የሕይወት እንጀራ

ወደ ዕብራውያን

ኢየሱስ ሊቀ ካህናት የመሆን ብቃት አለው (ዕብ. 4፡14–5፡10)

ማሞ ከልጅነቱ ጀምሮ የካቶሊክ እምነት ተከታይ ነበር። ከልጅነቱ ጀምሮ ኃጢአት በሚሠራበት ጊዜ ወደ ቄስ እንዲሄድ የሚያስረዳ ትምህርት ተከታትሎአል። ወላጆቹ፥ «ከቄሱ ዘንድ ሂድና የሠራኸውን ኃጢአት ተናዘዝ። እርሱም ይቅርታ ያደርግልሃል። ካልሆነ እግዚአብሔር በኃጢአትህ ይቀጣሃል» ሲሉ ያስረዱት ነበር። የሚሞቱበት ጊዜ በሚቃረብበት ወቅት ደግሞ ቄስ እንዲጠራና ጸበል እረጭቶ ኃጢአቶችን ሁሉ ይቅር እንዲያስብል ተነግሮት ነበር። ይህም ወደ መንግሥተ ሰማይ እንዲገባ ይረዳዋል ተብሎ የታሰበ ነበር። ሚሚ የወንጌል አማኞች ቤተ ክርስቲያን አባል ነች። አንድ ሰው ክርስቲያን ለመሆን ከፈለገ፥ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥቶ ማመን እንዳለበት ተምራለች። በዚህ ጊዜ ኅብረተሰቡን ወደ ክርስቶስ መምራት የሽማግሌዎች ኃላፊነት እንደሆነ ታውቃለች። ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ደግሞ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ ማምጣት የወንጌላዊው ሥራ እንደሆነ ታስባለች። የውይይት ጥያቄ፡– እንደ ካህን ወይም የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌ ያሉ ሰዎች በእግዚአብሔርና በምእመናን መካከል የአማላጅነትን ተግባር ሲያከናውኑ ያየህበትን ሁኔታ ግለጽ። ለ) ይህ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረው እውነት ይመስልሃል? ለምን? በአብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በእግዚአብሔርና በምእመናን መካከል የሚቆሙ የተወሰኑ መሪዎችን የማስነሣት ዝንባሌ ያለ ይመስላል። አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት እነዚህን ሰዎች ካህናት ወይም ቄሶች ይሏቸዋል። በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት፥ ሽማግሌዎች ወይም ወንጌላውያን የካህናትን ሚና ይጫወታሉ። ተራ የቤተ ክርስቲያን ምእመናን ግን ይህ በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል የተቀመጠ ግርዶሽ እንደሆነ ያስባሉ። ይቅርታ ለማግኘት ወይም ድነትን (ደኅንነትን) ለመቀበል እነዚሁኑ የሠለጠኑ ሰዎች ማማከር ያስፈልጋቸዋል። ነገር ግን በአዲስ ኪዳን ውስጥ ከምንመለከታቸው ታላላቅ እውነቶች አንዱ መንፈስ ቅዱስ በአማኞች ሁሉ ልብ ውስጥ እንደሚያድርና እያንዳንዱ አማኝ ካህን እንደሆነ ነው። እያንዳንዱ አማኝ በቀጥታ ወደ እግዚአብሔር ቀርቦ ችግሮቹን ሊያዋየው ይችላል፤ እንዲሁም እያንዳንዱ አማኝ ስለሌላው የማማለድ፥ በቃሉ መምከር እንዲሁ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ የመምራት መብት አለው (1ኛ ጴጥሮስ 2፡5፥ 9 አንብብ)። አማኞች ለይቅርታና ለእገዛ ሊመጡ የሚገባቸው ወደ አንድ ሊቀ ካህናት ብቻ ነው። እርሱም ታላቁ ሊቀ ካህናችን የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። አይሁዶች እግዚአብሔር ሊቀ ካህናት የተባለ አገልጋይ በእነርሱና በእግዚአብሔር መካከል እንደ ተሾመ በማመን ነበር የኖሩት። አምልኮ የሚካሄደው በሊቀ ካህናቱ በኩል ነበር። ይቅርታ የሚገኘውና መሥዋዕቶች የሚቀርቡት በካህናቱ በኩል ነበር። ሕዝቡ መሥዋዕቱን ይዞ ወደ ካህናት ወይም ሊቀ ካህናት ይመጣል። እነዚህም አገልጋዮች መሥዋዕቶቹን ለእግዚአብሔር ካቀረቡ በኋላ ሕዝቡ ይቅርታ እንዳገኙ ይናገራሉ። ምናልባትም የአይሁድ ክርስቲያኖች በቀድሞው አምልኮአቸው (ይሁዲነት) ሊቀ ካህናቱ የሚሰጣቸውን ይህንን ማረጋገጫ ከአዲሱ የክርስትና እምነታቸው አላገኙም ይሆናል። ወይም ደግሞ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ሊቀ ካህናቱ ቁልፍ ሚና የሚጫወትበት ጥንታዊ የአምልኮ ሥርዓት በክርስቶስ ስለነበራቸው እምነት አማራጭ ሊሆን እንደሚችል አስበው ይሆናል። ነገር ግን የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ክርስቶስ ከሊቀ ካህናቱ ሥልጣን እንደሚበልጥ ያሳያል። ክርስቶስ ከአሮን ወይም ካህናትና ሊቀ ካህናት ሆነው ካገለገሉት የአሮን ዘሮች ሁሉ በላይ ነው። ስለሆነም ከእንግዲህ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የሚቆም ሊቀ ካህናት አያስፈልግም። እንዲህ ዓይነቱን ሊቀ ካህናት መጠቀሙ እግዚአብሔር ክርስቶስ ብቻ ሊቀ ካህናችን እንዲሆን ካቀደበት ሁኔታ ጋር ይቃረናል። በክርስቶስ በኩል ሁላችንም ነፃና ቀጥተኛ የመግቢያ በር አለን። ጥንታዊ የአይሁዳውያን አምልኮ በአራት ዐበይት ነገሮች ላይ የተመሠረተ ነበር። በመጀመሪያ፣ ካህናት የሚባሉ የአምልኮ መሪዎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህም በዋናነት ጎልቶ የሚታየው ሊቀ ካህናቱ ነው። ሁለተኛ፥ የአምልኮ ቦታ፥ ማለትም የመገናኛ ድንኳንና በኋላም ቤተ መቅደሱ። ሦስተኛ፥ እንስሳት የሚሠዉበት የአምልኮ ሥርዓት፤ አራተኛ፥ በብሉይ ኪዳን የነበረ የአምልኮ አስተዋጽኦ ነበር። በሚቀጥሉት ስድስት ምዕራፎች ውስጥ ክርስቶስ እነዚህን ሁሉ ዓላማዎች ከብሉይ ኪዳን በላቀ መንገድ እንዴት ከፍጻሜ እንደሚያደርስ ጸሐፊው ያብራራል። ጸሐፊው ክርስቶስ ከአሮን የዘር ሐረግ ከሚወለዱ አይሁዳውያን ሊቀ ካህናት እንዴት እንደሚበልጥ ከመግለጹ በፊት፥ በዕብራውያን 4፡14-16 ውስጥ የትምህርቱን ማጠቃለያ ይሰጠናል። ይህም ማጠቃለያ ክርስቶስ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓት ፍጻሜ እና በይሁዲነት ውስጥ ከሚገኝ ከማንኛውም ነገር የላቀ መሆኑን የሚያሳይ ነው። ቀደም ሲል ጸሐፊው አምላክ የሆነው ኢየሱስ የሰውን ሥጋ ለብሶ በሰዎች መካከል ለመኖር በመቻሉ ሊቀ ካህናችን የመሆን ብቃት እንዳለው ገልጾአል። በዕብራውያን 4፡14-16፤ ጸሐፊው ሊቀ ካህናችን ስለሆነው ስለ ክርስቶስ ሦስት ቁልፍ ነገሮችን ይነግረናል፡ ሀ) ጸሐፊው ክርስቶስን «ትልቅ» ሊቀ ካህናት ይለዋል። ይህም ከአሮን ወይም ከማንኛውም ሊቀ ካህናት የሚበልጥ መሆኑን ያሳያል። ጸሐፊው ቀደም ሲል ክርስቶስ አምላክ መሆኑን ገልጾአል። በመሆኑም፥ ክርስቶስ እንደ አሮን ካለ ከማንኛውም ሊቀ ካህናት የበለጠ ነው። ለ) ኢየሱስ በተሻለ ስፍራ (በሰማይ) ያገለግላል። ክርስቶስ በሰማይ ያለችው ቤተ መቅደስ ግልባጭ በሆነችው ምድራዊ ቤተ መቅደስ ውስጥ አያገለግልም፡፡ ስለዚህ ጉዳይ በዕብራውያን ምዕራፍ 9 ውስጥ በስፋት እንመለከታለን። ሐ) ኢየሱስ የሚራራ ሊቀ ካህናት ነው። ምንም እንኳን ኢየሱስ እምላክ ቢሆንም፥ እርሱ ፍጹም ሰውም ነው። ሰው እንደ መሆኑ መጠን፥ ዛሬ የሚያስቸግሩንን ነገሮች ሁሉ በሕይወት ዘመኑ ተጋፍጦ አይቷል። በየቀኑ ኃጢአት ለመሥራት እንደምንፈተን ሁሉ እርሱም ግላዊ ክብርን ለመሻት፥ የእግዚአብሔርን መንገድ ላለመታዘዝ፣ ከስደትና ከሞት ለመሸሽ የተፈተነባቸው ጊዜያት ነበሩ። ስለሆነም ሥጋ ለባሾች ለሆንን ለእኛ ሊራራልንና ሊረዳን ይችላል። በእኛና በክርስቶስ ሰብአዊነት መካከል ያለው ልዩነት አንድ ብቻ ነው። ይኸውም እኛ ኃጢአተኞች ስንሆን፥ እርሱ ኃጢአት ሠርቶ የማያውቅ መሆኑ ነው። ይህ እውነት ከእኛም ምላሽ ይጠብቃል። ጸሐፊው ከእኛ የሚጠበቁትን ሁለት ምላሾች ይገልጻል፡- ሀ) «ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ!» ስደትን መፍራት ወይም የዓለም ነገሮች ከክርስቶስ ጋር ያለንን ጥብቅ እምነትና የቅርብ ግንኙነት እንዲሸረሽሩ መፍቀድ አይኖርብንም። ለ) ሊቀ ካህናችን በችግሮቻችን እንዲረዳን መጠየቅ አለብን። እምነታችንን ለመካድ ወይም በኃጢአት ለመውደቅ በምንፈተንበት ጊዜ፥ ያለንበትን ሁኔታ ሊረዳ ወደሚችለው አምላክ በጸሎት መቅረብ ይኖርብናል። እርሱም ይረዳናል። በኃጢአት ለመውደቅ በምንፈተንበት ጊዜ፥ ክርስቶስ ችግራችንን በመረዳት ፈተናችንን እንድናሸንፍ ሊረዳን ቃል ገብቷል። ብቸኝነት ሲሰማን፥ በአገልግሎታችን ተስፋ ስንቆርጥ ወይም ምንም ዓይነት ችግር ሲደርስብን፥ እንደምንረዳ እናውቃለን። ምክንያቱም እንደ ሰው ያለንበትን ችግር የሚረዳና እንደ አምላክ ደግሞ ከችግሮቻችን ሁሉ የሚልቅ ሊቀ ካህናት አለንና። እኛ ወደ እግዚአብሔር በምንቀርብበት አመለካከትና አይሁዶች ወደ እግዚአብሔር በሚቀርቡበት አመለካከት መካከል ትልቅ ልዩነት አለ። እግዚአብሔር ወደ ሲና ተራራ በቀረበ ጊዜ እጅግ ከመፍራታቸው የተነሣ እግዚአብሔር ከሙሴ ጋር ብቻ እንዲገናኝ ጠየቁት። አሁን ግን፥ ሙሉ ለሙሉ የኃጢአታችንን ይቅርታ ስላገኘን፥ በድፍረት ወደ እግዚአብሔር ልንቀርብ እንችላለን። ድፍረታችን የመነጨው ከራሳችን ላይሆን፥ ክርስቶስ በእኛ ምትክ ካቀረበው መሥዋዕት ነው። በልበ ሙሉነት ልንቀርብ የምንችልበት ምክንያት ደግሞ በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው አምላክ ምን ዓይነት እንደሆነና በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ምን እንዳደረገልን ስለምናውቅ ነው። ዙፋኑ በጸጋና በምሕረት የተሞላ ነው። ምክንያቱም እግዚአብሔር ይህንን ይመስላል። ልጆቹ ስለሆንን ይወደናል። ይህ ፍቅር ፍርሃታችንን አውጥቶ ይጥለዋል (1ኛ ዮሐ 4፡16-18)። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የእግዚአብሔርን እርዳታ በፈለግህ ጊዜ የተጋፈጥካቸውን ችግሮች ዘርዝር። ለ) ክርስቶስ አምላክም ሰውም፥ መለኮታዊ– ሰብአዊ ሊቀ ካህናችን መሆኑ እነዚህን ችግሮች በተጋፈጥክ ጊዜ ማበረታቻ የሆነህ እንዴት ነው? ሐ) ሊቀ ካህናትህ በችግር ጊዜህ እንዴት እንደረዳህ የሚያሳዩትን ምሳሌዎች ዘርዝር። አሁን ለእርዳታው እርሱን ለማመስገን ጊዜ ውሰድ። አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ክርስቶስ ሊቀ ካህናት ነው በሚለው ትምህርት ግር እንደ ተሰኙ ጥርጥር የለውም። በሌሎች የአዲስ ኪዳን ክፍሎች እንዲህ ዓይነት ትምህርት አይገኝም። ክርስቶስ እንዴት ሊቀ ካህናት ሊሆን ይችላል? «እግዚአብሔር ሊቀ ካህናትን የሚመርጠው ከአሮን የዘር ሐረግ አልነበረምን?» ሲሉ መጠየቃቸው የማይቀር ነው። ክርስቶስ የይሁዳ ነገድ በመሆኑ፥ ሊቀ ካህናት የመሆን ብቃትን ከየት አገኘው? የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ የሊቀ ካህናትን አገልግሎት፥ ሊቀ ካህናት እንዴት እንደሚመረጡ፥ እንዲሁም የክርስቶስ የክህነት ሐረግ ከየት እንደሚመነጭ በመመርመር እነዚህን ጥያቄዎች ይመልሳል። ሀ) የሊቀ ካህንነት መመዘኛዎች ሰው መሆን ያስፈልገዋል። «ከሰው ተመርጦ።» ከሊቀ ካህንነት ዐበይት መመዘኛዎች አንዱ የሚወክላቸውን ሰዎች መምሰሉ ነበር። ሰው እንደ መሆኑ መጠን፥ ሊቀ ካህናቱ የሰው ልጆች የሚጋፈጧቸውን ችግሮች ይረዳል። ኃጢአተኝነታቸውን፥ ነገሮችን በተሳሳተ መንገድ መገንዘባቸውን፥ ድካማቸውን ሁሉ ይረዳል። ሊቀ ካህናቱ እንዲህ ዓይነቱን ደካማ ግለሰቦች ወደ እግዚአብሔር ያቀርባቸዋል። በመሆኑም፥ ለሰዎች ሊቀ ካህናት ለመሆን ክርስቶስ ሰው መሆን ያስፈልገው ነበር።

ኢየሱስ ሊቀ ካህናት የመሆን ብቃት አለው (ዕብ. 4፡14–5፡10) Read More »

ስለ አለማመን የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (ዕብ. 3፡7-4፡13)

