሳሌነት ሊቀርብ የሚችል ታላቅ የእግዚአብሔር ሰው የሆነው እንዴት ነው? ሐ) በዮሴፍ ሕይወት ውስጥ የእግዚአብሔር ቁጥጥር የታየባቸውን መንገዶች ዘርዝር። መ) በስደት ውስጥ ይቅርታንና ትዕግሥትን ስለማሳየት ከዮሴፍ ሕይወት የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ከብዙ ዓመታት በፊት፥ እግዚአብሔር በሌላ ምድር መጻተኞች ሆነው እንደሚኖሩና ለ400 ዓመታት በባርነት እንደሚገዙ ለአብርሃም ተናግሮት ነበር (ዘፍጥ. 15፡13)። በዮሴፍ ታሪክ ይህ ትንቢት መፈጸም ጀመረ። እግዚአብሔር የገባውን ቃል ኪዳንና የሰጠውን ተስፋ እኛ በምንፈልገው ፍጥነት ባይፈጽምም፥ ለሰጠው ተስፋና ቃል ኪዳን ግን ሁልጊዜ ታማኝ ነው። ዮሴፍ ወደ ግብፅ የሄደበት ምክንያት (ዘፍጥ. 37):- ከዘፍጥረት ምዕራፍ 37 ጀምሮ የእግዚአብሔርን እጅ በሥራ ላይ እናያለን። እግዚአብሔር አንድ ዓይነት ትርጉም ያላቸውን ሁለት ሕልሞች ለዮሴፍ ሰጠው። በመጀመሪያ፥ የወንድሞቹ ነዶዎች ለእርሱ ሲሰግዱ ያያል። በሁለተኛው ሕልም ደግሞ ፀሐይ፥ ጨረቃና አሥራ አንዱ ከዋክብት ለእርሱ ሲሰግዱለት አየ። ይህ ሕልም በወንድሞቹ ላይ ገዥ እንደሚሆንና እነርሱም እንደሚሰግዱለት ማለትም እንደ መሪያቸው ተቆጥሮ እንደሚያከብሩት የተሰጠ ትንቢት ነበር። ይህም ትንቢት ከብዙ ዓመታት በኋላ ዮሴፍ የግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ ወንድሞቹ ምግብ ፍለጋ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ተፈጸመ። ትዕማር የይሁዳን ዘር አዳነች (ዘፍጥ. 38)፡- በዮሴፍ ታሪክ አጋማሽ ላይ በሌሉች ወንድሞቹ በተለይም በይሁዳ ሕይወት ኃጢአትና ክፋት መኖሩን የሚያሳይ አሳዛኝ ታሪክ እንመለከታለን። የይሁዳ ትልቁ ልጅ ዔር ትዕማር የምትባል ከነዓናዊት አገባ፤ ነገር ግን አንድም ልጅ ሳይወልድ ሞተ። በዚያ ዘመን በነበረው ወግ መሠረት ይሁዳ የሚቀጥለውን ልጁን አውናንን ከትዕማር ጋር ማጋባት ነበረበት። በባሕሉ መሠረት የሚወለደው የመጀመሪያ ልጅ የሟቹ ወንድም የዔር እንደሆነ ይቆጠር ነበር። የቀሩት ልጆች ደግሞ የአውናን ይሆኑ ነበር። የመጀመሪያው ልጅም የብኩርናን መብት ያገኝ ነበር። በሞተውም ልጅ ምትክ ከአያቱ ርስት ይወርስ ነበር። ይህ ማለት ይሁዳ ለበኩር ልጁ ያወርሰው የነበረው ነገር የመጀመሪያ ልጁ ከሞተ በኋላ የሚተላለፈው ለሁለተኛ ልጁ ሳይሆን ከትዕማር ለተወለደው ለልጅ ልጁ ይሆናል ማለት ነው። አውናን በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ስላደረገ እግዚአብሔር ቀሠፈው። ባሕሉን ለማክበርና ለወንድሙ ልጅ ለማሳደግ ያልፈለገ ይመስላል። ምናልባት ምንም ልጅ ሳይወልዱ በሞተው ወንድሙ ምትክ የብኩርናን መብት እንደሚወርስ ሳይገምት አልቀረም። አውናን ከሞተ በኋላ ይሁዳ በባሕሉ መሠረት ሦስተኛ ልጁን ለትዕማር ለመዳር ፈቃደኛ ሳይሆን ቀረ። ግዴታውን ለእርሷና ለመጀመሪያ ልጁ ሳይፈጽም ቀረ፤ ስለዚህ እርሷና ልጆችዋ የብኩርና መብት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ይሁዳን አታለለችው። ራሷን ሴተኛ አዳሪ አስመስላ በማቅረብ አማችዋ የሆነው ይሁዳ ከእርሱ ጋር እንዲተኛ አደረገችው። ከእርሱም ፋሬስና ዛራ ብላ የጠራቻቸውን መንታ ልጆች ወለደች። ይህን በማድረግዋ የይሁዳን ዘር ከመጥፋት አዳነች። የብኩርናን መብትም በቤተሰቧ በማስቀረት ልጇ ለይሁዳ የተሰጠውን የተስፋ ቃል ወራሽ እንዲሆን አደረገች። የሚያስደንቀው ነገር ንጉሡ ዳዊትና የዳዊት ልጅ ተብሎ የሚጠራው የኢየሱስ ክርስቶስ ዘር የመጣው ከትዕማር ልጅ ከፋሬስ መሆኑ ነው(ማቴ. 1፡3)። እግዚአብሔር ዮሴፍን በግብፅ ጠብቆ አከበረው (ዘፍጥ. 38-40)። ሀ. እግዚአብሔር ዮሴፍን በጲጥፋራ ቤት አከበረው፡- ዮሴፍ በዚህ ሰው ቤት ባሪያ ቢሆንም፥ ከእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝቦች አንዱ ነበር። እስራኤላውያንን ከራብ በማዳን የተሰጣቸው ቃል ኪዳን ከፍጻሜ እንዲደርስ ለማድረግ በእግዚአብሔር የተመረጠው ሰው ዮሴፍ ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር ዮሴፍን አከበረውና በግብፅ ውስጥ ባለውና መሪ በነበረው በጲጥፋራ ቤት አገልጋዮች ሁሉ አለቃ እንዲሆን አደረገ። ከጲጥፋራ ሚስት ጋር ዝሙት ፈጽሞ ሕይወቱ ሁሉ እንዲበላሽና እንዲጠፋ ለማድረግ ሰይጣን ሞከረ። ዮሴፍ ግን በዚህ መንገድ እግዚአብሔርንና ጲጥፋራን ላለመሳደብ ወስኖ የሰይጣንን ሙከራ ተቃወመ። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ለዮሴፍ ከጲጥፋራ ሚስት ጋር ዝሙት መፈጸም በጣም ቀላል የነበረው ለምንድን ነው? ለ) በዚህ ዘመን ብዙ ክርስቲያኖች በዚህ ኃጢአት የሚወድቁት ለምንድን ነው? ሐ) ይህንን ፈተና ስለማሸነፍ ከዮሴፍ ሕይወት የምንማረው ነገር ምንድን ነው? ለ) እግዚአብሔር ዮሴፍን በወኅኒ ቤት አከበረው፡- ምንም ጥፋት ያልነበረበት ንጹሕ የነበረው ዮሴፍ ወደ ወኅኒ ቤት ከገባ በኋላ በዚያ ለብዙ ዓመታት ቆየ። እግዚአብሔር በዚያም ቢሆን ሞገስን ሰጠውና በወኅኒ ቤቱ የእስረኞች አለቃ አደረገው። የወኅኒ ቤቱ የእስረኞች አለቃ ስለነበር እዚያ ታስረው ከነበሩት ከፈርዖን ጠጅ አሳላፊና የእንጀራ አበዛ ጋር ለመገናኘት ቻለ። እነዚህ ሁለት ሰዎች በግብፅ ቤተ መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች ነበሩ። ጠጅ አሳላፊው ንጉሡ ወይን ጠጅ ከመጠጣቱ በፊት የሚቀምስለት ሰው ነበር። ይህም ንጉሡን ማንም ሰው በመርዝ ሊገድለው እንዳይችል የተደረገ ዘዴ ነበር። ብዙውን ጊዜ የጠጅ አሳላፊው የንጉሡ ምሥጢረኛና የቅርብ ጓደኛ ነበር። የእንጀራ አበዛውም ንጉሡ ለሚበላቸው ነገሮች ሁሉ ኃላፊነት ስለ ነበረበት በጣም ከፍተኛ ስፍራ የነበረው ሰው ነው። እነዚህ ሁለት ሰዎች በእስር ቤት በነበሩ ጊዜ ዮሴፍ ሊተረጉምላቸው የቻለውን ሁለት ሕልሞች አዩ። የጠጅ አሳላፊው ሕልም ትርጓሜ ንጉሡን ያገለግልበት ወደነበረው ወደ ቀድሞ ሥፍራው መመለሱ ነበር። የእንጀራ አበዛው ሕልም ትርጓሜ ደግሞ የንጉሡን ምሥጢር ስላባከነ በስቅላት እንደሚገደል ነበር። እነዚህ ሕልሞች በኋላ የፈርዖንን ሕልም ለመተርጎም ወደ ቤተ መንግሥት እንዲጠራ ያደረጉት ስለነበሩ በጣም ጠቃሚ ሕልሞች ነበሩ። እግዚአብሔር ዮሴፍን በፈርዖን ፊት አከበረውና ጠቅላይ ሚኒስትር አደረገው (ዘፍጥ. 40-45)። ዮስፍ የፈርዖንን ሕልም ከተረጐመ በኋላ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ እንደደረሰ ይታወቃል። እግዚአብሔር በዮሴፍ በኩል ለፈርዖን ሰባት የጥጋብና ሰባት የረሃብ ዓመታት እንደሚመጡ በሕልሙ አሳወቀው። ዮሴፍ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደመሆኑ መጠን ለረሀቡ ጊዜ የሚሆነውን እህል በጥጋቡ ጊዜ አዘጋጀ። እግዚአብሔር ዮሴፍን ያን ወደ መሰለ ከፍተኛ የሥልጣን ቦታ ያመጣው ለምንድን ነው? ሀ) የግብፅን ሕዝብ ከራብ ለማዳን፥ ለ) የተመረጠውን የእስራኤልን ሕዝብ ከራብ ለማዳንና፥ ሐ) ለአብርሃም የገባውን የተስፋ ቃል ለመፈጸም ይችል ዘንድ የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ግብፅ ለማምጣት ነው። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ዕቅዱን ለመፈጸም ሲል ዮሴፍን በዚህ ዓይነት ካከበረው፥ ዛሬም ለእኛ እንዴት እንደሚሠራ ይህ ምን ያስተምረናል? ለ) እግዚአብሔር በዮሴፍ ሕይወት እንዳደረገው በአንተ ወይም በሌላው ክርስቲያን ሕይወት ያደረገውን ተመሳሳይ ነገር የሚገልጹ ምሳሌዎችን ዘርዝር። ዮሴፍ ለባርነት የሸጡትን ወንድሞቹን ለመፈተን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንዲያልፉ አደረጋቸው። እርሱን ለባርነት ስለሸጡበት ኃጢአት በእርግጥ መፀፀታቸውን ማየት ፈለገ። ይሁዳ ራሱን በብንያም ምትክ ለመስጠት የተዘጋጀ መሆኑንና ወንድሞቹም እንደዚያ የተቀጡበት ምክንያት እግዚአብሔር ራሱ ስለቀጣቸው እንደሆነ መቀበላቸውን ሲያይ ከኃጢአታቸው በእርግጥ መመለሳቸውን አወቀ። ከዚያ በኋላ ራሱን ገለጠላቸው። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዮሴፍ ወንድሞቹ እንደተለወጡና በእርግጥ ከኃጢአታቸው እንደተመለሱ ማወቅ ለምን አስፈለገው? ለ) ክርስቲያኖች በእውነት ከኃጢአታቸው መመለሳቸውን በምን እናውቃለን? የያዕቆብ ትውልድና ትንሹ የእስራኤል ጎሳ ወደ ግብፅ መውረድ (ዘፍጥ. 46-50)። ዮሴፍ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሆነ በኋላ ቤተሰቡ ወደ ግብፅ መጥተው እንዲኖሩ አደረገ። የእስራኤል ሕዝብ አባት የሆነው ያዕቆብም ወደ ግብፅ ወረደ። የዮሴፍን ልጆች ጨምሮ ወደ ግብፅ የመጡት እስራኤላውያን ጠቅላላ ቁጥር 70 ነበር። ከ400 ዓመታት በኋላ 70 የነበረው የእስራኤላውያን ቁጥር 2 ሚሊዮን ደርሶ ነበር። ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ለልጆቹ ለእያንዳንዳቸው በረከቱን አስተላለፈ። እነዚህ በረከቶች የትንቢት መልክ ሲኖራቸው የተሰጡትም በቀጥታ ከእግዚአብሔር እንደመጡ ተደርገው ነበር። የያዕቆብ በረከቶችና ትንቢት የእግዚአብሔር ቃል ነበሩ፤ እግዚአብሔርም ፈጸማቸው። ሀ) ያዕቆብ የዮሴፍን ሁለት ልጆች ኤፍሬምና ምናሴን ባረካቸው (ዘፍጥ. 48)። ይህንን በማድረግ ያዕቆብ የበኩር ልጅን መብት ለዮሴፍና ለልጆቹ ሰጠ። ደግሞም የብኩርናን መብት ከዮሴፍ ልጆች ለታናሹ ለኤፍሬም ሰጠ።
ዘፍጥረት 37-50 የዮሴፍ ታሪክ Read More »