የመንፈስ ቅዱስ የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ንጋቷ መንፈስ ቅዱስ በሕይወቷ እንዲሠራ የምትፈልግ ንቁ ክርስቲያን ነበረች። እግዚአብሔር እንዲጠቀምባት ትፈልግ ስለነበር ከእግዚአብሔር ጋር ያላትን ግንኙነት የሚያበላሽ ማንኛውም ዓይነት ኃጢአት በሕይወቷ እንዳይኖር ትጠነቀቅ ነበር። ነገር ግን አንድ ቀን በፍትወት ኃጢአት ወደቀች፤ መንፈስ ቅዱስ ወቀሳትና ወደ መዝሙር 51፡11 በመሄድ ዳዊት መንፈስ ቅዱስ ከሕይወቱ እንዳይወሰድበት እግዚአብሔርን የለመነበትን ጸሎት አነበበች። እርሷም እግዚአብሔር መንፈሱን እንዳይወስድባት ለመነች።
የውይይት ጥያቄ፦
- ሀ) ንጋቷ የጸለየችው ጸሎት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነው ብለህ ታስባለህ? አሳብህን አብራራው።
- ለ) ክርስቲያኖች ኃጢአትን በሚያደርጉበት ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ትቷቸው ይሄዳል የሚለውን አሳብ የሚደግፍ የአዲስ ኪዳን ጥቅስ አለን? ካሉ ጥቀሳቸው።
- ሐ) ጸሎታችን መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት እንዲኖረው የምንፈልገው ለምንድን ነው?
ንጋቷ ይህን ያደረገችው በቅንነት ሲሆን ጸሎቷም እጅግ የተቀጣጠለና ጽኑ ነበር። ነገር ግን ጸሎቷ ትክክለኛ ነበር? ይህ ጸሎት እንደ ዳዊት ላሉ የብሉይ ኪዳን ቅዱሳን ትክክል ነበር። ነገር ግን ከኢየሱስ ሞት በኋላ ለሚኖሩ ክርስቲያኖች ሕይወት መንፈስ ቅዱስ ሊወሰድ እንደሚችል መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራልን?
ከዚህ በታች መንፈስ ቅዱስ በብሉይ ኪዳን ከሠራባቸው መንገዶች ጋር ተመሳሳይ የሆኑ በርካታ አገልግሎቶች በአዲስ ኪዳን ቢኖሩም ያሉትን ልዩነቶችም እንዳሉ እንመለከታለን። አሮጌው ኪዳን ከአዲስ ኪዳን የተለየ ነው። በብሉይ ኪዳን የነበረው የመንፈስ ቅዱስ ሥራ በአዲስ ኪዳን ካለው የመንፈስ ቅዱስ ሥራ የተለየ ነው። በዘመናት ሁሉ ውስጥ ያለውን የእግዚአብሔርን ቃልና ዕቅዶች በመረዳት ማመንና መጸለይ ከፈለግን በሁለቱ ኪዳኖች መካከል ያለውን ተመሳሳይነትና ልዩነት ማስተዋል አለብን። የልዩነቶቹን ማዕከላዊ ስፍራ የያዘው የመንፈስ ቅዱስ ሥራና አገልግሎት ነው።
መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስተምረን መንፈስ ቅዱስ በጰንጠቆስጤ ዕለት ሲወርድ በመንፈስ ቅዱስና በአማኞች መካከል በሚኖረው ግንኙነት አንድ ታላቅ ለውጥ ተከናወነ። የአዲስ ኪዳን ትምህርት እንደሚያመለክተው ከጰንጠቆስጤ ዕለት ጀምሮ አንድ ክርስቲያን ኃጢአት ባደረገ ጊዜ ሁሉ መንፈስ ቅዱስ ትቶት አይሄድም የሚል ይመስላል።
