የማርቆስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ እና ትርጓሜ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ክፍል ውስጥ እጅግ አስፈሪና አስቸኳይ ስለሆነ ጊዜ ይናገራል። “የጥፋት ርኩሰት” የማይገባው ቦታ ላይ ቆሞ ሲታይ ፥ በይሁዳ ያሉት ወደ ተራሮች እንዲሸሹ ያሳስባል። ይህ ሽሽት ምን ያህል አጣዳፊ እንደሆነ ሲገልጽ ፥ በሰገነት ላይ ያለ ዕቃውን ለመውሰድ ወደ ቤት እንዳይወርድ ፥ በእርሻ ላይ ያለ ደግሞ ልብሱን ለመውሰድ ወደ ኋላ እንዳይመለስ ይነግረናል። በተለይም ነፍሰ ጡር ለሆኑና ለሚያጠቡ እናቶች መከራው እንደሚከብድ ፥ ሽሽቱም በክረምት እንዳይሆን መጸለይ እንደሚገባ ያሳስባል። ይህ መከራ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ሆኖ የማያውቅና ወደፊትም የማይሆን ታላቅ መከራ ነው። ሆኖም እግዚአብሔር ስለ መረጣቸው ቅዱሳን ሲል እነዚያን ቀናት ባያሳጥራቸው ኖሮ ማንም ሊድን ባልቻለ ነበር። በዚያ ጊዜ “ክርስቶስ እዚህ አለ” ወይም “እዚያ አለ” የሚሉ ሐሰተኛ መሲሐውያንና ነቢያት ተነሥተው ቢቻልስ የተመረጡትን እንኳ ለማሳት ምልክትና ድንቅ እንደሚያደርጉ ጌታ አስቀድሞ አስጠነቀቀን።
ይህ ክፍል በታሪክ ደረጃ በሰባኛው ዓመተ ምሕረት የኢየሩሳሌምን መፍረስ የሚያመለክት ቢሆንም ፥ በመንፈሳዊ ትርጉሙ ግን በዘመናት መጨረሻ ስለሚመጣው ታላቅ መንፈሳዊ ውጊያ ያስተምረናል። “የጥፋት ርኩሰት” ማለት ለእግዚአብሔር ቅድስና በማይገባ ስፍራ ላይ የሚቆም የርኩሰትና የክፋት አምልኮ ነው። ጌታ “ሽሹ” ሲለን ከክፋትና ከሐሰት ትምህርት በቶሎ ልንለይ እንደሚገባን ለማሳየት ነው።
አንድ ምሳሌ እንመልከት፦ አንድ ትልቅ ሕንጻ ላይ የእሳት አደጋ መከሰቱን የሚገልጽ ደወል ቢደወል ፥ በዚያ ሕንጻ ውስጥ ያለ ሰው “ቆይ መጀመሪያ ፎቶዎቼን ላዝግጅ” ወይም “ወርቅና ብሬን ልሰብስብ” አይልም። ብቸኛው ትኩረቱ ነፍሱን ማዳን ነው። ጌታም መንፈሳዊ አደጋ ሲመጣ ልባችን በምድራዊ ንብረትና ምቾት መታሰር እንደሌለበት ሊያሳየን ፈልጎ ነው። የእኛ “ተራራ” የተባለው ጌታ ራሱ ነውና መሸሸጊያችንን በእርሱ ላይ ልናደርግ ይገባል።
ጌታ ቀኖቹን አሳጠረ ማለቱ በፈተናው መካከል እንኳ የእግዚአብሔር ምሕረትና ጥበቃ እንደማይለየን ያሳያል። ሐሰተኛ መሲሐውያን ድንቅና ተአምር ማድረጋቸው ደግሞ ፥ እምነታችን በሚታዩ ምልክቶች ላይ ሳይሆን በማይለወጠው በእግዚአብሔር ቃል ላይ ብቻ ሊመሠረት እንደሚገባ ያስጠነቅቀናል። ዛሬም ብዙ የሚያሳስቱ ድምፆች ቢኖሩም ፥ እኛ ግን አስቀድሞ የነገረንን የጌታን ቃል ይዘን ልንነቃና ልንጠነቀቅ ይገባል። መዳናችን የሚረጋገጠው በምናየው ተአምር ሳይሆን በጠበቅነው እውነት ነው።
ተግባራዊ የውይይት ጥያቄዎች
👉”የጥፋት ርኩሰት” የሚለው ሐረግ ከዳንኤል ትንቢት አንጻር ምን ትርጉም አለው?
👉በይሁዳ ያሉ ወደ ተራራ እንዲሸሹ የታዘዙት ለምንድን ነው?
👉”በቤት ጣሪያ ላይ ያለ… ሊወስድ አይውረድ” የሚለው አገላለጽ የክስተቱን አጣዳፊነት እንዴት ያሳያል?
👉ለርጉዞችና ለሚያጠቡ ለምን ወዮላቸው ተባለ?
👉እግዚአብሔር ዘመኑን ያሳጠረው ስለማን ሲል ነው?
👉ሐሰተኞች መሲሖች የሚያሳዩአቸው ምልክቶች ከእውነተኛ ተአምራት በምን ይለያሉ?
👉ኢየሱስ “ሁሉን አስቀድሜ ነገርኋችሁ” ማለቱ ለደቀመዛሙርቱ ምን ዓይነት ዝግጅት ይሰጣል?
👉በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ መባሉ ስለ ሁኔታው አስቸጋሪነት ምን ይገልጻል?
👉”ለአንባቢው ያስተውል” የሚለው የማርቆስ ማስታወሻ ለምን አስፈለገ?
👉የየተመረጡትስ ቢሆን ለምን ለስሕተት ሊዳረጉ ይችላሉ?