ብዙውን ጊዜ ስላለፈው ዘመን ታላቅነት ለማውራት እንወዳለን። ቤተ ክርስቲያናችን እንዴት እንደ ተመሠረተችና እንዳደገች፥ እግዚአብሔር በመካከላችን የሠራቸው ተአምራት፥ ወዘተ. ተናግረን አንዘልቅም። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ አይሁዶች የሙሴን ዘመን ታሪኮች ቀይ ባህርን ስላቋረጡባቸው ተአምራታዊ ሁኔታዎች ያስታውሱ ነበር። መናውን፥ ከዓለት ውስጥ የፈለቀውን ውኃ፥ ድርጭቱን እግዚአብሔር ለሕዝቡ አስደናቂ ነገር እንደሠራበት ዘመን አድርገው ይቆጥሩ ነበር። የአይሁዶችን ታላቅ ሕዝብነት ለመግለጽ ኃላፊ ታሪኮች ይጠቅሱ ነበር። ይሁንና የታሪኩን ሌላኛ ጎን ዘንግተው ነበር። ይኸውም የአይሁድን ሕዝብ ዐመፅና እግዚአብሔርም በእርሱ ላይ የነበራቸውን እምነት በማጣታቸው ምክንያት ያመጣባቸው ፍርድ እንዳልተፈጸመ ታሪክ ማለፋቸው ነበር። የዕብራውያን ጸሐፊ የተቀረውን የሙሴን ታሪክና በአባቶቻቸው ላይ የደረሰውን ሁኔታ ሊያስታውሳቸው ፈለገ። እግዚአብሔር በሠራላቸው ተአምራት ላይ ከማተኮር ይልቅ፣ ጸሐፊው በእግዚአብሔር ላይ እምነታቸውን ጥለው ቢሆን ኖሮ ምን ሊከሰት እንደሚችል ይገልጽላቸዋል። በዚህ በሁለተኛው የማስጠንቀቂያ ምንባብ ጸሐፊው ወደ ከነዓን በመግባቱ «እረፍት» ላይ አጽንኦት ይሰጣል። ጸሐፊው ወደ ከነዓን የመግባቱን እረፍት ድነት (ደኅንነትን) ከማግኘትና ወደ መንግሥተ ሰማይ ከመግባቱ እረፍት ጋር ያነጻጽራል። ምሁራን ይህ እረፍት የሚያመለክተው አማኞች በምድር ላይ ያገኙትን በረከት ስለመሆኑ ይከራከራሉ። ምናልባትም ይህ እረፍት በክርስቶስ የሚገኘውን የድነት (ደኅንነት) እረፍት (ከነዓንን ሳይሆን) በመንግሥተ ሰማይ የምናገኘውን ክብር አጣምሮ የያዘ ሳይሆን አይቀርም። በብሉይ ኪዳን፥ አይሁዶች ከሙሴ መሪነት ከግብጽ እስከ ከነዓን የተጓዙበት መንገድ ጥቂት ሳምንታትን ብቻ የሚፈጅ ነበር። ነገር ግን ለአይሁዳውያኑ አርባ ዓመታት ፈጀባቸው። ካለማመናቸው የተነሣ፥ በምድረ በዳ ውስጥ የእግዚአብሔርን አስደናቂ ተአምራት የተመለከቱት ከሃያ ዓመት እድሜ በላይ የሆኑ አይሁዶች (ከኢያሱና ካሌብ በስተቀር) ወደ ከነዓን ምድር እረፍት ሳይገቡ ሞተዋል። በኢያሱ መሪነት ጊዜም አይሁዶች ወደ ከነዓን ሊገቡና ከአገሪቱ የተወሰነውን ክፍል ሊይዙ ቢችሉም፥ እግዚአብሔር ሊሰጣቸው የፈለገውን እረፍት አላገኙም ነበር። ባለማቋረጥ ከጠላቶቻቸው ጋር ጦርነት ይገጥሙ ነበር። በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ከእግዚአብሔር ጋር አይጓዙም ነበር። ከዚህም የተነሣ በኋላ ከዚህች አገር በምርኮኛነት ተወስደዋል። አይሁዶች ከቶውንም እግዚአብሔር ሊሰጣቸው የፈለገውን መንፈሳዊና ሥጋዊ እረፍት አላገኙም። ለዚህም ምክንያቱ በእምነታቸው ሊጸኑና ለእግዚአብሔር ታማኞች ሆነው ሊኖሩ አለመቻላቸው ነው። ይህ እግዚአብሔር ለአይሁዶች ተስፋ የገባው እረፍት ገና ያልተፈጸመና ወደፊት የሚመጣ መሆኑን በመዝሙር 95፡7-11 ውስጥ ተገልጾአል። የኢያሱ ዘመን ካለፈ ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ የተጻፈው ይኸው መዝሙር፥ የእግዚአብሔር ሕዝብ እረፍቱን ለማግኘት በእግዚአብሔር ታማኝነት ሊጸና እንደሚገባ ያሳስባል። የአይሁድ ክርስቲያኖች፥ እንዲሁም ዛሬ በሕይወት ያለን ሁላችንም እግዚአብሔር ለእኛ ወዳዘጋጀው ወደዚሁ መንፈሳዊ የድነት (ደኅንነት) እረፍትና መንግሥተ ሰማይ እንድንገባ ተጠይቀናል። ነገር ግን ወደዚሁ እረፍት ለመግባት እንደ ቀድሞዎቹ አይሁዶች መሆን የለብንም። ልክ እንደ እነርሱ እግዚአብሔር እረፍቱን እንዳዘጋጀልን የተስፋ ቃል ሰጥቶናል። እንደ እነርሱ ወንጌሉን ሰምተናል፤ ልክ እንደ እነርሱ፥ የእግዚአብሔርን ተአምራት አይተናል። እረፍቱን ማግኘታችን ወይም አለማግኘታችን የሚወሰነው በእግዚአብሔር ላይ ባለን እምነትና ለእርሱ ታማኞች በመሆናችን ነው። ካላመንን ግን ዛሬ ምንም ያህል በረከቶች ብናገኝም፥ የኋላ ኋላ በአለማመናችን የተነሣ የእግዚአብሔርን ፍርድ እንቀበላለን። ስለሆነም፥ «እንደዚያ አለመታዘዝ ምሳሌ ማንም እንዳይወድቅ ወደዚያ እረፍት ለመግባት እንትጋ»። በመጀመሪያ፥ መንፈሳዊ እረፍታችንን ልንጀምር የምንችለው እንደ ይሁዲነት ባለ ታሪካዊ ሃይማኖት ወይም የወላጆቻችንን ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ እምነት በመከተል ሳይሆን፥ በክርስቶስ በማመን መሆኑን ሊታወስ ይገባል። ከክርስቶስ ፊታችንን በምንመልስበት ጊዜ ወደ እረፍቱ ለመግባት አልፈለግንም ማለት ነው። ሁለተኛ፥ እግዚአብሔርን ሆን ብለን ሳንታዘዝ ስንቀርና በክርስቶስ ላይ የነበረንን እምነት ስንክድ፥ ይህ የዘላለማዊውን የመንግሥተ ሰማይ እረፍታችንን ከአደጋ ላይ ይጥላል። እግዚአብሔር ለአሁንና ለወደፊት የገባልንን መንፈሳዊና ዘላለማዊ እረፍት እናገኝ ዘንድ ለእግዚአብሔር ታማኝነት ጸንተን ስደትን ልንጋፈጥ ይገባል። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖች ነን የሚሉ ሰዎች ወደ ዓለም ወይም ወደ ቀድሞው ሃይማኖታቸው በሚመለሱበት ጊዜ፥ እግዚእብሔር ለእነርሱ ያዘጋጀውን እረፍት የሚገፉት እንዴት ነው? ለ) የመንግሥተ ሰማያትን ዘላለማዊ እረፍት በተመለከተ፥ እንዲህ ዓይነቱ ውሳኔ የሚያስከትለው ዘለቄታዊ ውጤት ምንድን ነው? ጸሐፊው ሁለተኛ ማስጠንቀቂያውን ወደ እግዚአብሔር ቃል በማመልከት ይፈጽማል። ሁላችንም ከምንጋፈጣቸው እጅግ አደገኛ ነገሮች መካከል ከእምነታችንና ከታዛዥነታችን መውደቅ ይገኙባቸዋል። መውደቅ በምንጀምርበት ጊዜ፥ ብዙውን ጊዜ በልባችን ውስጥ ምን እየተፈጸመ እንዳለ መመልከቱ አዳጋች ነው። አእምሮአችን ወደ ተሳሳተ ትምህርት ወይም አስተሳሰብ እንዴት እየገሰገሰ እንዳለ አንገነዘብም። ፍላጎታችን እግዚአብሔር ወደማይከብርባቸው ነገሮች እየተሯሯጠ መሆኑን አንመለከትም። በኃጢአት በምንወድቅበት ጊዜ እንኳን ብዙውን ጊዜ አእምሮአችን ለፈጸምነው ጥፋት ማመኻኛ ለማግኘት ይሞክራል። ለመሆኑ ለዚህ ዓይነቱ ችግሮች መፍትሔው ምንድን ነው? የራሳችንን ልብ እንድንመለከት የሚረዳን ምን ይሆን? የዚህ መልእክት ጸሐፊ መፍትሔው የእግዚአብሔር ቃል ብቻ መሆኑን ይጠቁማል። በሆስፒታል ውስጥ የበሽተኛውን ሰውነት ቀዶ ከውስጡ የተበላሸውን ነገር እንደሚያይና እንደሚያስወግድ ሐኪም የእግዚአብሔር ቃልም ከስለታም ሰይፍ በበለጠ ሁኔታ ወደ ሰው ልብ ይዘልቃል። የእግዚአብሔር ቃል እጅግ ጠልቆ ወደ ነፍሳችን ውስጥ ይዘልቃል። ይህም ብዙውን ጊዜ ሌሎችና ከራሳችንም የተደበቀ ስፍራ ነው፡፡ በዚያም የእግዚአብሔር ቃል የልብን አሳብና ፍላጎት ይመረምራል። ይህ አዎንታዊም አሉታዊም ውጤት አለው። በአዎንታዊ መልኩ፥ የእግዚአብሔር ቃል የተሳሳተ አሳብ መጠንሰስ የጀመርንበትን ስፍራ ያሳየናል። የተሳሳተ ተግባር የሚከተለው ከዚሁ አሳብ ነውና። ይህ ደግሞ የምንለወጥበትን፥ ንስሐ የምንገባባትን፥ ወደ እግዚአብሔር የምንመለስበትንና ወደ እረፍት ካለመግባቱ ፍርድ የምናመልጥበትን መንገድ ያመቻቻል። በአሉታዊ ጎኑ፥ ከእግዚአብሔር ምንም ነገር ልንደብቅ እንደማንችል ያሳያል። መንፈሳዊ ነን ብለን ሰዎችን ልናሞኝ ብንችልም፥ እግዚአብሔርን ግን ልናታልለው እንችልም። እርሱ በተደበቀው ማንነታችን፥ በነፍሳችንና በአእምሮአችን ያለውን ሁሉ ያያል። በሚያየውም መሠረት፥ ተጠያቂዎች አድርጎ ይፈርድብናል። ይህም በአመዛኙ በውጫዊ ማንነታችን ውስጥ ከሚታየው የበለጠ ነው። ከዛ ትንሿን አለመታዘዝ ወይም ሰዎችን የምትጎዳ የማትመስለውን አነስተኛ ኃጢአት ያያል። ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል የማይጠሙ በሚመስሉበት ዘመን ውስጥ እንኖራለን፤ አስደናቂ ነገሮችን ለማየት እንናፍቃለን፤ እንደ በልሣን መናገር፥ ፈውስ እና እነዚህን በመሳሰሉ ነገሮች የሚናገሩትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ብቻ እናነባለን፤ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ቁጣ ለማምለጥ፥ እንደ ግለሰቦች እና ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር እንድንገባ ወደሚፈልገው እረፍት ለመግባት ከፈለግን፥ ሰይፉን ከሕይወታችንና ከአብያተ ክርስቲያኖቻችን ማዛመድ ይኖርብናል። እግዚአብሔር በልባችን ውስጥ የተደበቀውን እንዲገልጥና እያጠፋን ያለውን በሽታ እንዲያስወግድ መፍቀድ አለብን። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በብዙ ክርስቲያኖች እና አብያተ ክርስቲያናት ልቦች ውስጥ የተሰወሩትን አንዳንድ በሽታዎች ዘርዝር። ለ) እነዚህን ነገሮች ቆፍሮ ለማውጣትና ሰዎችን ለመለወጥ ብቃት ያለው የእግዚአብሔር ቃል ብቻ የሆነበትን ሁኔታ ግለጽ። ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ ይህ የእግዚአብሔር ሰይፍ ከሰዎች ሕይወት ኃጢአትን እንዲያስወግድ በተሻለ ሁኔታ የምትጠቀምበት እንዴት ነው ነው? መ) መንፈስ ቅዱስ ሰይፍ ውስጣዊ ሁኔታን ለራስህ እንዲያሳይህ በግል ሕይወትህ ምን እያደረግክ ነው? ሠ) እግዚአብሔር የሚፈልገውን ዓይነት ሰው ትሆን ዘንድ በታላቅ ሰይፉ እንዲያስተካክልህ በጸሎት ጠይቀው። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ስለ አለማመን የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (ዕብ. 3፡7-4፡13) Read More »

ክርስቶስ ከሙሴ ይበልጣል (ዕብ. 3፡1-19)