እግዚአብሔር መሐሪና ታጋሽ ስለሆነ ሥነ-መለኮታዊ ግድፈታችንን አይቆጥርብንም። በሥነ-መለኮታዊ ይዘቱ ፍጹም ያልሆነ ነገር ብንነግረውም እንኳ ማዳመጡን አይተውም። ባይሆንማ ኖሮ በመረዳታችን መቶ በመቶ ትክክል የሆንን ስለሌለን እግዚአብሔር ከጸሎታችን የትኛውንም አይሰማም ነበር። ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል የሚለውን በትክክል ብንረዳና ለእምነታችን መሠረት ብናደርገው ምንኛ የተሻለ ይሆናል። የእግዚአብሔርን ቃል ለማጥናትና የሚያስተምራቸውን ትምህርቶች ለመረዳት ጊዜ ባለመስጠታችን፤ አንድ ሰው «ጓደኛዬ ነው» እያለ እየተመካብን ስማችንን ለማወቅ እንኳ ጥረት ሳያደርግ ሲቀር የሚሰማንን ዓይነት ስሜት እግዚአብሔር ይሰማዋል። የዚህ የጥናት መምሪያ መጽሐፍ አንዱ ዓላማ መንፈስ ቅዱስን የበለጠ እንድናውቀው ማስቻል ነው።
የውይይት ጥያቄ፦ ኤር. 31፡31-34፤ ኢዩ. 2፡28-32 አንብብ።
- ሀ) እነዚህ ጥቅሶች እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን የሚያደርገው በብሉይ ኪዳን ካደረገው የተለየ እንደሚሆን የሚያሳዩት በምን በምን መንገዶች ነው?
- ለ) እነዚህ ጥቅሶች በመንፈስ ቅዱስ አሠራርም ለውጦች እንደሚኖሩ የሚያሳዩት እንዴት ነው?
የሚያድግ መገለጥ (Progressive Revelation)
የእግዚአብሔርን ቃል በምናጠናበት ጊዜ ልናስታውሳቸው የሚገቡ ሁለት አስፈላጊ ነገሮች አሉ። በመጀመሪያ የእግዚአብሔር ፍጹም እውነት በአንድ ጊዜ የተሰጠ ሳይሆን በጊዜ ሂደት ቀስ በቀስ እየተገለጠ የመጣ እንደነበር ማስታወስ ይገባናል። ይህ በሥነ-መለኮት ትምህርት ቋንቋ የሚያድግ መገለጥ ይባላል። ይህም እግዚአብሔር በዘመናት ውስጥ ፈቃዱን ደረጃ በደረጃ መግለጡን ያሳያል።
ለምሳሌ፦ አንድ ሳይንቲስት የአንድ ዓመት ሴት ልጁን ለማስተማር ጀመረ እንበል፦ «ልጄ ሆይ፥ ዛሬ ስለ አቶሚክ ኃይል የሚታወቁ እውነቶችን በሙሉ እነግርሻለሁ» በማለት የተማራቸውንና ለብዙ ዓመታት ያጠናቸውን ነገሮች በሙሉ ሊነግራት ቢሞክር የሚገባት ይመስላችኋል? አይገባትም። እንደ ልጅ ልትረዳው የምትችለው የተወሰነ የእውቀት ገደብ አለ። ነገር ግን በዓመታት ውስጥ እያደገች ስትሄድ ስለ ሳይንስና ስለ አቶሚክ ኃይል ትንሽ በትንሽ ቢያስተምራት አባቷ የሚለውን ነገር ቀስ በቀስ መረዳት ትችላለች።
ይህ ምሳሌ እግዚአብሔር ሰዎችን እንዴት እንደሚያስተምር ይገልጻል። እግዚአብሔር ለሙሴም ሆነ ለእስራኤላውያን ስለ ራሱም ሆነ ስለ ፈቃዱ ያለውን እውነት በሙሉ በአንድ ጊዜ አልነገራቸውም። ይህን ለማድረግ ሞክሮ ቢሆን ኖሮ አይገባቸውም ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር ፈቃዱን በዘመናት ውስጥ ደረጃ በደረጃ ገለጠላቸው። በእርግጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለሰው ልጅ ያለውን ሁሉ ገልጦ እስከሚጨርስ እግዚአብሔር ከ1500 ዓመታት በላይ ወስዶበታል። በዚህ ጊዜ ሁሉ እግዚአብሔር ሰዎች ስለ እርሱ ያላቸው እውቀት ደረጃ በደረጃ እንዲጨምር አድርጎላቸዋል።
