የሉቃስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ እና ትርጓሜ
የሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ አራት የሚጀምረው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ ከዮርዳኖስ በመመለስና በመንፈስ መሪነት ወደ ምድረ በዳ በመሄዱ ነው። ይህ ክፍል እጅግ ጥልቅ የሆነ መንፈሳዊ ትርጉም አለው፤ ምክንያቱም የመጀመሪያው አዳም በገነት ውስጥ ሆኖ በሰይጣን ተሸንፎ ሳለ፣ ሁለተኛው አዳም የተባለው ክርስቶስ ግን በምድረ በዳ መከራና ረሃብ ውስጥ ሆኖ ጠላትን ድል ማድረጉን ያሳያል። ጌታችን ለ አርባ ቀናት ምንም ሳይበላ መቆየቱ ሰብዓዊነቱንና ለፈተና የተጋለጠ መሆኑን ሲያመለክት፣ ፈተናው የመጣው ደግሞ በሰውኛ አቅሙ ደክሞት በነበረበት በዚያ የመጨረሻ ሰዓት ነበር። ይህም ጠላት ሁልጊዜ የእኛን ደካማ ጎንና የተቸገርንበትን ጊዜ እንደሚጠባበቅ ያስገነዝበናል።
የመጀመሪያው ፈተና የቀረበው በሥጋዊ ፍላጎት ላይ ነበር። ሰይጣን “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ ይህን ድንጋይ እንጀራ እንዲሆን በል” አለው። ይህ ፈተና ጌታችን መለኮታዊ ኃይሉን ለገዛ ሥጋዊ ፍላጎቱ እንዲጠቀምበት የቀረበ ግፊት ነበር። ጌታችን ግን “ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም ተብሎ ተጽፏል” በማለት በመለኮታዊ እውነት መለሰለት። ይህም ሕይወታችን የሚመነጨውና የሚጠበቀው ከምግብ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ቃል መሆኑን ያረጋገጠበት ነው። ሁለተኛው ፈተና ደግሞ በዓለማዊ ሥልጣንና ክብር ላይ ያተኮረ ነበር። ሰይጣን የዓለምን መንግሥታት ሁሉ አሳይቶ “ለእኔ ብትሰግድልኝ ይህ ሁሉ ለአንተ ይሆናል” አለው። ጌታችን ግን “ለጌታ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ ተብሎ ተጽፏል” በማለት የአምልኮና የሥልጣን ባለቤት እግዚአብሔር ብቻ መሆኑን በመሰከር ጠላትን አሳፈረው።
ሦስተኛውና የመጨረሻው ፈተና የነበረው የእግዚአብሔርን ጥበቃ የመፈተን ጉዳይ ነበር። ሰይጣን ጌታችንን ወደ መቅደስ ጫፍ ወስዶ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ ከዚህ ወደ ታች ራስህን ወርውር” አለው፤ ሌላው ቀርቶ መዝሙር 91ን በመጥቀስ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሽፋን ለመስጠት ሞከረ። ጌታችን ግን ጠላት ቃሉን ለራሱ ዓላማ እንዳያጣምም በመከልከል “ጌታን አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ተጽፏል” በማለት ድል አደረገው። ሰይጣንም ፈተናውን ሁሉ በጨረሰ ጊዜ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ። ይህ ታሪክ የሚያስተምረን ፈተናን የምናሸንፈው በገዛ ጥበባችን ሳይሆን በታተመውና በተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን ነው። ክርስቶስ እኛ የምንፈተንበትን መንገድ ሁሉ አልፎ ድል ስለነሳልን፣ እኛም በእርሱ ሆነን ድል አድራጊዎች ነን።
ተግባራዊ የውይይት ጥያቄዎች
👉መንፈስ ቅዱስ ኢየሱስን ወደ ፈተና መምራቱ (ቁ. 1) ስለ ፈተናና ስለ መንፈሳዊ እድገት ምን ያስተምረናል?
👉ኢየሱስ በቃለ እግዚአብሔር ሰይጣንን ማሸነፉ ዛሬ ለኛ ምን አይነት ተግባራዊ አርአያ ነው?
👉ሦስቱ የፈተና አይነቶች ከሰው ልጅ መሰረታዊ ደካማ ጎኖች ጋር እንዴት ይያያዛሉ?
👉ሰይጣን ራሱ መጽሐፍ ቅዱስን (መዝሙር 91) ጠቅሶ መፈተኑ (ቁ. 10-11) ምን አይነት ጥንቃቄ እንድናደርግ ያስገድደናል?
👉ኢየሱስ “ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በንጀራ ብቻ አይኖርም” ማለቱ ለቁሳዊ ፍላጎታችን ምን ትርጉም ይሰጣል?
👉“ዲያብሎስ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ” (ቁ. 13) የሚለው ቃል ወደፊት ስለሚመጣው መንፈሳዊ ትግል ምን ፍንጭ ይሰጣል?
👉በፈተና ጊዜ የመንፈስ ቅዱስ ሙላት ያለው ሚና ምንድን ነው?
👉ኢየሱስ በምድረ በዳ 40 ቀን መቆየቱ ከእስራኤል የ40 ዓመት ጉዞ ጋር እንዴት ይነጻጸራል?