ጸሐፊው ክርስቶስ ከመላእክት እንደሚበልጥና ሰብአዊ ባህሪን በመልበሱ ምክንያት ሙሉ በሙሉ እንደሚረዳን ከገለጸ በኋላ፥ አማኞች (ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋይ የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች) ወደ ክርስቶስ እንዲመለከቱ ይጋብዛል። (ማስታወሻ፡- ዕብ. 3፡1 እንደ «ስለዚህ» ዓይነቶቹን ቃላት በትኩረት መመልከቱ ክፍሉን መረዳታችንን ለማረጋገጥ ጥሩ ምሳሌያችን ነው። ስለዚህ የሚለው ቃል ቀደም ሲል ከተገለጸው እውነት የተነሣ አንድ ልንሰጥ የሚገባን ምላሽ እንዳለ ያመለክታል።) አይሁዶች እርዳታ ፍለጋ ወደ መላእክት መሄድ አያስፈልጋቸውም ነበር። ክርስቲያንና የፖለቲካ መሪዎች የሆኑትን ሰዎችን መፈለግ አያስፈልጋቸውም። ስመ ጥር ወደሆኑ ሰዎች መልስ ፍለጋ መሄድ አያስፈልጋቸውም ነበር። ማየት የሚያስፈልጋቸው ክርስቶስን ብቻ ነበር። ሀ) ሐዋርያ፡- ከእርሱ በበለጠ አካል በውክልና እንዲሠራለት የሚላክ አገልጋይ ነው። ኢየሱስ የእግዚአብሔርን ሙሉ ሥልጣን ይዞ ነበር የተላከው። ወደ ምድር የመጣው፥ የተናገረውና ያደረገው ሁሉ በእግዚአብሔር ፋንታ የተከናወነ ነበር። ስለሆነም ክርስቶስ የተናገረው ወይም ያስተማረውን አለመቀበል ማለት እግዚአብሔር አብን እንዳለመቀበል ማለት ነው። አይሁዶች፥ «እግዚአብሔር አብን እንደ አያት ቅድማያቶቻችን እናመልከዋለን እያሉ ክርስቶስ ግን አንፈልገውም» ሊሉ አይችሉም ነበር። ምክንያቱም ክርስቶስን ባለመቀበል እግዚአብሔር አብንም እየተቃወሙ ነበርና። ለ) ሊቀ ካህናት፡- የአይሁዶች የአምልኮ ሥርዓት የሚመራው በሊቀ ካህናት ነበር። ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታ ያገኙ ዘንድ የኃጢአት መሥዋዕቶችን የሚያቀርበው እርሱ ነበር። ነገር ግን ጸሐፊው የተሻለ መሥዋዕት ያቀረበ (ራሱን) ሌላ የሚበልጥ ሊቀ ካህናት እንዳለ ያመለክታል። የክርስቶስን መሥዋዕት ትቶ ሰብአዊ ሊቀ ካህናት ወደሚያቀርበው የእንስሳት መሥዋዕት መመለሱ ከእግዚአብሔር ዘንድ ከእንግዲህ ይቅርታ አያስገኝም ነበር። አይሁዶች፥ «ክርስቶስ ከመላእክት ሊበልጥ ይችላል ነገር ግን በሲና ተራራ ሕግን ከሰጠን ከሙሴ ሊበልጥ አይችልም» ማለታቸው አይቀርም ነበር። ስለሆነም የዕብራውያን ጸሐፊ ክርስቶስ ከሙሴ እንደሚበልጥ ወደሚናገርበት ሦስተኛ ነጥቡ ይሸጋገራል። በአይሁዶች አስተሳሰብ ከሙሴ የሚበልጥ ሰው አልነበረም። ሙሴ ከግብጽ ባርነት ነፃ አውጥቷቸው ነበር። ከእግዚአብሔር ጋር ቃል ኪዳን እንዲያደርጉና ሕግም እንዲቀበሉ አድርጓል። ከእግዚአብሔር ጋር ፊት ለፊት ተነጋግሯል። ምንም እንኳን አብርሃምና ዳዊት ታላላቅ የእግዚአብሔር ሰዎች ቢሆኑም፥ ሙሴን የሚያህል አልነበረም። (አይሁዶች እንደ ብዙዎቻችን በሰው ላይ ትኩረት በማድረጋቸው አንድን ነገር ለማድረግ የሚያስፈልግ እውነተኛው ኃይል ከየት እንደሚመጣ ዘንግተው ነበር። እስራኤላውያንን ከግብጽ ያወጣው እግዚአብሔር እንጂ ሙሴ አልነበረም።) ሕግንና ቃል ኪዳንን የሰጠው እግዚአብሔር እንጂ ሙሴ አልነበረም። በተመሳሳይ መንገድ ለሰዎችም ድነት (ደኅንነት) የሚሰጠው እግዚአብሔር እንጂ እኛ አይደለንም። በአምልኮ፥ በዝማሬና በቃል፥ በስብከት ውስጥ የሚንቀሳቀሰው እግዚአብሔር እንጂ ኳየሩ ወይም ሰባኪው አይደለም። የዕብራውያን ጸሐፊ ሙሴ ከክርስቶስ ይበልጣል ለሚለው የአይሁዶች አስተሳሰብ መልስ ለመስጠት፥ ሙሴንና ክርስቶስን ያነጻጽራል። ተመሳሳይነታቸው፡ ሀ) ሙሴና ኢየሱስ 1) ሁለቱም ለእግዚአብሔርና ለተሰጣቸው ሥራ ታማኞች ነበሩ። (ሙሴ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከግብጽ ባርነት ማውጣት ኃላፊነት ሲሰጠው፥ ክርስቶስ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከመንፈሳዊ ባርነት ነፃ የማውጣት ኃላፊነት ተሰጥቶት ነበር።) ለ) ሁለቱንም ለአገልግሎት የሾማቸው እግዚአብሔር ነበር። ራሳቸው አገልግሎቱን አልመረጡም። ልዩነቶቻቸው፡ ክርስቶስ በሚከተሉት ምክንያቶች ከሙሴ ይበልጣል ምክንያቱም፡- ሀ) ሙሴ የእግዚአብሔር ቤተሰብ አካል ነበር (የእግዚአብሔር ቤተሰብ)። ሙሴ አይሁዳዊ በመሆኑ የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑት የብሉይ ኪዳን አይሁዳውያን ቤተሰብ ነበር። ክርስቶስ ግን አምላክ እንደ መሆኑ፥ የቤቱ ማለትም የእግዚአብሔር ሕዝብ አናጺ ነበር። የብሉይ ኪዳንንም ሆነ የአዲስ ኪዳንን ሕዝብ የመሠረተው ክርስቶስ ነበር። ለ) ሙሴ በቤቱ ውስጥ (የአይሁድ ሕዝብ) የእግዚአብሔር አገልጋይ ነበር። እርሱም ወደፊት የሚመጣውን ታላቅ ቤት አመልክቷል። ክርስቶስ ለዘላለማዊ ቤት (በእግዚአብሔር ሕዝብ) ላይ ሥልጣን ያለው የእግዚአብሔር ልጅ ነው። ምንም እንኳን ሙሴ ታላቅ፥ የእግዚአብሔር ሰው ቢሆንም፥ አይሁዳውያን አማኞች ሙሴ ሰው መሆኑን መገንዘብ ነበረባቸው። ሰው ደግሞ መመለክ የለበትም፡፡ ክርስቶስ ግን የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚገነባ አምላክ ነው፡፡ ድነትን (ደኅንነትን) ፍለጋ ወደ ሕግና ሙሴ መመለሱ ከአምላክ ወደ ሰው የመመለስ ያህል ነበር። የውይይት ጥያቄ፡- እኛም ክርስቶስን ከማመን ሰውን ወደ ማመን እንዴት ልንመለስ እንደምንችል ግለጽ። ይህ የተሳሳተ የሚሆነው ለምንድን ነው? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ክርስቶስ ከሙሴ ይበልጣል (ዕብ. 3፡1-19) Read More »

ክርስቶስ ከመላእክት ይበልጣል (ዕብ. 1፡4-2፡18)

በአይሁዶች ባሕሪና እምነት ውስጥ መላእክት በከፍተኛ ደረጃ ይከበራሉ። አይሁዶች ታላቅ የእግዚአብሔር መገለጥ እንደሆነ የሚያምኑት የሙሴ ሕግ የተሰጠው በመላእክት በኩል ነበር (ዕብ. 2፡2)። ስለሆነም፥ አይሁዳውያን አማኞች ክርስቶስ ከመላእክት እንደሚበልጥ መረዳት ያስፈልጋቸው ነበር። የዕብራውያን ጸሐፊ ክርስቶስ ከየትኛውም መልአክ የሚበልጥባቸውን መንገዶች እንደሚከተለው ዘርዝሯል፡- ሀ) ክርስቶስ ለየትኞቹም መላእክት ከተሰጠ ስም ወይም ማዕረግ የሚበልጥ ስም አለው። እርሱ የእግዚአብሔር «ልጅ» ተብሏል። ለ) እግዚአብሔር መላእክት ክርስቶስን እንዲያመልኩ አዝዟቸዋል። ሐ) መላእክት የእግዚአብሔር አገልጋዮች እንጂ የሚመለኩ አይደሉም። ነፋስና እሳት ሰውን የሚያገለግሉ ነገሮች እንደሆኑ ሁሉ በነፋስ የሚሠራ ወፍጮ ለማስነሣት፥ ምግብ ለማብሰል፥ ወዘተ)፥ መላእክትም የተፈጠሩት እግዚአብሔርን እንዲያገለግሉ እና ዕቅዱን እንዲፈጽሙ ነው። መ) የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ክርስቶስ አምላክ ነው። አምላክ እንደ መሆኑ መጣን፥ ዙፋኑ ዘላለማዊ ነው። በዚሁ የዘላለም መንግሥት ውስጥ በሰዎች ሁሉ ላይ የመግዛት ሥልጣን አለው። እርሱ ከእግዚአብሔር ፍጥረታት ሁሉ በላይ ነው። ይህም መላእክትንና ሰዎችን ይጨምራል። ሠ) ክርስቶስ ዘላለማዊ ነው። አርጅቶ ከሚሞትና በአንድ ቀን ከሚጠፋ ፍጥረት በተቃራኒ፥ ክርስቶስ ለዘላለም አይለወጥም። ከዚህ በተቃራኒ መላእክት ፍጡራን በመሆናቸው ጅማሬ አላቸው። ረ) ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ የሥልጣን ሥራ ተሰጥቶታል፡፡ ይህ የክብር ስፍራ ከክርስቶስ በቀር ለመላእክት አልተሰጠም። ጸሐፊው ለአይሁዳውያን አማኞች ክርስቶስ እንዴት ታላቅ እንደሆነ እያሳያቸው ነው፡፡ በአጽናፈ ዓለም ውስጥ ያሉትን እንደ መላእክት ያሉትን ታላላቅ የተፈጠሩ ነገሮች በመውሰድ ከክርስቶስ ጋር ያነጻጽራቸዋል። መላእክት ታላቅ ሥልጣን ቢኖራቸውም፥ ክርስቶስ አምላክ በመሆኑ ይበልጣቸዋል። ስለሆነም፥ አይሁዶችና እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ያሉ ሰዎች መላእክትን ማክበር ቢኖርባቸውም፥ ከክርስቶስ ጋር ሲነጻጸሩ ግን እጅግ ዝቅተኛ ስፍራ እንዳላቸው መገንዘብ ይኖርባቸዋል። መመለክ የሚገባው ኢየሱስ ነው፤ መልአክን በፍጹም ማምለክ የለብንም። ከዚያም ጸሐፊው ሌላ አስደናቂ እውነት ይገልጻል። በመላእክትና በክርስቲያኖች መካከል ያለው ግንኙነት ምንድን ነው? ክርስቲያኖች ለመላእክት ልዩ ክብር መስጠት ይገባቸዋል? ወደ መላእክት መጸለይ አለብን? ልናመልካቸው ይገባል? ጸሐፊው በአይሁዳውያን አስተሳሰብ እነዚህን ጥያቄዎች በማንሣት፥ መላእክት ሁሉ መዳንን ይወርሱ ዘንድ ስላላቸው ለማገዝ የሚያገለግሉ መናፍስት አይደሉምን?» ሲል ይጠይቃል። ምንም እንኳን መላእክት ታላቅና ኃያል ቢሆኑም፥ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የእግዚአብሔር መንፈሳዊ አካል የሆኑ ክርስቲያኖች ከመላእክት ይበልጣሉ። መላእክት እግዚአብሔር ፈቃዱን ለማስፈጸም የሚጠቀምባቸው አገልጋዮች ናቸው። እግዚአብሔር ልጆቹን (አማኞችን) እንዲያገለግሉ መላእክትን ይጠቀማል። የውይይት ጥያቄ፡– ይህ ምንባብ መላእክት ላይ ከፍተኛ ትኩረት ማድረግንና እነርሱን ለማምለክ መሻትን በተመለከተ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ የሚሰጠው እንዴት ነው? (የመጀመሪያው የማስጠንቀቂያ ምንባብ – ዕብ. 2፡1-4) ጸሐፊው ክርስቶስ ከመላእክት እንደሚበልጥ ማስተማሩን አቋርጦ የመጀመሪያውን ዐቢይ የማስጠንቀቂያ ምንባብ ያቀርባል። ይህ የጎንዮሽ ጉዳይ በማቅረብ የመጽሐፉን አሳብ የሚያቋርጥ በመሆኑ፥ ምሁራን ቅንፋዊ ሲሉ ይገልጹታል። ከዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ዐበይት ዓላማዎች አንዱ የአይሁድ አማኞችንና ክርስቲያኖችን በሙሉ ከእምነት ተሰናክለው እንዳይወድቁ ማስጠንቀቅ ነው። እያንዳንዱ የማስጠንቀቂያ ምንባብ ካለፈው ይበልጥ እየጠጠረ ይሄዳል። የውይይት ጥያቄ፡- ዘጸ. 19፡1-25፤ 20፡18-21 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር ለአይሁዶች ሕግ ለመስጠት በሲና ተራራ ላይ በተገለጸበት ወቅት ሁኔታው ምን ይመስል እንደነበር ግለጽ። ለ) አይሁዶች ይህን ያህል የፈሩት ለምን ነበር? ሐ) ከፍርሃታቸው የተነሣ ሙሴ ምን እንዲያደርግ ለመኑት? ስለ መላእክት ማስተማሩ ጸሐፊው ሕግ በመላእክት አማካኝነት በእስራኤላውያን ስለተሰጠበት ሁኔታ እንዲያስብና የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔርን ልጅ ለሰው ልጆች ከገለጸበት ሁኔታ ጋር እንዲያነጻጽር አደረገው። የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ክርስቶስ ከመላእክትና ከሙሴ እንደሚበልጥ ሁሉ፥ ክርስቶስ ያመጣው በጻጋ የሚገኝ የመዳን መንገድን እንዲሁ መላእክት ለአይሁዶች ካመጡት የሕግ መንገድ ይበልጥ ነበር (ዘዳግ. 33፡2)። አይሁዶች ሁሉ የሕጉን መሰጠት በታላቅ እድናቆት ነበር የሚያስታውሱት። ቅዱሱ እግዚአብሔር ከመላእክት ጋር ፍጹም ሕጉን ምርጥ ሕዝብ ለሆኑት አይሁዶች ሰጥቷል። ይህ ጊዜ ምን ያህል ልዩ እንደ ነበር መመልከት ይቻላል። አይሁዶች ሁሉ ለዚሁ የሕግ መሰጠት ራሳቸውን ማንጻት ያስፈልጋቸው ነበር። እነርሱም ሆኑ እንስሶቻቸው ወደ ተራራው ቢጠጉ ሞት እንደሚጠብቃቸው ተነግሯቸው ነበር። የእግዚአብሔር የሕልውናው ክብር እጅግ ታላቅ በመሆኑ እስራኤላውያን በፍርሃት ተዋጡ። ከዚህም የተነሣ ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር እንዲገናኝ ጠየቁት። ሕጉ እራሱ የጠነከረ በመሆኑ፥ ከዚሁ የሕግ ክፍሎች አብዛኞቹን መተላለፍ የሞት ቅጣት ያስከትል ነበር (ለምሳሌ፥ ዘጸ. 31፡14፤ 21፡12-17፥ ዘሌዋ. 20፡10-11)። በመሆኑም የብሉይ ኪዳን የሕግ መንገድ አለመቀበሉ ታላቅ ቅጣት ያስከትል ነበር። ስለሆነም፥ በተፈጠሩ መላእክት አማካኝነት የተሰጠው ዝቅተኛው የብሉይ ኪዳን ሕግ ተላላፊዎችን በሞት የሚያስቀጣ ከሆነ፥ የእግዚአብሔር ልጅ በሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የመጣው የእግዚአብሔር የጸጋ መንገድ በማይቀበሉት ሰዎች ላይ የበለጠ ቅጣት ያስከትል ነበር። ይህም በእግዚአብሔር ልጅ በኩል መምጣቱ ብቻ ሳይሆን፥ እግዚአብሔር ለአይሁዶች በተለያዩ ተአምራቶች ያረጋገጠው መንገድ ነው። (እግዚአብሔር ተአምራትን ስለሚልክባቸው ምክንያቶች አንዱ ይህ ነው። ተአምራቶች የሚመጡት የሰዎችን ፍላጎት ብቻ ለማሟላት ሳይሆን ወንጌሉ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ለማረጋገጥ ጭምር ነው።) በኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያምኑ ሰዎች መንፈሳዊ ስጦታዎች መሰጠታቸው ወንጌሉ ከእግዚአብሔር ዘንድ መምጣቱን ያመለክታል። ይህ በብሉይ ኪዳን ዘመን ያልነበረ ልምምድ ነው። ይህንን ሁሉ ችላ ብሎ ዝቅ ወዳለው የሕግ መንገድ መመለሱ የበለጠ ቅጣት ያስከትል ነበር። ይህም ሥጋዊ ሞት ብቻ ሳይሆን፥ መንፈሳዊና ዘላለማዊ ሞት ጭምር ነው። ስለሆነም፥ ጸሐፊው ራሱን ጨምሮ አማኞች ሕይወታቸውን መጠበቅ እንዳለባቸው ያስጠነቅቃል። ክርስቲያኖች ከወንጌሉ እውነት እንዳይወድቁ ያስጠነቅቃቸዋል። ብዙ ጊዜ አለማመን በድንገት የሚከሰት ነገር ሳይሆን በሂደት የሚመጣ ነው። ይህ መልሕቋ ተሰብሮባት ወደ ውኃ እንደምትሰምጥ እና ከዚያም ከድንጋይ ጋር እንደምትጋጭ ጀልባ ማለት ነው። ወይም ደግሞ የታሰረበትን ገመድ በጥሶ ወደ ጫካው ውስጥ በመሮጥ ጉድጓድ ውስጥ እስኪገባ ድረስ በሚንከራተት በኋላም የአውሬ ራት እንደሚሆን በግ ማለት ነው። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ ጸሐፊው ወደ ሐሰት ትምህርት የምንገባውና ባለማመን ልባችን የሚደነድነው ቀስ በቀስ እንደሆነ ይናገራል። መጽሐፍ ቅዱስ ማንበብና ሳናቋርጥ መጸለይ እናቆማለን። ከዓለማውያን ጋር ወዳጅነት እንመሠርታለን። ገንዘብ ወይም ትምህርት ዋነኛው ነገር እንደሆነ በማሰብ በእነዚሁ ነገሮች ላይ እናተኩራለን። ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ እናቆማለን። ዓይኖቻችን ሴቶችን በምኞት ይመለከታሉ። ከሥራ ባልደረቦቻችን ጋር ቢራ መጠጣት እንጀምራለን። እነዚህ ሁሉ ነገሮች መንፈሳዊ ሕይወታችን እንዲጎዳ ያደርጋሉ። በመጨረሻም፥ የእምነታችን መሠረት ይናጋና እምነታችን ይደረመሳል። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እምነቱን ስለካደ እና በግል ስለምታውቀው አንድ ሰው አስብ። ክህደታቸው እምነታቸውን ባለመጠበቃቸው ምክንያት ቀስ በቀስ የጀመረው እንዴት ነበር? ለ) ባለማመን እንዳትወድቅ በሕይወትህ ምን እያደረግክ ነው? ጸሐፊው ክርስቲያኖች ባለማመን እንዳይወድቁ በጽኑ ካስጠነቀቃቸው በኋላ፥ ክርስቶስ ከመላእክት እንደሚበልጥ የሚያስረዳውን ትምህርት ይቀጥላል። ሠ) ክርስቶስ ሰው በመሆኑ ከመላእክት ይበልጣል (ዕብ 2፡5-9)። ጸሐፊው ስለ ሁለት ዓይነት ሰዎች የሚያስብ ይመስላል። በመጀመሪያ፤ ፍጹም ሰው የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ ምንም እንኳን ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ቢሆንም፥ ሰው ሆኗል። ይህ ማለት ግን በሥልጣንና ኃይል ከመላእክት በታች ሆኗል ማለት አይደለም። ክርስቶስ ሰው መሆኑ፥ የመግዛት መብቱን ከመቀነስ ይልቅ በምድር ላይ በመሢሕነቱ እንዲገዛ አስችሎታል። ይህ ሰው ከመሆኑ በፊት የሚቻል አልነበረም። ይህ ደግሞ ለየትኛውም መልአክ ያልተሰጠ መብት ነው። ሁለተኛ፥ ዛሬ ክርስቶስን በታማኝነት ከተከተልነው አማኞች ሁላችንም በክርስቶስ መንግሥት ውስጥ እንደምንገዛ ቃል ተገብቶልናል (2ኛ ጢሞ. 2፡12፤ ራእይ 5፡10)። ብዙውን ጊዜ መላእክት ከሰዎች እንደሚበልጡና አስፈላጊነታውም ከሰዎች በላይ እንደሆነ እናስባለን። ወደ እግዚአብሔር የቀረቡና ቅዱሳን ናቸው ብለን እንገምታለን። ኃጢአት አይሠሩም። የበለጠም ኃይል አላቸው። ስለሆነም ይበልጣሉ ብለን እናስባለን። መጽሐፍ ቅዱስ ግን ከዚህ የተለየ አቋም አለው። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ መዝሙር 8፡4-6ን በመጥቀስ፥ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ ሰዎች ከመላእክት እንደሚበልጡ ያስተምራል። በሚመጣው ዓለም ውስጥ ማለትም ወደፊት በሚመሠረት የክርስቶስ መንግሥት ውስጥ፥ እግዚአብሔር ለመላእክት የመግዛትን ሥልጣን አልሰጠም። ነገር ግን በምድር ላይ እና ወደፊት በሚመጣው መንግሥት ላይ የመግዛት ሥልጣን የተሰጠው ለሰዎች ነው። ምንም እንኳን የሰው ልጅ ከኃያላን መላእክት ጋር ሲነጻጸር ደካማ ቢሆንም፥ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ የመግዛት ሥልጣን የተሰጠው ለሰው እንጂ ለመላእክት አይደለም። እግዚአብሔር ሰዎችን በፈጠረ ጊዜ ምድርን እንዲገዙ ሥልጣን ሰጥቶአቸዋል (ዘፍጥ. 1፡26)። ነገር ግን ከኃጢአት የተነሣ የሰዎች አገዛዝ እግዚአብሔር