ይህ ሐቅ መጽሐፍ ቅዱስን እንዴት እንደምንረዳ በብዙ አቅጣጫ ያሳያል። በመጀመሪያ በብሉይ ኪዳን ሕዝብ ሕይወት ውስጥ ስለነበሩ፥ እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላላገሠጻቸው በኋላ ግን ለእኛ ስሕተት መሆናቸው ስለተነገረን ጉዳዮች እናነባለን። ለምሳሌ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ቅዱሳን አብዛኞቹ ከአንድ በላይ ሚስቶችን አግብተው ነበር። ይህ ተግባር የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዳልሆነ በአዲስ ኪዳን ሰፍሮ ይታያል። ሆኖም ግን እግዚአብሔር የብሉይ ኪዳን ቅዱሳንን ሌሎች ነገሮችን ያስተምራቸው ነበር። ከአንድ በላይ የሆኑ ሚስቶችን የማግባት ልምምድን መቃወም ግን በእነዚህ ትምህርቶቹ ውስጥ አልተካተተም ነበር። እግዚአብሔር ወደ መንፈሳዊ ብስለት ሲያመጣንና ሲያሳድገን የሚያደርገው እንደዚሁ ነው። በተወሰኑ የሕይወታችን ጉዳዮች ደረጃ በደረጃ ይሠራል። በአንድ ጊዜ ፍጹም የሆነ ለውጥን ለማምጣት አይሞክርም።
የውይይት ጥያቄ፦ እግዚአብሔር በሕይወታችን ያሉትን ችግሮቻችንን በአንድ ጊዜ ከማስወገድ ይልቅ ረጅም ጊዜ ወስዶ በትዕግሥት ሲያከናውነው የሚያሳዝነን (የሚፈትነን) ለምንድን ነው?
በሁለተኛ ደረጃ አንዳንድ ቁልፍ የሆኑ የእምነት አስተምህሮዎች የተገለጡት በጊዜ ሂደት ውስጥ ነው። እግዚአብሔር እውነትን ሁሉ የገለጠው በአንድ ጊዜ ሳይሆን ደረጃ በደረጃ ነው። ይህንን ስለ መንፈስ ቅዱስ ስናጠና እንመለከተዋለን። የሥላሴን ትምህርትና የመንፈስ ቅዱስን ህልውና በሚገባ የምንረዳው እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን የሰጠውን መገለጥ ስንረዳ ብቻ ይሆናል። መንፈስ ቅዱስ በብሉይ ኪዳን የነበረውን ሥራ ለመረዳት የአዲስ ኪዳን መገለጥ ያስፈልገናል።
በሦስተኛ ደረጃ ልንመለከተው የሚገባን እግዚአብሔር በዘመናት ውስጥ ነገሮችን ያከናወነበትን (የፈጸመበትን) አንዳንድ መንገዶች መለወጡን ነው። በብሉይ ኪዳን ዘመን የሠራበት መንገድ በአዲስ ኪዳን ከሠራበት መንገድ በአንዳንድ ሁኔታዎች ይለያል። ለምሳሌ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር በተቀዳሚ የሠራው በአይሁዳውያን በኩል ነበር። በአዲስ ኪዳን ደግሞ እግዚአብሔር አንዳችም የዘር ልዩነት ሳያደርግ ከሕዝቡ ሁሉ ጋር በእኩልነት ይሠራል። በብሉይ ኪዳን ባለን መረዳት ላይ ብቻ ብንመሠረት በትውልዳችን አሕዛብ ስለሆንን ማናችንም የእግዚአብሔር ሕዝብ አካል መሆን አንችልም ነበር።
