የማርቆስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ እና ትርጓሜ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም ሊገባ ሲቃረብ በደብረ ዘይት አቅራቢያ ወዳሉት ወደ ቤተ ፋጌና ወደ ቢታንያ ደረሰ። በዚያም ከደቀመዛሙርቱ ሁለቱን ልኮ ማንም ያልተቀመጠበትን ውርንጫ እንዲያመጡለት አዘዛቸው ፤ “ጌታ ያስፈልገዋል” የሚል ቃልም ሰጣቸው። ውርንጫውንም አምጥተው ልብሳቸውን በላዩ ላይ ጣሉበት ፤ እርሱም ተቀመጠበት። ብዙ ሰዎችም ልብሳቸውንና ከዛፍ የቆረጡትን ቅርንጫፎች በመንገድ ላይ እያነጠፉ “ሆሣዕና! በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው! የምትመጣው የአባታችን የዳዊት መንግሥት የተባረከች ናት! ሆሣዕና በአርያም!” እያሉ በታላቅ ደስታ ይዘምሩ ነበር። ጌታም ወደ ኢየሩሳሌም ገብቶ ወደ መቅደሱ ከገባ በኋላ ሁሉንም ተመልክቶ ምሽት ስለነበር ወደ ቢታንያ ተመለሰ። በማግስቱም ከቢታንያ ሲወጡ ጌታ ተራበ። ከሩቅ ቅጠል ያላት በለስ አይቶ ፍሬ ይገኝባት እንደሆነ ብሎ ወደ እርሷ ሄደ ፤ ነገር ግን የፍሬ ወቅት ስላልነበረ ከቅጠል በቀር ምንም አላገኘባትም። ጌታም ወደ በለሷ ተመልክቶ “ከእንግዲህ ወዲህ ለዘላለም ማንም ከአንተ ፍሬ አይብላ” በማለት ረገማት። ደቀመዛሙርቱም ይህን ሰሙ።
ይህ ክፍል የመሲfhን ትክክለኛ ማንነትና እግዚአብሔር ከሕዝቡ የሚጠብቀውን ፍሬ በግልጽ የሚያሳይ ነው። ጌታ ኢየሱስ በውርንጫ ላይ ተቀምጦ መግባቱ ትልቅ ትርጉም አለው። በጥንት ዘመን ነገሥታት ለጦርነት ሲወጡ በፈረስ ላይ ይቀመጡ ነበር ፤ ለሰላም ሲመጡ ግን በአህያ ወይም በውርንጫ ላይ ይቀመጡ ነበር። ጌታችን ኢየሱስ የሰላም ንጉሥ መሆኑንና የመጣውም በኃይል ሊገዛ ሳይሆን በሕይወቱ ሊያገለግል መሆኑን በተግባር አሳየን። ሕዝቡ “ሆሣዕና” (አሁን አድን!) እያሉ መጮኻቸው ፥ እርሱ ነጻ አውጪ መሲሕ መሆኑን ማመናቸውን ያሳያል።
ለምሳሌ፦ አንድ ታላቅ እንግዳ ወደ ቤታችን ሲመጣ ምንጣፍ እንደምናነጥፍ ሁሉ ፤ የኢየሩሳሌም ሕዝብም ልብሳቸውን ማነጠፋቸው ለንጉሡ ያላቸውን ፍጹም አክብሮትና ተገዢነት ይገልጻል። ሆኖም ጌታ ወደ መቅደሱ ገብቶ “ሁሉን ተመለከተ” የሚለው ቃል ፥ ዛሬም ጌታ በሕይወታችንና በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ያለውን እውነተኛ ሁኔታ በትኩረት እንደሚመለከት ያስታውሰናል።
የበለሷ መርገም ደግሞ እጅግ ጥልቅ የሆነ መንፈሳዊ መልእክት አለው። በለስ ቅጠል ካወጣች ፍሬ መያዝ ነበረባት ፤ ቅጠል ኖሮ ፍሬ አለመገኘቱ ግን “ግብዝነትን” ወይም “ሐሰተኛ መልክን” ያሳያል። በለሷ በወቅቱ የነበረችውንና ውጫዊ የሃይማኖት ሥርዓት ያላት ነገር ግን ውስጣዊ የቅድስና ፍሬ የሌላትን ኢየሩሳሌምን ትወክላለች። ጌታ በለሷን መርገሙ ፥ ፍሬ በሌለው የሃይማኖት ሕይወት ላይ የሚመጣውን ፍርድ ያሳየናል።
ለምሳሌ፦ አንድ ሱቅ በሩ ላይ “ትኩስ ዳቦ አለ” የሚል ማስታወቂያ ለጥፎ ፥ ገብተን ስንጠይቅ ግን ምንም ባዶ ቢሆን ምን ይሰማናል? ልክ እንደዚሁ ፥ ክርስቲያን ነን ብለን የምንመላለስ ግን የፍቅር ፥ የሰላም ፥ የትሕትና ፍሬ በሕይወታችን የማይታይ ከሆነ ጌታን እናሳዝናለን። ጌታ ዛሬም በሕይወታችን የሚፈልገው የሚያምር “ቅጠልን” (ንግግርንና ሥርዓትን) ብቻ ሳይሆን ፥ የሚበላ “ፍሬን” (ተግባራዊ ሕይወትን) ነው። ይህ ክፍል የሚያስተምረን ጌታን እንደ ሰላም ንጉሥ ልንቀበለውና ፥ በሕይወታችንም ለእርሱ የሚሆን ፍሬ ልናፈራ እንደሚገባን ነው።
ተግባራዊ የውይይት ጥያቄዎች
👉ኢየሱስ በአህያ ውርንጭላ ላይ ሆኖ መግባቱ ስለ ሰላማዊ ንግሥናው ምን ይናገራል?
👉ሕዝቡ “የሚመጣው የአባታችን የዳዊት መንግሥት ቡርክት ናት” ማለታቸው ምን ዓይነት ተስፋ እንደነበራቸው ያሳያል?
👉ኢየሱስ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ሁሉን ከተመለከተ በኋላ ወደ ቢታንያ የተመለሰው ለምንድን ነው?
👉የበለሷ መርገም ከኢየሱስ ርኅራኄ ጋር እንዴት ይጣጣማል?
👉”የበለስ ወራት አልነበረም” ተብሎ ሳለ ኢየሱስ ፍሬ መፈለጉና መርገሙ ፍትሐዊ ነውን?
👉በለሷ የእስራኤል ሃይማኖታዊ ሕይወት ምሳሌ የሆነችው በምን መንገድ ነው?
👉ይህ ተአምር በኢየሱስ አገልግሎት ውስጥ ብቸኛው የማጥፋት (Destructive) ተአምር መሆኑ ምን ትርጉም አለው?
👉”ለጌታ ያስፈልገዋል” ተብሎ ሲነገራቸው የውርንጭላው ባለቤቶች መፍቀዳቸው ምን ያስተምራል?
👉ሆሣዕና ማለት “አሁን አድን” (Save now) ማለት መሆኑ ከኢየሱስ ቤዛነት ጋር እንዴት ይያያዛል?
👉ኢየሱስ የበለስ ዛፍን መጠቀሙ ከብሉይ ኪዳን ነቢያት (ለምሳሌ ኤርምያስ) ምሳሌያዊ ተግባር ጋር እንዴት ይነጻጸራል?