ክርስቶስ ከመላእክት ይበልጣል (ዕብ. 1፡4-2፡18) Read More »

ክርስቶስ የሚበልጥ የእግዚአብሔር መገለጥ ነው (ዕብ. 1፡1-3)

ታረቀች ያደገችው በጠንካራ የኦርቶዶክስ አማኞች ቤተሰብ ውስጥ ነበር። ከትንሽነቷ ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በጥንቃቄ መከተል እንዳለባት ተምራለች። በአብዛኛው ተአምረ ማርያም ወይም የኦርቶዶክስን እምነት የሚያጠናክሩትን ሌሎች መጻሕፍት እንድታነብ ትመከር ነበር። ታረቀች በተጨማሪም፥ ክርስቶስ በቀዳሚነት አምላክ እንጂ ሰው እንዳልሆነ፥ እርሱ ታላቅ አምላክ በመሆኑ ምክንያት ሰዎች በቀጥታ ወደ እርሱ ሊደርሱ እንደማይችሉ ተምራለች። በመላእክት ወይም የክርስቶስ እናት በሆነችው ድንግል ማርያም በኩል ልትጸልይ እንደምትችል ተነግሯታል። በማርያም በኩል ከጸለየች እርሷ ጥያቄዋን ለክርስቶስ እንደምታቀርብላት ተረድታለች። ምክንያቱም ጥሩ ልጆች ሁሉ እናቶቻቸውን ይታዘዛሉ። ታረቀች እግዚአብሔር ከእርሷ የሚፈልገው በተወሰኑ ቀናት እንድትጾምና በበዓል ቀናት ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሄደች መላእክትን እንድታገኝ፥ ቅዱሳንንና ድንግል ማርያምን እንድታከብር መሆኑን አመነች። በመሆኑም እነዚህን ልምምዶች ጠንቀቅ ታደርግ ጀመር። አንድ ቀን ታረቀች የኦርቶዶከስ የተሐድሶ ቡድን አባል ከሆነች አማኝ ጋር ተገናኘች። በዚህም ጊዜ ታረቀች የተሐድሶ ቡድን አባል የሆነችው አማኝ ለየት ያለ የንግግር፥ የጸሎትና የአምልኮ ዘይቤ እንደምትከተል ተገነዘበች። ልዩነቱ ከምን እንደ መጣ ስትጠይቅ፥ ይህች የተሐድሶ አባል የክርስትና እምነት አስኳሉ ክርስቶስ እንደሆነ ገለጸችላት። ማምለክ፥ መጸለይ፥ መዘመርና ማክበር ያለብን ክርስቶስን ነው ስትል ገለጸችላት፡፡ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ከመሆኑ በተጨማሪም ፍጹም ሰውና ሊቀ ካህናችን በመሆኑ ሩቅና የማይደረስበት ሳይሆን፥ በቀጥታ ልንጸልይለት የምንችለው አምላክ ነው አለቻት። ድነት (ደኅንነት) በኦርቶዶክስ ቤተሰብ ውስጥ በመወለድ፥ ለድሆች በመመጽወት፥ ለቅድስት ማርያም ወይም ለመላእክት በመጸለይ፥ ሃይማኖታዊ በዓላት ላይ በመገኘት፥ ወዘተ.. እንደማይገኝ አብራራችላት። ድነት (ደኅንነት) ክርስቶስ ለኃጢአቷ መሥዋዕት ሆኖ እንደ ሞተ በማመን የምታገኘው የግላዊ ውሳኔ ውጤት እንደሆነም ገለጸችላት። ይህም ክርስቶስን የመከተልና ከእርሱ ጋር ኅብረት የማድረግን ፍላጎት እንደሚያሳድር አስረዳቻት። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ብዙ የኦርቶዶክስ አማኞች ከክርስቶስ ጋር የግል ግንኙነት ላመመሥረት የሚቸገሩት ለምንድን ነው? ከክርስቶስ ይልቅ ከቅዱሳን፥ ከመላእክት፥ ከድንግል ማርያም ጋር መዛመድ የሚቀላቸው ለምንድን ነው? ሐ) ከቅዱሳን፥ ከመላእክት፥ ወይም ከድንግል ማርያም ይልቅ በክርስቶስ ላይ ማተኮር ለምን እንደሚያስፈልግ ግለጽ። የዕብራውያን መልእክት እንደ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች በመልካም ነገሮች ላይ ዓይኖቻቸውን ላሳረፉ አይሁዶች የተጻፈ መልእክት ነው። እነዚህ መልካም ነገሮች ግን እጅግ አስፈላጊዎች አልነበሩም። የአይሁድ አማኞች የብሉይ ኪዳን ጽሑፎችን፥ የእንስሳት መሥዋዕቶችን፥ ካህኖቻቸውን ወይም እንደ ሙሴ ያሉትን የብሉይ ኪዳን ቅዱሳን ማክበርን፥ እንዲሁም የቤተ መቅደሱን ሕንጻ ወሳኝ አድርገው ይቆጥሩ ነበር። እነዚህ መልካም ነገሮች ላይ በማተኮር፥ እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር በቀጥታ ለመገናኘት የሚፈልግ መሆኑን ዘነጉ። እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ሥጋ ለብሶ ሲመጣ አይሁዶች የብሉይ ኪዳን የተስፋ ቃሎች ፍጻሜ አድርገው ሊቀበሉት አልፈለጉም። እግዚአብሔር አዲስ ነገር እንዳደረገ ሳያውቁ ባህላዊ እምነቶቻቸውንና ልምምዶቻቸውን መከተላቸውን ቀጠሉ። በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተመሳሳይ ዝንባሌ ይታያል። መልካም አስተሳሰብ ያላቸው ብዙ ሰዎች በቤተ ክርስቲያን ሕንጻዎቻቸው በካህኖቻቸው፥ በታቦት፥ በሃይማኖታዊ ባርነት ወይም በጾም ላይ ያተኩራሉ። ቅዱሳንን፥ መላእክትንና ድንግል ማርያምን በጥንቃቄ ያከብራሉ። ይህን በማድረጋቸው ግን እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን እንደ ልጆቹ በቀጥታ ከእርሱ ጋር እንዲገናኙ የሚፈልግ መሆኑን ለማየት ታውረዋል። ክርስቶስ በሞተበት ጊዜ ሰውንና እግዚአብሔርን ይለይ የነበረው የቤተ መቅደስ መጋረጃ ተቀዷል። አሁን ኢየሱስ ክርስቶስ የግል ኃጢአታቸው መሥዋዕት እንደሆነ የሚያምኑ ሰዎች በሙሉ በድፍረትና በልበ ሙሉነት እግዚአብሔር ወደሚገኝበት የጸጋው ዙፋን ሊቀርቡ ይችላሉ። በዚህም ጊዜ ከሚወዳቸውና ከሚንከባከባቸው ሰማያዊ አባታቸው ጋር እንደሚነጋገሩ ይረዳሉ። የዕብራውያን ጸሐፊ ይህንን ታላቅ መጽሐፍ የጻፈው እግዚአብሔር በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል ያከናወነውን ተግባር ቸል እያሉ በትውፊቶችና ውጫዊ ነገሮች ላይ ማተኮሩ ስሕተት መሆኑን ለማመልከት ነው። ይህ መጽሐፍ ከውጫዊ ነገሮች ወይም ከትውፊቶቻችን በላይ የእምነታችን ጀማሪና ራስ በሆነው (ዕብ 12፡2-3) በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ዓይናችንን እንድንተክል ያሳስበናል። ይህ መልእክት አይሁዶች በብሉይ ኪዳን አምልኮ ውስጥ እጅግ ከሚያከብሯቸው ነገሮች ሁሉ ክርስቶስ እንደሚበልጥ በጥንቃቄ ያሳያል። ጸሐፊው አይሁዶች ወደ ታሪካዊና ትውፊታዊ አምልኳቸው በመመለስ ክርስቶስ እንዳልሞተላቸው ሁሉ የቀድሞ አኗኗራቸውን እንዳይቀጥሉ በጽኑ ያስጠነቅቃቸዋል። ዛሬ እኛ እንደ ካህናትና ዝነኛ ሰባኪዎች በመሳሰሉት ሰዎች ትኩረት እንዳናደርግ ያስጠነቅቀናል። እንደ ማርያም ወይም መላእክት ያሉትን አማላጆችን መጠቀም የለብንም። እንዲህ የምናደርግ ከሆነ በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት ማድረጉ በቂ እንዳልሆነ መግለጻችን ነው። ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት ለመለካት የቤተ ክርስቲያን አባልነት፥ ለደሃ መመጽወት፥ የአንድ ቤተ እምነት አባል መሆን፥ በልሳን መናገር ወይም ፈውሶች በመሳሰሉት ውጫዊ ነገሮች ላይ ማተኮር የለብንም። ይልቁንም መንፈሳዊ ዓይኖቻችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ሊያርፉና ከእርሱ ጋር ያለማቋረጥ ግንኙነት ልንፈጥር ይገባል። ልክ እንደኛው አይሁዶችም የሃይማኖታቸው ሁሉ መሠረት ቅዱሳት መጻሕፍት (ብሉይ ኪዳን) መሆናቸውን ያምኑ ነበር። እግዚአብሔር ለግለሰቦች እራሱን ለመግለጡ እነርሱም በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው የእግዚአብሔርን ቃላት ለመጻፍ በቅተዋል። አይሁዶች ቅዱሳት መጻሕፍትንና እግዚአብሔር መልእክቱን ለመጻፍ የተጠቀመባቸውን አገልጋዮች እጅግ ያከብሩአቸዋል። አይሁዶች ብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የገለጠው በእስትንፋሰ እግዚአብሔር የተጻፈ መልእክት እንደሆነና ይህም በቀዳሚነት ክርስቶስን ለሰዎች የሚገልጥ እንደሆነ ያምኑ ነበር። የሚገርመው ግን አይሁዶች አካላዊውን መጽሐፍ እጅግ እያከበሩት (የእግዚአብሔርን ቃል ለማክበር ብራናውን ይስሙት ነበር።)፤ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እጽንኦት የሰጡበትን ክርስቶስን ለማወቅ አልቻሉም። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ የእግዚአብሔር የመጨረሻው መገለጥ የሆነው ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ውስት ከታዩት መገለጦች ሁሉ እንደሚበልጥ ለመግለጽ ማብራሪያውን ይጀምራል። ጸሐፊው ታሪክን በሁለት ይከፍላል። እነዚህም ከጥንት ጀምሮ እና በዚህ ዘመን መጨረሻ የሚሉ ናቸው። ጥንት ወይም በብሉይ ኪዳን ዘመን፥ እግዚአብሔር ራሱን ገልጦ ለአይሁዶች ተናግሯል። እግዚአብሔር ራሱን ለነቢያት ለመግለጥ የተለያዩ መንገዶችን ተጠቅሟል። አንዳንዶች ራእዮችን አይተዋል። ሌሎች ደግሞ ሕልም አልመዋል። ሌሎች ቃሉን በሚጽፉበት ጊዜ መንፈስ ቅዱስ በልባቸው ላይ ሲንቀሳቀስ ይሰማቸው ነበር። እንዲሁም የእግዚአብሔርን ድምጽ ከመስማታቸው የተነሣ የጻፉ ነቢያትም ነበሩ። መልእክቱ የመጣበት መንገድ ወሳኝ አልነበረም። ዋናው ከእግዚአብሔር ዘንድ መምጣቱ እና የእግዚአብሔር ቃል መሆኑ ብቻ ነበር። ክርስቶስ በመጣ ጊዜ፥ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ከብሉይ ኪዳን እጅግ በጠራ መንገድ ገልጧል። በሌላ ሰው በኩል ከመናገር ይልቅ ራሱ እግዚአብሔር በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ወደ ምድር መጣ። በዚህ ጊዜ በመናገር ብቻ ሳይሆን፥ ለሰዎች በሚታይ መልኩ የእግዚአብሔርን ባህሪ እና ፈቃድ በግልጽ አሳይቷል። ጸሐፊው ክርስቶስ መልካም ሰው፥ ወይም በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩትን ነቢያት የሚመስል ሰው ብቻ እንዳልሆነ ይናገራል። ይልቁንም እርሱ ራሱ አምላክ ነበር። እግዚአብሔር በክርስቶስ በኩል ያስተላለፈው መገለጥ ከሌሎች የሚበልጠው የእግዚአብሔርን ፈቃድ የገለጠው ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ከሰብአዊ ነቢያት የሚበልጥ በመሆኑ ምክንያት ነው። እርሱ በብሉይ ኪዳን ዘመን የእግዚአብሔርን ቃል ከተቀበሉትና እግዚአብሔር ራሱን አያሌ ጊዜያት ከገለጠባቸው ሰዎች ሁሉ በላይ ነው። ሀ) የእግዚአብሔር መንግሥት ወራሽ የሆነውና እግዚአብሔር ወደ ዓለም የሚያመጣቸውን በረከቶች ሁሉ የሚቀበለው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። እርሱ ዙፋን ወራሽና አይሁዶች የሚጠብቁት መሢሕ ነው። ለ) እግዚአብሔር አብ ነገሮችን ሁሉ ለመፍጠር ክርስቶስን ሾሟል። ሐ) ክርስቶስ ሰው ብቻ ሳይሆን አምላክም ነው። እርሱም ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩል የሆነ ክብር አለው። የክብሩ መንጸባረቅና የባሕሪው ምሳሌ በመሆኑ በሕልውናው፥ በባሕሪውና በተግባራቱ ልክ እንደ እግዚአብሔር አብ ነው። መ) ክርስቶስ «ሁሉን በሥልጣኑ ቃል እየደገፈ» አጽናፈ ዓለሙን ጠብቆ ያኖረዋል። ሠ) ኃጢአታችንን የሚያነጻው ክርስቶስ ነው። ረ) ክርስቶስ «በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀምጧል።» ይህም የክብር ስፍራ ነው። በጥንታዊ ባህሎች፥ አንድ ንጉሥ በአዛዥነት ከእርሱ ቀጥሎ ያለውን ባለሥልጣን (ብዙውን ጊዜ የራሱን ልጅ ወይም እንደ ጠቅላይ ሚኒስቴር ያለውን ባለ ሥልጣን) ከቀኙ ያስቀምጠው ነበር። ምንም እንኳን በዋንኛው ሰማያዊ ዙፋን ላይ የሚቀመጠው እግዚአብሔር አብ ቢሆንም፥ የዚህ መልእክት ጸሐፊ ክርስቶስ ከሌሎች ኃይሎች ሁሉ ከፍ ብሎ በእግዚአብሔር አብ የሥልጣንና የአገዛዝ ቀኝ እንደሚቀመጥ ይናገራል። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ ጥቅሶች ክርስቶስ ሙሉ በሙሉ አምላክ እንደሆነ የሚያሳዩበትን ሁኔታ አብራራ። ለ) ክርስቶስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩልና ዳሩ ግን የተለየ መሆኑን የሚያሳዩት እንዴት ነው? ሐ) እነዚህ ጥቅሶች እግዚአብሔር አብና ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ እንጂ የተለያዩ የሥላሴ አካላት አለመሆናቸውን የሚያስረዳውን «የኢየሱስ ብቻ» ተከታዮች