ይህ እውነት ለመንፈስ ቅዱስ ያለንን መረዳትም ይነካል። በብሉይ ኪዳን ዘመን እግዚአብሔር መንፈሱን ለተወሰኑ ሰዎች ለተወሰነ አገልግሎት ይሰጥና በኋላ ላይ መልሶ ይወስድ ነበር። ዳዊት መንፈስ ቅዱስ እንዳይወሰድበት የለመነው ለዚህ ነበር (መዝ. 51፡11)። በአዲስ ኪዳን ግን የመንፈስ ቅዱስ ህልውና ለክርስቲያኖች ሁሉ በዋስትና ተሰጥቷል፤ ለዚህም ነው መንፈስ ቅዱስ ከእውነተኛ ክርስቲያኖች የሚወሰድበት ወቅት ስለመኖሩ ምንም መረጃ የሌለን። ይህ ከሆነ የብሉይ ኪዳን የመንፈስ ቅዱስ አሠራር ከብሉይ ኪዳን ዘመን ወዲህ እስከ ዛሬ ስለተለወጠ እግዚአብሔር መንፈሱን እንዳይወስድብን እንደ ዳዊት መጸለይ አያስፈልገንም።
መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም ልንጠቀምባቸው የሚገቡ መመሪያዎች
- የቤተ ክርስቲያን ዋና ትምህርትን ወይም ልምምድን በአንድ ጥቅስ ላይ ብቻ ፈጽሞ አትመሥርቱ፦ ስለመረጣችሁት ርእስ የሚናገሩ ሌሎች ተዛማጅ ጥቅሶችን ተመልከቱ። አብዛኛዎቹ የሐሰት ትምህርቶች የሚመጡት ብዙ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ቃል በአጠቃላይ የሚያስተምረውን ባለመመልከታቸው ነው። አንድ ወይም ሁለት ጥቅሶችን ብቻ መዘው ይወስዱና እነዚያን ጥቅሶች ብቻ ያስተምራሉ። ለምሳሌ በአንዳንድ አገሮች ክርስቲያኖች በማር. 16፡18 የተጻፈውን አሳብ አንድ ሰው መንፈሳዊ መሆኑን ወይም አለመሆኑን ለመፈተን ይጠቀሙበታል። መርዛማ እባቦችን ወደ ቤተ ክርስቲያን በማምጣት እባቦችን ይነካሉ። ብዙዎች በእባብ ተነድፈው ይሞታሉ። ብዙዎቻችን ይህ ጥቅስ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ የተጻፈበት ምክንያት ለዚህ ዓላማ እንዳልሆነ እንስማማለን። በተመሳሳይ መንገድ ብዙ ክርስቲያኖች አንድ ወይም ሁለት ጥቅሶችን ከብሉይ ኪዳን ወይም ከእምነት ታሪክ ወስደው ስለ መንፈስ ቅዱስ የተሳሳተ መረዳት ውስጥ ይገባሉ።
- ሁልጊዜ አንድን ክፍል ለመተርጐም በአዲስ ኪዳን ውስጥ የሚገኙ ጠቃሚ ጥቅሶችን በተለይም መልእክቶችን ተጠቀሙ፦ ብሉይ ኪዳንን ለመረዳትና ለመተርጐም አዲስ ኪዳንን ተጠቀሙ። ደግሞ የሐዋርያት ሥራንና ወንጌላትን ለመተርጐም መልእክቶችን ተጠቀሙ። እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን የሰጣቸው እውነቶች በተለይ በመልእክቶች በግልጽ ስለተቀመጡ (ስለተብራሩ) እግዚአብሔር አስቀድሞ የሰጣቸውን መገለጦች ለመረዳት ከሁሉ የላቁ ማብራሪያዎች ናቸው። የሥነ-መለኮት ትምህርቶችን በብሉይ ኪዳንና በሐዋርያት ሥራ ላይ ብቻ እንዳትመሠረቱ ተጠንቀቁ። አንድን ጥቅስ በምትተረጉሙበት ጊዜ የሁሉንም መጻሕፍት ትምህርቶች ግምት ውስጥ አስገቡ።
የውይይት ጥያቄ፦
- ሀ) የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት፦ ማቴ. 5፡38፤ ማር. 9፡27 (ከማቴ. 5፡21-48 ጋር አስተያይ)። ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ጋር ካላስተያየናቸው በስተቀር እነዚህ ጥቅሶች በተሳሳተ መንገድ ሊተረጐሙ የሚችሉት እንዴት ነው?