ክርስቶስ የሚበልጥ የእግዚአብሔር መገለጥ ነው (ዕብ. 1፡1-3) Read More »

የዕብራውያን መልእክት ልዩ ባሕርያት፣ መዋቅር እና አስተዋጽኦ

የዕብራውያን መልእክት ልዩ ባሕርያት የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ እንደ ጳውሎስ ኢየሱስ ክርስቶስ፥ ክርስቶስ ኢየሱስ ወይም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እያለ አይጽፍም። ነገር ግን አንዱን ስም ብቻ (ኢየሱስ ወይም ክርስቶስ) ሲል ይጽፋል። ከመጨረሻዎቹ ጥቂት ቁጥሮች በስተቀር፥ የዕብራውያን መልእክት ደብዳቤ አይመስልም። ጸሐፊው ስሙን በማስተዋወቅ ሰላምታ የሚሰጥበት መግቢያ በመጽሐፉ ውስጥ አይገኝም። ይህ እምነታቸውን ለመካድ ለሚያስቡ የተወሰኑ የአይሁድ ክርስቲያኖች የተላከ ሰነድ ወይም ስብከት ነው። በመጽሐፉ ውስጥ አምስት «የማስጠንቀቂያ» ምንባቦች አሉ (ዕብ. 2፡1-4፤ 3፡7-4፡13፤ 5፡11-6፡8፤ 10፡19-39፤ 12፡14-29)። (ማስታወሻ፡ አንዳንድ ምሁራን ሰባት የማስጠንቀቂያ ምንባቦች እንዳሉ ይናገራሉ። እነዚህም፥ ዕብ. 2፡1-4፣ 3፡7-19፣ 4፡11-13፤ 5፡11-6፡20፣ 10፡26-31፤ 12፡25-29፥ 13፡15-19)። እነዚህ ምንባቦች እማኞች ክርስቶስን ክደው ወደ ቀድሞው አኗኗራቸው እንዳይመለሱ ጽኑ ማስጠንቀቂያዎችን ይሰጣሉ። ድነት (ደኅንነት) እና ዘላለማዊ በረከቶች የሚገኙት በክርስቶስ ብቻ ነው። የዕብራውያን መልእክት አይሁዳውያን ክርስቲያኖች በሚገባ የሚያውቁትን ብሉይ ኪዳን በብዙ ስፍራዎች ላይ ይጠቅሳል። ነገር ግን ጸሐፊው የተጠቀመባቸው የብሉይ ኪዳን ክፍሎች የተወሰዱት ከአረማይክ ወይም ዕብራውያን የብሉይ ኪዳን ሳይሆን፥ ሴብቱዋጄንት ከሚባለው የግሪክ የብሉይ ኪዳን ትርጉም ነው። ይህም እነዚህ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች የዕብራውያን የብሉይ ኪዳን በብዛት ከግልጋሎት ላይ ከሚውልበት ኢየሩሳሌም ከተማ ሳይሆን፥ የግሪክ የብሉይ ኪዳን አገልግሎት በሚሰጥባት በሌላ የሮም ግዛት ውስጥ እንደነበሩ ያመለክታል። ጸሐፊው ከብሉይ ኪዳን ሲጠቅስ፥ በአብዛኛው ከሙሴ መጻሕፍት ወይም ከመዝሙራት ይጠቅሳል። እንደ ብዙዎች የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ሙሴ ወይም ዳዊት ምንባቡን እንደ ጻፈው ከመናገር ይልቅ እግዚአብሔር (ዕብ. 2፡6)፥ ኢየሱስ (ዕብ. 2፡11-12) ወይም መንፈስ ቅዱስ (ዕብ. 3፡7) ምንባቡን እንደተናገረ ይገልጻል። በዚህም የብሉይ ኪዳንን መለኮታዊ ሥልጣን ከፍ አድርጎ ያሳያል። ጸሐፊው እንደ ሀ) «የሚሻል» (ዕብ. 1፡4፤ 6፡9፣ 7፡7፥ 22፤ 8፡6፤ ወዘተ…)፤ ለ) «ዘላለማዊ» (ዕብ 1፡8፤ 5፡6፥ 9፤ 6፡1-2፥ 20፣ 7፡11፥ 17፥ 21፥ 24፥ 28፤ ወዘተ…)፤ ሐ) «ፍጹም» (ዕብ. 2፡10፤ 5፡9፣ 7፡11፥ 19፣ 9፡9፤ 10፡1፥ 14፤ ወዘተ..) መ) «ሰማያዊ» (ዕብ. 1፡10፤ 3፡1፤ 4፡14፤ 6፡4፤ ወዘተ) ባሉት ቃላት ላይ ትኩረት ይሰጣል። ጸሐፊው ትምህርቱ ራሱንም እንደሚያጠቃልል የሚያመለክቱትን አገላለጾች ይጠቀማል (ዕብ. 4፡1፥ 11፥ 14፥ 16፤ 6፡1፤ 10፡22-25፤ 12፡1-3፥ 28፤ 13፡1፥5፥ 13፥15።) የዕብራውያን መልእክት ስለ ክርስቶስ ማንነትና ሥራ ሰፊ ማብራሪያ ያቀርባል። ክርስቶስ ካህናችን መሆኑን፥ ለኃጢአታችን መሠዋቱን፥ እንዲሁም ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው መሆኑን ያብራራል። የዕብራውያን መዋቅር ዕብራውያን በጥንቃቄ የተዋቀረ መጽሐፍ ነው። ጸሐፊው ክርስቶስ ከሌሎች የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ማዕከላት እንደሚበልጥና የእነዚሁ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓቶች ፍጻሜ የሆነላቸውን ምክንያቶች በመዘርዘር መልእክቱን ግሩም አድርጎ አዋቅሮአል። በመሠረታዊነት ይህ መልእክት ሁለት ዐበይት ክፍሎች አሉት። ሀ. ዕብ. 1፡1–10፡18 የመጽሐፉን መሠረታዊ ትምህርት ያቀርባል። ይኸውም አይሁዶች ጥንታዊ ሃይማኖታቸውን ታላቅ እንዳደረጉ ከሚያስቧቸው ነገሮች ሁሉ ክርስቶስ እንደሚበልጥ የሚያሳይ ነው። ክርስቶስ ከብሉይ ኪዳን ቅዱሳን መጻሕፍት፥ መላእክት፥ ሙሴ፥ ኢያሱ፥ አሮን፥ የእንስሳት መሥዋዕቶች፥ ወዘተ እንደሚበልጥ ተገልጾአል። ለ) ዕብ. 10፡19-13፡25 በእምነት መኖር ምን ማለት እንደሆነና አማኞች እምነታቸውን በእግዚአብሔር ላይ በመጣል እንዴት በታማኝነት እንደሚጻኑ ያብራራል። ወደ መንግሥተ ሰማይ እስክንደርስ ድረስ ለእርስ በርሳችን ታማኞች ሆነን መጽናት ይኖርብናል። መንግሥተ ሰማይ አማኞችን ሁሉ በመጠባበቅ ላይ ያለች እውነተኛይቱ ኢየሩሳሌም ናት። ጸሐፊው ትምህርቱን በሚያቀርብበት ጊዜ በአመዛኙ ቆም ይልና የሚያስተምራቸው እውነቶች ምን ዓይነት አስከትሎት እንዳላቸው ለአንባብያኑ ያስገነዝባል። በተለይም እንዲህ ዓይነቱን ማስጠንቀቂያ የሚሰጠው ክርስቶስን ክዶ ወደ ይሁዲነት መመለስ አደገኛ መሆኑን ለማመልከት ነው። እነዚህ አምስት (አንዳንድ ምሁራን እስከ ሰባት ያደርጓቸዋል) የማስጠንቀቂያ ምዕራፎች (ዕብ. 2፡1-4፤ 3፡7-4፡13፤ 5፡11-6፡8፤ 10፡19-39፤ 12፡14-29) ቅንፋዊ ምንባቦች በመባል ይታወቃሉ፥ ለዚህም ምክንያቱ እነዚህ ምንባቦች ወደኋላ ለመመለስ የሚያስቡትን ሰዎች ለማስጠንቀቅ ሲሉ የክርክሩን ይዘት የሚያቋርጡ መሆናቸው ነው። ጸሐፊው ማስጠንቀቂያውን ከሰጠ በኋላ፥ ወደ አሳቡ በመመለስ ክርስቶስ ከብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓት እንደሚበልጥ የሚያምንባቸውን ማረጋገጫዎች ያቀርባሉ። የዕብራውያን አስተዋጽኦ ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ከተከበሩት ነገሮች ሁሉ በላይ ነው (ዕብ. 1፡1-10፡18)። ሀ. ክርስቶስ የእግዚአብሔር ከፍተኛው መገለጥ ነው (ዕብ 1፡1-3)። ለ) ክርስቶስ ከመላእክት ይበልጣል (ዕብ. 1፡4-2፡18)። የመጀመሪያው የማስጠንቀቂያ ምንባብ – (ዕብ 2፡1-4) ሐ) ክርስቶስ ከሙሴ ይበልጣል (ዕብ. 3፡1-19)። መ) ሁለተኛው የማስጠንቀቂያ ምንባብ- ዕብ 3፡7-4፡13። [ክርስቶስ ከኢያሱ እንደሚበልጥ የሚናገረውን ክፍል ያጠቃልላል።(ዕብ. 4፡1-13)] ሠ. ክርስቶስ ከአሮን ወገን ከሆኑት ሊቀ ካህናት ይበልጣል (ዕብ. 4፡14-7፡28)። ክርስቶስ ሊቀ ካህናት ለመሆን ብቁ ነው (ዕብ. 4፡14–5፡10)። ሦስተኛ የማስጠንቀቂያ መልእክት (ዕብ. 5፡11-6፡20)። የክርስቶስ ሊቀ ካህንነት ከአሮን ይበልጣል (ዕብ 7)። ረ) የክርስቶስ አገልግሎትና መሥዋዕት በብሉይ ኪዳን ዘመን ከነበሩት ይበልጣል (ዕብ. 8-10)። የክርስቶስ አገልግሎት ከብሉይ ኪዳን በሚበልጠው አዲስ ኪዳን ላይ የተመሠረተ ነው (ዕብ 8)። የክርስቶስ አገልግሎት ከመገናኛ ድንኳን በሚበልጠው ሰማያዊ ቤተ መቅደስ ውስጥ ይካሄዳል (ዕብ. 9፡1-12)። የክርስቶስ መሥዋዕት ከእንስሳት መሥዋዕቶች ይበልጣል (ዕብ 9፡13–10፡18)። ክርስቶስ ከብሉይ ኪዳን ውስጥ ካሉት ነገሮች ሁሉ ስለሚበልጥ፥ እርሱን እንዴት መከተል እንዳለብን (ዕብ. 10፡19–13፡25) ሀ. አራተኛው የማስጠንቀቂያ ምንባብ (ዕብ. 10፡19-39)። ለ. ክርስቶስን መከተል እምነትን ይጠይቃል (ዕብ. 11)። ሐ. ክርስቶስን መከተል ማለት በመንፈሳዊ ሩጫችን መጽናት ማለት ነው (ዕብ. 12፡1-13)። መ. አምስተኛው የማስጠንቀቂያ ምዕራፍ (ዕብ. 12፡14–29)። ሠ. እንደ የክርስቶስ ተከታዮች እንዴት መመላለስ እንዳለብን (ዕብ. 13፡1-17)። ረ. መደምደሚያ (ዕብ. 13፡18-25)

የዕብራውያን መልእክት ልዩ ባሕርያት፣ መዋቅር እና አስተዋጽኦ Read More »

የዕብራውያን መልእክት ዓላማ

የውይይት ጥያቄ፡- የሚከተሉትን ጥቅሶች አንብብ። ዕብ. 1፡1-4፤ 3፡3፤ 6፡9፤ 7፡7፤ 19፥22፤ 8፡6፤ 9፡23፤ 10፡34፤ 11፡16፥35፥ 40፤ 12፡24። የዕብራውያን መልእክት ክርስቶስ ካምን ከምን እንደሚበልጥ ይናገራል? የመጀመሪያ ዓላማ፡ ኢየሱስ ክርስቶስ አይሁዶች በብሉይ ኪዳን ዘመን ታላቅ ነው ብለው ከሚያስቡት ነገር ሁሉ እንደሚበልጥ ለማሳየት። አይሁዶች ረዥም ዘመናት ውርሳቸውና በብሉይ ኪዳን ከእግዚአብሔር ጋር በነበራቸው ልዩ ቃል ኪዳን ምክንያት ከፍተኛ የትምክህተኝነት ስሜት ይሰማቸው ነበር። የእግዚአብሔር እስትንፋስ ያረፈበት ቃልና ኪዳናት ነበሩዋቸው። አይሁዶች በመላእክት የተጎበኙ፥ ከሙሴ ሕግን የተቀበሉና እግዚአብሔር ባዘዛቸው መንገድ አምልኮአቸውን የሚያካሂዱ፥ ወዘተ… በመሆናቸው ይኩራሩ ነበር። አይሁዳውያን ክርስቲያኖች በተለይ ከወገኖቻቸው ስደት በተነሣ ጊዜ በእነዚህ ነገሮች ላይ አጽንኦት ወደ መስጠቱ አቅጣጫ ለመመለስ እየተፈተኑ ነበር። ጸሐፊው ለዚህ ሁኔታ ምላሽ ለመስጠት አይሁዶች ወደ ብሉይ ኪዳን የአምልኮ መንገድ ቢመለሱ፥ በክርስቶስ የመስቀል ላይ ሞት ማመናቸውን እንደ ካዱ ያስረዳል። ክርስቶስ ታላቅ ሰው ነው ብሎ ቢያስቡም እንኳን፥ ወደ ብሉይ ኪዳን መመለሱ የክህደት ተግባር ነበር። ለኃጢአታቸው መሞቱን ጭራሽ እንዳልተፈጸመ ታሪክ ከንቱ ማድረጋቸው ነበር። የእግዚአብሔርን የድነት (ደኅንነት) መንገድ ባለመቀበላቸው ሌላ የመዳን መንገድ አያገኙም ነበር። እግዚአብሔር የእንስሳት መሥዋዕቶችን የድነት (ደኅንነት) እና የይቅርታ መንገድ አድርጎ የሚቀበልበት ጊዜ አልፎ ነበር። ጸሐፊው የክርስቶስን ታላቅነትና እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን ያቀደው ነገር ሁሉ ፍጻሜው መሆኑን ያስረዳል። ብሉይ ኪዳን እንደ ጥላ ሲሆን፥ እውነታው ክርስቶስ ነበር። ክርስቶስ የሚገልጣቸውን ነገሮች በተምሳሌትነት አሳይቷል። ጸሐፊው ለምን አይሁዳውያን ክርስቶስ ላይ ዓይኖቻቸውን መትከል እንዳለባቸውን ወደ ይሁዲነት መመለስ እንደሌለባቸው ሲገልጽ፥ የሚከተሉትን ነጥቦች አብራርቷል። ክርስቶስ ከሚከተሉት ሁሉ እንደሚበልጥ፥ በዕብራውያን መልእክት ውስጥ እንመለከታለን፡ ሀ) ክርስቶስ እግዚአብሔር ከገለጣቸው ቀደምት መገለጦች፥ እንደ ኢሳይያስ ካሉት ነቢያትም የሚበልጥ ነው። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን ቃሉን የሰጠው በደካማ የሰው ልጆች በኩል ሲሆን፥ በአዲስ ኪዳን ዘመን ግን አምላክ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኝነት ነበር። እርሱም በአካል ተገኝቶ በሰዎች መካከል ያደረና እግዚአብሔርን በታላቅ አኳኋን የገለጸ አምላክ ነው (ዕብ. 1፡1-4)። ለ) ክርስቶስ አይሁዶች፥ ከሚያከብሩአቸው የብሉይ ኪዳን መላእክት በላይ ነበር። ጸሐፊው መላእክት እግዚአብሔር ሕዝቡን እንዲያገለግሉ የሚልካቸው መናፍስት መሆናቸውን ይናገራል። መላእክት የእግዚአብሔር አገልጋዮች ነበሩ። ክርስቶስ ግን አምላክና ሰዎች እንዲሁም መላእክት የሚሰግዱለት መሆኑን ተመልክቷል (ዕብ. 1፡3-2፡18)። ሐ) ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ታላቅ ሕግ ሰጪ ከነበረው ከሙሴ በላይ ነው (ዕብ. 3፡1-6)። ሙሴ ምንም ያህል ታላቅ ቢሆንም፥ የቤቱ አካል ወይም የእግዚአብሔር ሕዝብ አካል ነበር። ክርስቶስ ግን አምላክ እንደ መሆኑ፥ ከእግዚአብሔር ሕዝብ በላይ ነበር። እርሱ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ቤት ንድፍ እንደሚያወጣና እንደሚቆጣጠር ዕቅድ ነዳፊ ነበር። መ) ክርስቶስ ከሊቀ ካህናቱ ከአሮን ይበልጣል (ዕብ. 5፡1-10)። አሮንና ከእርሱ በኋላ የነበሩት ሊቀ ካህናት በሙሉ ኃጢአተኞች በመሆናቸው፥ ለራሳቸው ኃጢአቶች መሥዋዕቶችን ማቅረብ ያስፈልጋቸው ነበር። አሮን ሰው በመሆኑ በሞት እንደ ተሸነፈና ሌሎች (ብዙዎች መንፈሳዊያን ያልሆኑ የሊቀ ካህናትነት አገልግሎቱን እንደተቀበሉ ተገልጾአል። ክርስቶስ በብዙ መንገድ ከአሮን ይበልጣል። ክርስቶስ ካህንም ንጉሥም በመሆኑ ከአሮን ይበልጣል። ኃጢአት የሌለበት እና ፍጹም በመሆኑ ከአሮን ይበልጣል። ሰውም አምላክም በመሆኑና ከዚህም የተነሣ ሰውንና እግዚአብሔርን ለመወከል በመቻሉ ከአሮን ይበልጣል። አሮን አገልግሎቱ ባለመጠናቀቁ ምክንያት ለማረፍ ያልተፈቀደለት ሲሆን፥ ክርስቶስ የመሥዋዕትነት አገልግሎቱን ስላጠናቀቀና እንደገና መድገም ስለማያስፈልገው በእግዚአብሔር አብ ቀኝ ተቀምጧል። በአሮንና በሊቀ ካህናት ዘመን ሰዎች ወደ እግዚአብሔር እንዳይቀርቡ የሚከላከል መጋረጃ በቤተ መቅደስ ውስጥ ነበር። ክርስቶስ በሞተ ጊዜ ግን መጋረጃ ው ከላይ እስከ ታች ተቀዷል፤ በመሆኑም አማኞች በድፍረት ወደ ጸጋው ዙፋን ሊቀርቡ ይችላሉ)። ሠ) ክርስቶስ ከብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች የበለጠ መሥዋዕት ነው (ዕብ 9፡11-14)። እንስሳት ጊዜያዊ የኃጢአት ይቅርታ ከማስገኘት ያለፈ ፋይዳ የላቸውም፡፡ እንስሳት እንደ መሆናቸው፥ ለሰዎች ኃጢአቶች ምትክ ሆነው ሊሞቱ አይችሉም። ክርስቶስ ግን ሰውም አምላክም በመሆኑ፥ የበለጠ ታላቅ መሥዋዕት ሆኗል። የብሉይ ኪዳን እንስሳት ባለማቋረጥ መሠዋት የነበረባቸው ሲሆን (በቀን ብዙ እንስሳት፥ በዓመት በሚሊዮን የሚቆጠር)፥ የክርስቶስ አንድ መሥዋዕት ከአዳም ጀምሮ እስከ መጨረሻው ግለሰብ ያሉትን ሰዎች ኃጢአት ለማንጻት ችሏል። የእንስሳት መሥዋዕቶች ከፊልና ጊዜያዊ የኃጢአት መሸፈኛ ነበሩ። የክርስቶስ መሥዋዕት ግን ዘለቄታዊ በመሆኑ፥ በእርሱ የሚያምኑትን ለዘላለም ያነጻቸዋል። ረ) ክርስቶስ በላቀ ድንኳን ወይም ቤተ መቅደስ ውስጥ ያገለግላል ( ዕብ. 9፡1-10)። ሰብአዊ ካህናት የሰማያዊቱ ቤተ መቅደስ ነጸብራቅ በሆነ እና ፍጹምነት በጎደለው የመገናኛ ድንኳን ወይም ቤተ መቅደስ ውስጥ አገልግለዋል። (ይህ ልጆች የሚሰሩት የቆርቆሮ መኪና ከእውነተኛ ትልቅ መኪና እንደሚያንስ ማለት ነው።) ክርስቶስ እውነተኛ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ በሆነችው መንግሥተ ሰማያት ውስጥ ያገለግላል። ምንም እንኳን ክርስቶስ በምድር ላይ ቢሞትም፥ እግዚአብሔር በሚቀበለው መንገድ ኃጢአት ይቅርታ የሚያገኝበትን መንገድ ለማቅረብ ደሙን (ሕይወቱን የሠዋው) በሰማይ ነበር። ክርስቶስ የብሉይ ኪዳንና የአይሁዶች የአምልኮ ሥርዓት ማዕከላት ከሆኑት ነገሮች ሁሉ ስለሚበልጥ፥ ከክርስቶስ ርቆ ፍጹም ወዳልሆነ፥ የአምልኮ ሥርዓት መመለሱ ሞኝነት ነበር። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እንደ ክርስቶስ ታላቅ ሳይሆኑ ዛሬ ክርስቲያኖችን የሚማርኩ የሚመስሉትን አንዳንድ ነገሮች ዘርዝር። በሕይወትህ ውስጥ የሚማርኩ፥ ዳሩ ግን በዘላለም ዘመን አንጻር ሲታዩ መልካም ያልሆኑና እምነትን ሊያወድሙ የሚችሉ ነገሮች መኖራቸውን ለማወቅ ሕይወትህን መርምር። እነዚህን ነገሮች ለእግዚአብሔር ተናዘዝና ከጊዜያዊ ነገሮች ይልቅ ወሳኝ የሆኑትን ለመከተል ቁረጥ። የውይይት ጥያቄ፡– ዕብ. 2፡1-4፤ 3፡12-14፤ 4፡1-2፤ 5፡11-6፡8፤ 10፡26-31 አንብብ። በእነዚህ ምንባቦች ውስጥ ለክርስቲያኖች የተሰጡት ማስጠንቀቂያዎች ምን ምን ናቸው? ሁለተኛ ዓላማ፡ አማኞች ከስደት ለማምለጥ ብለው በክርስቶስ ላይ ያላቸውን እምነት እንዳይክዱ በጽኑ ለማስጠንቀቅ። ክርስቲያኖች እምነታቸውን እንዳይክዱ የሚያሳስቡ እጅግ ጠንካራ ማስጠንቀቂያዎች በዕብራውያን መልእክት ውስጥ ይገኛሉ። አይሁዳውያን ክርስቲያኖች በክርስቶስ በማመናቸው ምክንያት ከአይሁዳውያን ወገኖቻቸው የሚመጣውን ስደት ፈርተው ነበር። ብዙዎቹ እምነታቸውን ለመደበቅ፥ ወይም እምነታቸውን ክደው ወደ ይሁዲነት ለመመለስ እያሰቡ ነበር። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ እምነታቸውን ከመካድ ይልቅ በድፍረት ስደትን እንዲቀበሉ ይመክራቸዋል። የአይሁድ ክርስቲያኖች ስለ ክርስቶስ ብዙ ካወቁ በኋላ እምነታቸውን ሲክዱ፥ ዘላለማዊ ቅጣቶች ይከተሏቸዋል። ሌላ የመዳን መንገድ አያገኙም። ስለሆነም ወደ ኋላ ከመመለስ ይልቅ በብሉይ ኪዳን ዘመን እንደ ነበሩትና ከጊዜያዊ ችግሮች አሻግረው የሰማይን በረክቶች እንደ ተመለከቱት የእምነት ጀግኖች መሆን ያስፈልጋቸው ነበር። ሊቀ ካህናችን የሆነው ክርስቶስ ደግሞ ትግላችንን ስለሚያውቅ እነዚህን ፈተናዎች እንድናሸንፍ ይረዳናል፡፡ የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በኢትዮጵያ ብዙ አማኞች እምነታቸውን የካዱት ለምንድን ነው? ለ) እንደ እነዚህ ዓይነት ውሳኔዎች ስለሚያስከትሏቸው ዘላለማዊ ውጤቶች የዘነጉት ነገር ምንድን ነው? ሐ) ሰዎች እምነታቸውን መካድን እንደ አማራጭ እንዳይወስዱ ቤተ ክርስቲያን እንዴት በተሻለ ሁኔታ ልታስተመራቸው ትችላለች? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የዕብራውያን መልእክት ዓላማ Read More »