- ለ) የእግዚአብሔርን ቃል በአጠቃላይ በመመልከት ፈንታ አንድ ወይም ሁለት ጥቅሶችን ብቻ በመምረጥና በመመልከት የአስተሳሰብ ስሕተት የሠሩ አንዳንድ ክርስቲያኖችን በምሳሌነት ጥቀስ።
መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት ልናስተውለው የሚገባ ሁለተኛው ዋና እውነት ያንን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እግዚአብሔር መጀመሪያ ለሕዝቡ በሰጠበት ወቅት የነበረውን ልዩ ሁኔታ ማሰብ ነው። ለምሳሌ በኤርምያስ 31 ላይ እግዚአብሔር የቀድሞውን ኪዳን አዲስ ከሚመጣው ኪዳን ጋር ያነፃፅራል። ስለዚህ አንድን ጥቅስ በምንመለከትበት ወቅት ያ ጥቅስ ለብሉይ ኪዳን ብቻ የተሰጠና በአዲስ ኪዳን ግን የተለየ እንደሆነ ወይም ለሁለቱም ኪዳኖች እኩል ይሠራ እንደሆነ መመልከት ተገቢ ነው። በኢዩኤል 2 ላይ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን የሚጠቀምበት መንገድ እንደሚለወጥ ተጽፏል። መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠው ለተወሰኑ ሰዎች ብቻ ሳይሆን ለእግዚአብሔር ሕዝቦች በሙሉ ይሆናል። ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ በብሉይ ኪዳን ከነበረው ሚና በተለየ መልክ በአዲስ ኪዳን እንደሚያከናውን መጠበቅ እንችላለን።
በክርስቲያኖች መካከል ከፍተኛ የመረዳት ልዩነት ከሚታዩባቸው መጻሕፍት አንዱ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ነው። በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ አንዳንድ ጥቅሶች ብቻቸውን ካየናቸው ሌላ ትርጉም የሚሰጡና ትክክለኛ ትርጉማቸውን ለማግኘት በመልእክቶች ብርሃን ልናያቸው የሚገቡ አሉ። የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ የሽግግር መጽሐፍ ነው። ከብሉይ ኪዳን ወደ አዲስ ኪዳን የተደረገውን ሽግግር ያሳየናል። አንድ አዲስ መንግሥት ወደ ሥልጣን ሲመጣ አዲሱ የመንግሥት መመሪያ በግልፅ እስኪሰፍር ድረስ ጊዜ ይወስዳል። አንዳንድ ጊዜ አዲስ ሕገ-መንግሥት እስኪጻፍ ድረስ ጊዜያዊ መመሪያዎች ይወጣሉ። በተመሳሳይ መንገድ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን ዘመን የሚሆነውን ፖሊሲ (መመሪያ) በሙላት እስኪገልጥ ድረስ የነበረውን የሽግግር ሂደት በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እናያለን። ስለዚህ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍን በመልእክቶች ውስጥ ባሉ ግልጽ ትምህርቶች ብርሃን ልንረዳው ያስፈልጋል።
የውይይት ጥያቄ፦ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከቱ፦ ማቴ. 5፡21–48። እግዚአብሔር በአንድ ዘመን ከሰጠው መገለጥ በተከታዩ ዘመን የሚሰጠው የሚለየው በምን መንገድ ነው?
እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን በተመለከተ በዚህ መንገድ ያደረገውን ለውጥ ለመረዳት ከብሉይ ኪዳን ዘመን ጀምረን ኢየሱስ በወንጌላት ውስጥ ያስተማረውን፥ ቀጥሎም በሐዋርያት ሥራ ውስጥ ያለውን፥ በመጨረሻም በመልእክቶች ውስጥ የተሰጡትን ትምህርቶች ደረጃ በደረጃ መመልከት ያስፈልጋል። በዚህ መንገድ መንፈስ ቅዱስ በብሉይ ኪዳን ያደረገውንና አሁንም በማድረግ ላይ ያለውን ተመሳሳይ ሁኔታ እንመለከታለን። በተጨማሪ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መንፈስ ቅዱስ እየሠራ ካለው የተለየ ነገርም እንመለከታለን።
መንፈስ ቅዱስ በብሉይ ኪዳን
ባለፈው ሳምንት አንዱ አምላክ በህልውናው ከአንድ በላይ አካል እንዳለው የሚያመለክቱ ሁኔታዎች በብሉይ ኪዳን እንዳሉ አይተናል። ነገር ግን ስለ ሥላሴ ግልጽ ትምህርት ለማግኘት በአዲስ ኪዳን ላይ እንደገፋለን። አንዱ አምላክ እግዚአብሔር አብ፥ እግዚአብሔር ወልድና እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የተባሉ ሦስት አካላት እንዳሉት ግልጽ የሚያደርግልን አዲስ ኪዳን ነው። የመንፈስ ቅዱስንም ህልውና (አካልነት) የሚያሳየን አዲስ ኪዳን ነው።
በብሉይ ኪዳን ውስጥ በግልጽ ባይቀመጥም እንኳ መንፈስ ቅዱስ ያከናወነው ከፍተኛ ድርሻ ነበረው። መንፈስ ቅዱስ በብሉይ ኪዳን በሚታወቅበት ስሙ «የእግዚአብሔር መንፈስ» እየተባለ ከብዙ ጊዜ በላይ ተጠቅሷል። የእነዚህ ጥቅሶች ትኩረት ከእግዚአብሔር አብ በተለየ አካል ላይ አይደለም። ዋናው ትኩረት በሥራው በሚገለጠው የእግዚአብሔር ኃይል ላይ ነው። «የእግዚአብሔር መንፈስ» ነገሮችን ለማከናወን ዘወትር በሥራ ላይ ነው። መንፈስ ቅዱስ ተብሎ ሲጠቀስ እግዚአብሔርን እንደ ፈጣሪ፥ ተቆጣጣሪ፥ ገላጭና አስቻይ አድርጎ ለማሳየት ነው። ከብሉይ ኪዳን ብቻ መንፈስ ቅዱስ ከእግዚአብሔር አብና ከእግዚአብሔር ወልድ የተለየ አካል መሆኑን ለማረጋገጥ አንችልም፤ ይህን ማረጋገጫ የምናገኘው ከአዲስ ኪዳን ነው። ይህንን ከአዲስ ኪዳን ካረጋገጥን በኋላ ግን ወደ ብሉይ ኪዳን ተመልሰን በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበረውን የመንፈስ ቅዱስን ሥራ በግልጽ መረዳት እንችላለን።
1. መንፈስ ቅዱስ ፈጣሪ፣ ሕይወት ሰጭና የፍጥረት ተቆጣጣሪ ነው
የውይይት ጥያቄ፦ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት፦ ዘፍ. 1፡2፤ 2፡7፤ መዝ. 33፡6፤ ኢዮብ 26፡13፥ 33::4። መንፈስ ቅዱስ በፍጥረት ሥራ ውስጥ ዋና ተሳታፊ እንደነበር እንዴት ያሳዩናል?