የዕብራውያን መልእክት ለማን፣ መቼ እና የት ተጻፈ

መልእክቱ የተጻፈው ለማን ነበር? የመልእክቱ ተቀባዮች አይሁዶች መሆናቸው ግልጽ ነው። ይህ የጥንት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ለመጽሐፉ ከሰጡት «ዕብራውያን» ከሚለው የመጽሐፉ ስያሜ በግልጽ የሚንጸባረቅ ነው። (የዕብራውያን የጥንት የአይሁዶች ስም ነው።) መጽሐፉ አንባቢዎቹ የብሉይ ኪዳንን የመገናኛ ድንኳንና የአምልኮ ሥርዓት እንደሚያውቁም ያመለክታል። ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ያሉትን የአይሁዳውያን ጽሑፎችም ያውቁ ነበር። ይሁንና፥ መጽሐፉ የተጻፈው በሮም ግዛት ውስጥ በሁሉም ስፍራ ለሚገኙ አይሁዶች አይመስልም። ነገር ግን ጸሐፊውን ለሚያውቁና እርሱም በቅርቡ ለመጎብኘት ለሚፈልጋቸው የተወሰኑ የአይሁድ ክርስቲያኖች የተጻፈ ይመስላል። እነዚህ አንባቢዎች ስለነበሩበት ስፍራ ሁለት ዓይነት አመለካከቶች ቀርበዋል። አንዳንዶች በመሥዋዕት ላይ ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱ አንባቢዎቹ ቤተ መቅደሱ በነበረበትና መሥዋዕቶች በሚቀርቡበት በፓለስታይን ምድር የነበሩ መሆናቸውን ያሳያል። ሌሎች ደግሞ እነዚህ አንባቢዎች ከፓለስታይን ውጪ የነበሩ አይሁዶች መሆናቸውን ይናገራሉ። ይሁንና፥ ሁሉም አይሁዳውያን ወንዶች በዓመት ሦስት ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም መሄድ ስላለባቸውና ሁሉም አይሁዳውያን የእንስሳት መሥዋዕቶችን ስለሚያቀርቡ፥ እነዚህ የአይሁዳውያን ማኅበረሰብ በየትኛውም ስፍራ ሊኖሩ ይችላሉ። በተጨማሪም፥ የዕብራውያን መልእክት ፓለስታይን የሚኖሩ አይሁዶች ቋንቋ በሆነው በአረማይክ ሳይሆን በግሪክ መጻፉ አይሁዶቹ ከፓለስታይን ውጭ የነበሩ መሆናቸውን የሚያሳይ ይመስላል። ብዙ ምሁራን እንደሚስማሙበት መጽሐፉ የተጻፈው በሮም ለነበሩ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ነው። ምክንያቱም ጸሐፊው በመጽሐፉ መጨረሻ አካባቢ ከኢጣሊያ ሰላምታ ያስተላለፉትን ሰዎች ጠቅሷል። በቀደምት ክርስቲያናዊ ጽሑፎች ውስጥ ከሁሉም በፊት የዕብራይስጥን ቋንቋ የተጠቀመው በሮም ውስጥ የነበረው ክሌመንት መሆኑ ይህን አሳብ ያጠናክረዋል። ሌሎች ደግሞ ብዙ አይሁዶች የነበሩባትን አሌክሳንደሪያን አጭተዋታል። ከሐዋርያት ሥራና ከቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደምንረዳው፥ ቀደምት የቤተ ክርስቲያን ዓመታት ለአይሁዳውያን ክርስቲያኖች በጣም አስቸጋሪዎች ነበሩ። ከ10-20 ዓመታት ለነበሩት የመጀመሪያዎቹ የቤተ ክርስቲያን ዓመታት፥ ክርስትና በዋናነት የአይሁዶች ሃይማኖት ነበር። እነዚህ አይሁዶች የወትሮው የአምልኮ ሥርዐታቸውን ብዙም ሳይለውጡ ክርስቶስ ለኃጢአታቸው የሞተ መሢሐቸው መሆኑን አምነዋል። ነገር ግን አሁንም በቤተ መቅደስ ውስጥ ያመልኩ (የሐዋ. 2፡46፥ 3፡1)፥ የእንስሳት መሥዋዕቶች ያቀርቡና የአይሁዶችን ባህላዊ ልምምዶች ሁሉ ይከተሉ ነበር። ከአብዛኞቹ አይሁዶች የሚለዩበት ዋናው ነገር አይሁዳውያን ክርስቲያኖች በክርስቶስ መሢሕነት ማመናቸው ነበር። ቆርኔሌዎስ ከተለወጠና የአንፆኪያ ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተች በኋላ፥ ቀስ በቀስ ክርስትና እየተለወጠ ሄደ፥ ለመጀመሪያ ግዜ አሕዛብ ክርስቲያኖች ይሆኑ ጀመር። እነዚህ አሕዛብ በቤተ መቅደስ ውስጥ የማምለክ ፍላጎት አልነበራቸውም። የእንስሳት መሥዋዕቶችን ካለማቅረባቸውም በላይ፥ የአይሁዶችን ባህል አይከተሉም ነበር። የአሕዛብ አማኞች ቁጥር በጣም ጥቂት ስለነበር፥ በመጀመሪያ አይሁዳውያን አማኞች እነዚህ ወደ ክርስትና ከመጡት ጥቂት አሕዛብ ጋር ግብግብ መግጠም አላስፈለጋቸውም ነበር። ይህ ሁሉ የተለወጠው በመጀመሪያው የጳውሎስ የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞ ወቅት ነበር። ጳውሎስና በርናባስ በትንሹ እስያ ውስጥ ወንጌልን እየሰበኩ ሲዞሩ፥ ጥቂት አይሁዶችና ብዙ አሕዛብ በወንጌል ማመን ጀመሩ። በዚህ ጊዜ የአሕዛብ አማኞች ቁጥር ቀስ በቀስ የአይሁዶችን አማኞች ቁጥር እያጠፈ ይሄድ ጀመር። የአሕዛብ አማኞች ቁጥር እየጨመረ ሲሄድ በአይሁዳውያን ክርስቲያኖች አእምሮ ውስጥ አንድ አስፈላጊ ጥያቄ ያቃጭል ጀመር። ይኸውም አሕዛብ በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነትን የሚያገኙት እንዴት ነው? የሚለው ነበር። አብዛኞቹ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች አሕዛብ በክርስቶስ ከማመናቸው በተጨማሪ ወደ አይሁድነት መቀየር አለባቸው ብለው ያምኑ ነበር። ስለሆነም አንዳንድ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች አሕዛብ አማኞች መገረዝና የብሉይ ኪዳን ሕጎችን መጠበቅ እንዳለባቸው ያስተምሩ ጀመር። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ባይጠቀስም፥ የቤተ መቅደስ፥ የምኩራብና የሌሎችም የአይሁዳውያን ባሕላዊ ልምምዶች ሁኔታ ከግርዘት ጋር አብሮ ሊነሣ የሚችል ጥያቄ ነበር። አሕዛብ ክርስቲያኖች ከተገረዙ፥ በቤተ መቅደስ ውስጥ ማምለክን ጨምሮ ሌሎች የአይሁዶች ባህሎችን ሁሉ መከተል ይኖርባቸው ነበር። ጴጥሮስና የቀድሞዎቹ ቤተ ክርስቲያን መሪዎች በዚህ ጉዳይ ላይ ለመወያየት በተሰበሰቡ ጊዜ፥ አሕዛብ በክርስቶስ በማመናቸው ብቻ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን እንደሚያገኙ ከስምምነት ላይ ተደረሰ። ወደ አይሁዳዊነት መለወጥና የብሉይ ኪዳንን የአምልኮ ልማዶች መቀጠል አያስፈልጋቸውም ነበር (የሐዋ. 15)። ይህም አሕዛብ ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት ለማድረግ ወደ አይሁድነት መለወጥ እንዳለባቸው ከሚያስተምረው የብሉይ ኪዳን አመለካከት የተለየ ነበር። ለመጀመሪያ ጊዜ በአይሁድ ማኅበረሰብ ውስጥ ክፍፍል ተፈጠረ። እስካአሁን ድረስ፥ ሌሎች አይሁዶች ክርስትና ሌላው የይሁዲነት የሃይማኖት ክፍል እንደሆነ ያስቡ ነበር። ምንም እንኳን የአይሁድ መሪዎች ክርስቲያኖችን ቢያሳድዱም (የሐዋ. 9)፥ ተራ አይሁዳውያን የናዝሬቱ ኢየሱስን የሚከተሉትን አይሁዶች ወደ መቀበሉ ያዘነብሉ ነበር (የሐዋ. 2፡47። ነገር ግን ከዚሁ የሐዋርያት ሥራ 15ቱ ውሳኔ በኋላ ክርስትና ከይሁዲነት የተለየ መሆኑ ጥርት ብሎ ታየ። ከዚህም የተነሣ፥ ለአይሁዳውያን ማኅበረሰብ ውጥረት እየጨመረ ይሄድ ጀመር። የማያምኑ አይሁዶች በሚያምኑት አይሁዶችና ክርስትና ላይ ይነሡ ጀመር። የማያምኑ አይሁዶች ክርስትና ከይሁዲነት የተለየ ሃይማኖት መሆኑን በመገንዘባቸው፥ ክርስቲያኖችን በግልጽ ይቃወሙ ጀመር። ይህ ተቃውሞ በተለይ አይሁዶችና አሕዛብ በአንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚያመልኩበት በትንሹ እስያ አይሎ ነበር። በኢየሩሳሌም፥ ሁሉም አማኞች በቤተ መቅደስ ውስጥ የሚያመልኩ በመሆናቸው፥ በመጀመሪያ አካባቢ ክርስቶስን በሚከተሉና በማይከተሉ ተራ አይሁዶች መካከል ግልጽ የሆነ ግጭት አልተከሰተም። በኋላ በ60ዎቹ ዓ.ም አካባቢ ግን በፓለስታይን ሁኔታው ተለወጠ። ይሁዳ ከሮም ቅኝ ግዛት እንድትወጣ የዜጎቿ ፍላጎት እየጨመረ መጣ። የተለያዩ የዐማፅያን ቡድኖች ተመሠረቱ። በአሕዛብ ላይ ጠንካራ ተቃውሞ በይፋ ይሰነዘር ጀመር። ይህ ጥላቻ በሌሎችም አውራጃ ዎች ተሰራጨ። ከፍተኛ የሀገር ወዳድነት ስሜት የሚሰማቸው አይሁዶች የመጡት ከፍልስጥኤም ነበር። በዚህ ጊዜ ክርስቲያን አይሁዶች አጣብቂኝ ውስጥ ገቡ። ክርስቲያን ወንድሞቻቸውና እኅቶቻቸውን ትተው አይሁዳዊነታቸውን ያጠብቃሉ? አይሁዶች ለብቻቸው አሕዛብ ደግሞ ለብቻቸው የሚያመልኩባቸው ሁለት የተለያዩ ባዕዳዊ እምነቶች በመመሠረት አይሁዶችን ከአሕዛብ መለየት የቱ ይሻል ይሆን? በሮም ላይ የሚካሄደውን ዐመፅ ካልደገፉ፥ አገራቸውን እንደ ካዱ ከሃዲዎች ተደርገው ይቆጠሩ ጀመር። የማያምኑ አይሁዶች ክርስቲያን አይሁዶች ከአሕዛብ ተለይተው ወደ ጥንታዊ አምልኮአቸው እንዲመለሱ በመጠየቃቸው ምክንያት በይሁዳና በሮም ግዛቶች ሁሉ ትልቅ ውጥረት ተፈጠረ። ይህን አሳብ ለመቀበል ያልፈለጉ አይሁዶች አይሁዳዊነታቸውን እንደ ካዱ ተቆጠሩ። ከዚህም የተነሣ ከአይሁድ ወንድሞቻቸው ስደት ይሰነዘርባቸው ጀመር። በተለይ በ66 ዓ.ም በኢየሩሳሌም የነበሩ አይሁዶች በሮም ላይ በማመፃቸው ይኸው ውጥረት ከላቀ ደረጃ ላይ ደረሰ። በዚህ ጊዜ በየትኛውም ስፍራ የሚገኙ አይሁዶች ዐመፁን የመደገፍ ወይም ከሮም ጋር የመተባበር ግዴታ ነበረባቸው። በ70 ዓ.ም ሮማውያን ከተማይቱን ቤተ መቅደሱን በመደምሰስ ዐመፁን እስከ ደመሰሱበት ጊዜ ድረስ ይኸው አመጽ አይሁዶችን ከፋፍሎአቸው ቆይቷል። የቤተ መቅደሱ መደምሰስ የብሉይ ኪዳንን የአምልኮ ሥርዓት ከፍጻሜ አደረሰው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በፖለቲካው (ጎሰኝነት፥ ብሔርተኝነት፥ ወዘተ…) ዓለም ውስጥ እየተከናወነ ያለው ነገር በቤተ ክርስቲያን ላይ እንዴት ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ግለጽ። ለ) ከመንፈሳዊ ቤተሰብህ ይልቅ ከጎሳህ ጋር መወገን ፈታኝ የሚሆነው እንዴት ነው? ሐ) በቤተ ክርስቲያን ወይም በሽማግሌዎች መካከል የሚፈጠረው ክፍፍል አንዳንድ ጊዜ ከጎሳዊ ውርስ ጋር እንዴት እንደሚዛመድ ግለጽ። መ) ጎሰኝነት፥ ዘር ወይም ቤተሰባዊ ውርስ እንዲካሄዱ መፍቀድ ክርስቶስ ከጸለየበት ( ዮሐ 17 አንብብ) እና ጳውሎስ ካስተማረው (ገላ. 3፡28-29) እውነት ጋር የሚጻረረው እንዴት ነው? ከኢየሩሳሌም መደምሰስ ቀደም ብሎ አማኝ አይሁዶች ወደ ይሁዲነት ሊመለሱ ውጥረት በበዛባቸው ወቅት፥ የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ለክርስቲያን አይሁዶች ይህንን ጠቃሚ መልእክት ጽፎላቸዋል። ብዙ አይሁዶች ወደ ጥንታዊቷ እምነታቸው ለመመለስ እያሰቡ ነበር። «ጥንታዊ ልምምዶቻችን ለሙሴ፥ ለዳዊት፥ ለኢሳይያስና ለሌሎችም ጥሩዎች ከነበሩ፤ በክርስቶስ ማመናችንን ትተን ወደ እንስሳት መሥዋዕቶች ብንመለስ ምን አለበት?» ብለው ያስቡ ነበር። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ይህንን መልእክት ያስተላለፈው ወደ ጥንታዊ የአምልኮ መንገዳቸው ለመመለስ ያስቡ ለነበሩት አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ነበር። ጀርባቸውን ለክርስቶስ ሰጥተው ወደ እንስሳት መሥዋዕቶች ቢመለሱ ምን ዓይነት አደጋዎች እንደሚጠብቃቸው ይነግራቸዋል፡፡ ክርስቶስ ለኃጢአታችው ስለ ሞተ፥ የእንስሳት መሥዋዕቶች ከእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ለማግኘት ሆነ እርሱን ለማምለክ ከእንግዲህ አማራጭ መንገዶች ሊሆኑ አይችሉም ነበር። ዛሬ እግዚአብሔር ሰዎችን የሚያድን ብቸኛው መንገድ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ኃጢአት ባቀረበው መሥዋዕት አማካኝነት ብቻ ነው። ጸሐፊው በቅርቡ ቤተ መቅደሱ እንደሚደመሰስና የእንስሳት መሥዋዕቶች የሚቀርቡበት ሥርዓት እንደሚወገድ የሚያሳይ ትንቢታዊ መልእክት አስተላልፎአል (ዕብ. 8፡13)። የዕብራውያን መልእክት የተጻፈበት ዘመንና ቦታ የውይይት ጥያቄ፡– ዕብ 13፡24 አንብብ። ጸሐፊው ሰላምታውን የሚልከው ከየት ሆኖ ነው? የዕብራውያን መጽሐፍ፥ «ከኢጣልያ የሆኑቱ

የዕብራውያን መልእክት ለማን፣ መቼ እና የት ተጻፈ Read More »

የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ

የውይይት ጥያቄ፡- ዕብራውያን 1፡1 አንብብ። ሀ) ስለ ጸሐፊው የተጠቀሰ ምን ነገር አለ? ለ) ሮሜ 1፡1 አንብብ። ይህ የሮሜ መጽሐፍ ስለ ጸሐፊው ከሚናገረው እንዴት ይለያል? ምንም እንኳን የዚህ መጽሐፍ የአማርኛው ርእስ «የሐዋርያው የጳውሎስ መልዕክት ወደ ዕብራውያን» ቢልም፥ ጳውሎስ የመጽሐፉ ጸሐፊ እንደሆነ አይናገርም። ይህ ጳውሎስ በሮሜም ሆነ በሌሎች መልእክቶቹ መግቢያ ላይ ራሱን ከሚያስታውቅበት ሁኔታ የተለየ ነው። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ በመልእክቱ ውስጥ ስሙን አልጻፈም። ይህ ከጥንታዊ የደብዳቤ አጻጻፍ ልማድ የተለየ ነው። መልእክቱ መጀመሪያ የተጻፈላቸው ሰዎች ጸሐፊውን ያውቁት እንደነበረ አይጠረጠርም። ምክንያቱም ጸሐፊው ሊጎበኛቸው እንዳልቻለ (ዕብ. 13፡19)፥ ዳሩ ግን አንድ ቀን ከጢሞቴዎስ ጋር ለመምጣት እንደሚፈልግ ይናገራል (ዕብ. 13፡23)። እንደ አለመታደል ሆኖ፥ መጽሐፉም ሆነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ማን እንደሆነ አይናገሩም። በአጠቃላይ፥ የጥንቶቹ ምሥራቃዊያን አብያተክርስቲያናት (ሶሪያ፥ ግብጽና ኢትዮጵያ) ጳውሎስ ይህን መልእክት እንደ ጻፈ ያምናሉ። ምዕራባዊያን አብያተ ክርስቲያናት (ሮም) ግን ጳውሎስ ይህን መልእክት እንደ ጻፈ አያምኑም። የዕብራውያንን መልእክት ቀረብ ብለን ስንመረምር፥ ስለ ጸሐፊው የሚከተሉትን ነገሮች እናገኛለን። ሀ) ጸሐፊው የብሉይ ኪዳንን የአምልኮ ሥርዓትና የአይሁዳዊያን ጽሑፎችን የሚያውቅ አይሁዳዊ ነበር። ለ) ጸሐፊው የብሉይ ኪዳንን የግሪክ ትርጉም የሚያውቅ፥ ከፍልስጥኤም ውጭ የተወለደ ሔለናዊ አይሁድ ነበር። ጸሐፊው የተጠቀመበት የግሪክ ቋንቋ የፓለስታይን አይሁዶችን ዓይነት ሁለተኛ ቋንቋ አይመስልም። እንዲሁም ደግሞ የዕብራውያንን ብሉይ ኪዳን የተጠቀመው የፓለስታይን እይሁዶች በሚጠቀሙበት መንገድ አይደለም። ሐ) ጸሐፊው የክርስቶስ ቀጥተኛ ደቀ መዝሙር አልነበረም። ክርስቶስን ባያየውም፥ ከክርስቶስ ጋር ከነበሩት ሰዎች ወንጌልን ሰምቷል (ዕብ. 2፡3)። (ማስታወሻ ፥ ይህም ጸሐፊው ጳውሎስ እንዳልሆነ የሚያሳይ ይመስላል። ምክንያቱም ጳውሎስ ወንጌሉን ከክርስቶስ እንጂ ከሌሎች ሐዋርያት እንዳልተቀበለ ይናገራል። ገላ. 1፡11-12 ተመልከት።) መ) ጸሐፊው በ70 ዓ.ም ቤተ መቅደሱ በሮማውያን ሲደመሰስ በሕይወት ነበር። የዕብራውያን መልእክት በተጻፈበት ወቅት፥ ቤተ መቅደሱ አገልግሎት እየሰጠ ከመሆኑም በላይ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓትም እንደ ቀጠለ ነበር። ነገር ግን፥ በቅርብ ጊዜ ይህ ሁኔታ እንደሚያከትም የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ገልጾአል (ዕብ. 8፡13)። ሠ) ጸሐፊው ይሁዲነትን የሚያውቅ ብቻ ሳይሆን፥ ሐዋርያነትና ቀደምት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች የተቀበሉት ዝነኛ ሰው ነበር። ረ) ጸሐፊው እስር ቤት ውስጥ የነበረውን ጢሞቴዎስን ያውቅ ነበር (ዕብ. 13፡23)። የዕብራውያንን መልእክት ተቀባዮች ከጢሞቴዎስ ጋር ለመጎብኘት ይፈልግ ነበር። ሰ) ጸሐፊው በአንባቢዎቹ በሚገባ ስለሚታወቅ፥ ማንነቱን ለመግለጽና ተደማጭነት ለማግኘት ስሙን መጥቀስ አላስፈለገውም። ሸ) ጸሐፊው አንባቢዎቹን ለመጎብኘትና ከእነርሱ ጋር ዳግም አብሮ ለመሆን ይፈልጋል። ነገር ግን በሆነ ምክንያት (ምናልባትም እስር ቤት ውስጥ በመሆኑ) ይህን ለማድረግ ሳይችል ቆይቷል። ለመሆኑ እነዚህን መመዘኛዎች የሚያሟላና የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ሊሆን የሚችል ሰው ማን ነው? የተለያዩ ምሁራን የሰጧቸው አስተያየቶች ከዚህ በታች ተዘርዝረዋል። ጳውሎስ፡ ከ400 ዓ.ም እስከ 1600 ዓ.ም፥ ብዙውን ጊዜ ለዚህ መጽሐፍ የተሰጠው ርእስ «የጳውሎስ መልእክት ለዕብራውያን» የሚል ነበር። ይህም የመልእክቱ ጸሐፊ ጳውሎስ ነው የሚል አመለካከት በስፋት እንዲታይ አድርጓል። ጳውሎስ የፈሪሳዊነት ትምህርት የተከታተለ በመሆኑ፥ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓትንና የአይሁዶችን የአስተሳሰብ መንገዶች በጥልቀት ሊያውቅ ይችል ነበር። ሌሎች ከላይ የቀረቡትን መመዘኛዎችንም እንዲሁ ያሟላል። የዚህ መልእክት ጸሐፊ ጳውሎስ ነው የሚሉ ምሁራን ጳውሎስ ስሙን ያልጠቀሰበት ምክንያት አይሁዳውያን ክርስቲያኖች መጽሐፉን ለማንበብና ትምህርቶቹን ለመቀበል ፈቃደኞች እንዲሆኑ በማሰብ ነው ይላሉ። በሐዋርያት ሥራ ውስጥ እንደተመለከተው፥ አይሁዶች ጳውሎስን ይጠራጠሩና ትምህርቱን ላለመቀበል ይሞክሩ ነበር። (ነገር ግን ከዕብራውያን መልእክት ውስጥ እንደምንመለከተው፥ የመልእክቱ አንባቢዎች ጸሐፊውን የሚያውቁት ይመስላል።) እነዚህ ምሁራን እንደሚሉት ምንም እንኳን ጳውሎስ በቀጥተኛ መገለጥ ከክርስቶስ ብዙ ነገር ቢቀበልም፥ ስለ ክርስቶስ አብዛኛዎቹን እውነታዎች የተማረው ከሐዋርያት ነበር ሲሉ ይከራከራሉ (1ኛ ቆሮ. 5፡1-3)። የጳውሎስ የቅርብ የሥራ ተባባሪ የሆነው ጢሞቴዎስ መጠቀሱ (ዕብ 13፡23)፥ የዚህ መልእክት ጸሐፊ ጳውሎስ ነው የሚለውን አስተሳሰብ ያጠነክራል። ጳውሎስ ይህን መልእክት እንዳልጻፈው የሚናገሩ ምሁራን የሚከተሉትን ነጥቦች ይጠቅሳሉ። ሀ) ጳውሎስ የመልእክቱ ጸሐፊ መሆኑን በመግቢያው ላይ አልጠቀሰም። ይህ የዕብራውያንን መልእክት ከሌሎች መልእክቶች ሁሉ ይለየዋል። አንባቢዎቹ ጸሐፊውን ስለሚያውቁ፥ መልእክቱን የጻፈው ጳውሎስ ቢሆን ኖሮ እንደ ሌሎች መልእክቶች ሁሉ ጸሐፊነቱን ይናገር ነበር። ለ) የዕብራውያን መልእክት የተጻፈበት የግሪክ ቋንቋ ሌሎች የጳውሎስ መልእክቶች ከተጻፉበት የተለየ ነው። ሐ) እንደ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ያሉ ጳውሎስ በተደጋጋሚ የሚጠቀምባቸው አገላለጾች በዚህ መጽሐፍ ውስጥ አይገኙም። መ) ቀደምት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች የመጽሐፉ ጸሐፊ ማን እንደሆነ አያውቁም። መልእክቱ በግልጽ በጳውሎስ ቢጻፍ ኖሮ ያውቁት እንደነበር አይጠረጠርም። በርናባስ፡ በ200 ዓ.ም ተርቱሊያን የተባለ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ ምሁር የዕብራውያን መጽሐፍ ጸሐፊ በርናባስ ነው ሲል ተናግሯል። በርናባስ ከላይ የተጠቀሱትን አብዛኞቹን መመዘኛዎች ያሟላል። በርናባስ ከሌዊ ወገን የተወለደ ሔለናዊ አይሁድ በመሆኑ፥ የብሉይ ኪዳንን የአምልኮ ሥርዓትና ይሁዲነትን በሚገባ ያውቃል (የሐዋ. 4፡36)። ያደገው በፍልስጥኤም ሳይሆን ቆጵሮስ ውስጥ ነበር። አይሁዶችና የቀድሞዋ ቤተ ክርስቲያን በርናባስን ያከብሩት ነበር። በርናባስ ከመጀመሪያዎቹ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት አንዱ አልነበረም። ነገር ግን ከሐዋርያት ጋር ጊዜ በማሳለፍ ስለ ክርስቶስ ሊያውቅ ችሏል። ምንም እንኳን በርናባስ በአሕዛብ መካከል የወንጌል ስርጭት ተግባራትን ቢያከናውንም፥ ትኩረት የሰጠው ለአይሁዶች ይመስላል። አጵሎስ፡ በ15ተኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ አካባቢ፥ ማርቲን ሉተር አጵሎስ ይህን መልእክት ሳይጽፍ እንዳልቀረ ተናግሯል። አጵሎስ በአሌክሳንደሪያ የተወለደ አይሁዳዊ ቢሆንም፥ አይሁዳዊ ክርስቲያን ነበር። አጵሎስ በጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተለይም በአሕዛብ ዘንድ በስፋት ይታወቅ ነበር። ከአይሁዶች ጋር በመከራከር የክርስቶስን መሢህነት ለማሳየት የቻለ ብቃት ያለው አገልጋይ ነበር (የሐዋ. 18፡24-28)። ይህ ጸሐፊ ብሉይ ኪዳንን የተረዳባቸው አንዳንድ መንገዶች በዚህ ጊዜ በኤሌክሳንደሪያ (ግብጽ) የነበሩ አይሁዶች ከሚጽፉበት ሁኔታ ጋር ተመሳሳይ ነበር። 4 ሉቃስ፡ አንዳንድ ምሁራን የዚህ መእልክት ጸሐፊ ሉቃስ እንደነበር ገልጸዋል። ይህንንም ያሉት ሉቃስ የጻፋቸውን የሐዋርያት ሥራና የሉቃስ ወንጌል የግሪክ ቋንቋና የአጻጻፍ ስልት ከዕብራውያን መልእክት ጋር በማነጻጸር ነው። ነገር ግን ሉቃስ አሕዛብ በመሆኑ እንዲህ ዓይነት መጽሐፍ ይጽፋል ተብሎ አይታሰብም። ጵርስቅላና አቂላ፡ አንዳንድ ምሁራን ጵርስቅላ በአቂላ እገዛ ይህን መጽሐፍ እንደ ጻፈች ያስባሉ። እነዚህ ሰዎች በሮም ከተማ ውስጥ የሚኖሩ አይሁዶች መሆናቸውን እናውቃለን። ጵርስቅላና አቂላ ክርስቲያናዊ እውነት የማስተማር ብቃት ነበራቸው። ምክንያቱም ከጳውሎስ የሁለተኛና ሦስተኛ የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞዎች ላይ በከፊል የተሳተፉ ከመሆናቸውም በላይ፥ አጵሎስን ለማስተማርና ለአገልግሎት ለማዘጋጀት ከፍተኛ ከአስተዋጽኦ አድርገዋል (የሐዋ. 18፡26)። ከጳውሎስ ጋር ረጅም ጊዜ በማሳለፋቸውና ሔለናዊ አይሁዶች በመሆናቸው የብሉይ ኪዳንን የአምልኮ ሥርዓትና የግሪኩን ብሉይ ኪዳን ሊያውቁ ይችሉ ነበር። በዕብራውያን ውስጥ እንደተገለጸው የክርስቲያኖች ሃይማኖታዊ ጉዞ በእነዚህ ሰዎች በግልጽ የሚታወቅ ነበር። ምክንያቱም ራሳቸው ከቦታ ቦታ ሲንቀሳቀሱ ኖረዋልና። እንዲሁም በሮም ለተወሰነ ጊዜ የቆዩ በመሆናቸው በዚያ አካባቢ ይታወቁ ነበር። ስለሆነም፥ ሰላምታ የሚልኩላቸው ጣሊያናውያን ወዳጆች ሊኖሯቸው ይችሉ ነበር። ምናልባትም ጵርስቅላ በመልእክቱ ውስጥ ስሟን ያልጠቀሰችው የሴቶች ጸሐፊነት በወቅቱ ተቀባይነት ስለማያገኝ ይሆናል። ይሁንና፥ ይህንን ንድፈ አሳብ ለመቀበልም ሆነ ላለመቀበል የሚያስችል ብዙ መረጃ የለንም። ሌሎች የተለያዩ ምሁራን የሰጡአቸው የአገልጋዮች ስሞች ቢኖሩም። በስፋት የሚታወቁት አምስቱ እነዚህ ናቸው። መልእክቱን የጻፉት ጳውሎስ ወይም በርናባስ የነበሩ ይመስላል። ነገር ግን የዕብራውያንን መልእክት ማን እንደ ጻፈው በትክክል ለማወቅ አልተቻለም። ይሁንና፥ መንፈስ ቅዱስ ቀደምት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች የዕብራውያን መልእክት ትምህርቶች አስፈላጊዎች መሆናቸውን አምነው የአዲስ ኪዳን አካል አድርገው እንዲቀበሉት አስችሏቸዋል። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ Read More »

የዕብራውያን መግቢያ

ከጥንት ዘመን ጀምሮ፥ ከሁሉም ባህሎች ውስጥ ማለት ይቻላል የእንስሳት መሥዋዕት የአምልኮ አካል ነበር። እግዚአብሔር የአዳምና የሔዋንን እርቃን ለመሸፈን እንስሳትን ከገደለበት ጊዜ አንሥቶ (ዘፍጥ. 3፡21)፥ የእንስሳት መሥዋዕቶች የአምልኮ አካል ነበሩ። ሰይጣን ሰዎች ሐሰተኛ አምልኮ እንዲያካሂዱ ለማድረግ የእንስሳት መሥዋዕትን ያበረታታል። ይህ ሐሰተኛ ልምምድ እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የገለጸውን እውነተኛ አምልኮ በመኮረጅ የሚከናወን ነው። ለመሆኑ በእንስሳት መሥዋዕትና በአማኝ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? ዛሬም መሥዋዕቶቹ አስፈላጊ ናቸው? አማኞች የእንስሳትን መሥዋዕት ያቀርቡ ዘንድ ጠንቋዮችን ወይም የተለዩ ካህናትን መጠቀማቸው ስሕተት ነውን? የዕብራውያን መጽሐፍ ለእነዚህ ጥያቄዎች ምን መልስ ይሰጣል? አይሁዶች በክርስቶስ ካመኑ በኋላም ሳይቀር የእንስሳት መሥዋዕት ሥርዓታቸውን ለመቀጠል ይፈልጉ ነበር። የዕብራውያን ጸሐፊ የእንስሳትን መሥዋዕት ለኃጢአት ይቅርታ (ወይም የመናፍስትን ቁጣ ለማብረድ፥ ለፈውስ ወይም ከእርግማን ለመከላከል) መጠቀሙ በኢየሱስ ክርስቶስ ሞት ላይ ያላንን እምነት የሚቃረን መሆኑን ያስረዳል። ሰዎች ድነትን (ደኅንነትን) ከማግኘታቸው በፊት በእንስሳት መሥዋዕትነት፥ በካህናት የሚያገኟቸውን ነገሮች በሙሉ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሞተበት ጊዜ እንደፈጸመልን የዕብራውያን ጸሐፊ ያስገነዝባል። በመሆኑም እነዚህን ጥንታዊ ሥርዓቶችና የእንስሳት መሥዋዕት መጠቀሙ ግለሰቡ በክርስቶስ ላይ ሕያው እምነት እንደሌለው ያመለክታል። የክርስቶስ ሞት ሌሎችን መሥዋዕቶች ሁሉ አላስፈላጊ አድርጓችዋል። የውይይት ጥያቄ፡- በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ የዕብራውያን መልእክት ርእስ ምንድን | 1 ነው? የመጽሐፉ ጸሐፊ ማን ነው ይላል ? አጠቃላይ መልእክቶች ምንም እንኳን በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የዕብራውያን መጽሐፍ ርእስ የጳውሎስን ጸሐፊነት ቢያሳይም፥ ይህ ርእስ በጥንታዊ መዛግብት ውስጥ አይገኝም። መጽሐፉ ራሱ በማን እንደ ተጻፈ አይናገርም። (ስለ ዕብራውያን መጽሐፍ ጸሐፊ በምንነጋገርበት ክፍል ስለዚሁ ጉዳይ ሰፋ አድርገን እንመለከታለን።) ስለሆነም የጥንት አማኞች የዕብራውያንን መጽሐፍ ከጳውሎስ መልእክቶች መጨረሻና ከቀጣይ ጽሑፎች መጀመሪያ ላይ አስቀምጠውታል። ምሁራን ከዕብራውያን እስከ ይሁዳ ያለውን ክፍል «አጠቃላይ መልእክቶች» ሲሉ ይጠራሉ። አጠቃላይ መልእክቶች የተባሉበትም ምክንያት መልእክቶቹ የተጻፉት ለግለሰብ (እንደ ቲቶ) ወይም ለአንድ ቤተ ክርስቲያን (እንደ 1ኛ ቆሮንቶስ) ሳይሆን፥ ለአጠቃላይ ክርስቲያኖች ወይም በዛ ላሉ ተአንባቢያን በመሆኑ ነው። (ለግለሰቦች የተላኩት 2ኛ ና 3ኛ ዮሐንስ መልእክቶች ከ1ኛ ዮሐንስ ጋር አብሮ ስለሚካተቱ፥ የአጠቃላይ መልእክቶች አካላት ተደርገው ተወስደዋል።) እነዚህ ስምንት መጻሕፍት የተጻፉት በአምስት የተለያዩ ጸሐፊያን ነው። (ማስታወሻ፥ አጠቃላይ መልእክቶች ከዕብራውያን ሳይሆን ከ1ኛ ጴጥሮስ እንደሚጀምሩ የሚያስቡ ምሁራን አሉ።) (ማስታወሻ፡ እነዚህ ስምንት መጻሕፍት በእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የቀረቡበት የአቀማመጥ ቅደም ተከተል ከአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ ይለያል። ይህም የሆነው የአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ የግሪክ መጽሐፍ ቅዱስን ቅደም ተከተል ስለሚከተልና እንግሊዝኛው መጽሐፍ ቅዱስ የላቲንን የመጽሐፍ ቅዱስ ቅደም ተከተል ስለሚከተል ነው።) የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ስምንቱን የአጠቃላይ መልእክቶች መጽሐፍ በቅደም ተከተል ዘርዝር። ለ) ስለ ዕብራውያን መልእክት ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት አንብብ። ስለ ጸሐፊው፥ ስለ መልእክቱ ተቀባዮችና የመጽሐፉ ዓላማ፥ ወዘተ. የቀረበውን ትምህርት ጠቅለል አድርገህ አቅርብ። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የዕብራውያን መግቢያ Read More »