ፍጥረታትን በመፍጠር ሥራ ውስጥ የሥላሴ አባላት በሙሉ ዋና ተሳታፊ ነበሩ። እግዚአብሔር አብ እንደ ፈጣሪ ተመልክቷል (ዘፍ. 1፡1)። ኢየሱስ ክርስቶስም የነገሮች ሁሉ ፈጣሪ መሆኑ ተጽፏል (ቆላ. 1፡16-17)። በተጨማሪም መንፈስ ቅዱስ በፍጥረት ሥራ ውስጥ ተካፋይ እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ያሳየናል (ዘፍ. 1፡2፤ 2:7)።
መንፈስ ቅዱስ በመጀመሪያው የፍጥረት ሥራ ውስጥ ተካፋይ ነበር። በዘፍ. 1፡2 ላይ «የእግዚአብሔር መንፈስ» በውኃ ላይ ሰፍፎ እንደነበር ተጽፏል። በዚህ ቦታ የምናየው ነገር የእግዚአብሔር መንፈስ ሥራውን ለማከናወን እንደ ርግብ ሲያንዣብብ ነው። መንፈስ ቅዱስ በዚህ ሥራ ላይ የተሳተፈው እንዴት እንደነበር የፍጥረት ታሪክ በዝርዝር ባይናገርም እግዚአብሔር በተናገረ ጊዜ ተዘጋጅቶ ሲያንዣብብ የነበረው መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር የተናገረውን መሥራት እንደቀጠለ እንገምታለን። በመዝ. 33፡6 የሰማይ ሠራዊቶች በአፉ እስትንፋስ እንደተሠሩ ተጽፏል። የእግዚአብሔር «እስትንፋስ» እና የእግዚአብሔር «መንፈስ» ተመሳሳይ አሳብ መያዛቸውን በብሉይ ኪዳን በእርግጠኝነት ባናገኘውም መንፈስ ቅዱስ በፍጥረት ሥራ እንደተንቀሳቀሰ ያሳየናል።
በዘፍጥረት 2፡7 እግዚአብሔር በሰው ላይ የሕይወት እስትንፋስ እፍ እንዳለበት ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው እንደሆነ እናያለን። ቀደም ብሎ እግዚአብሔር ለእንስሳትና ለአእዋፍ ሕይወትን የሰጠው ቃል በመናገር ነበር። እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በሚፈጥርበት ጊዜ ግን የተለየ ነገር አደረገ፤ የራሱን ሕይወት «እፍ አለበት»። ብዙ ሊቃውንት የሰው ሕይወት ከሌሎች እንስሳት ሕይወት የተለየው ሕይወቱ የተገኘው በቀጥታ ከእግዚአብሔር እስትንፋስ ስለሆነ ነው ይላሉ። ቀደም ብለን የተመለከትነውን ካስታወስን በዕብራይስጥ ቋንቋ «መንፈስ» እና «እስትንፋስ» ተብለው የተተረጎሙት ቃላት አንድ ናቸው። በዚህም ሰው «መንፈስ» እንዲኖረው ያደረገው መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ፍንጭ እናገኛለን። ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት እንዲያደርግ ያስቻለው «መንፈስ» ወይም «እስትንፋስ» ነው።
ለ. መንፈስ ቅዱስ አዲስ ሕይወትን በመፍጠር የማያቋርጥ ተግባር ውስጥ ተሳታፊ ነው፦ መዝ. 104፡24-30 ሕይወት ያላቸው ነገሮች ሁሉ በሺህ የሚቆጠሩ በባሕር የሚገኙ ዓሣዎች እንኳ በሙሉ ለህልውናቸው በእግዚአብሔር ላይ እንዴት እንደሚደገፉ ይናገራል። የምግባቸውና የህልውናቸው ምንጭ እግዚአብሔር ነው። መሞት ወይም መኖር እንዳለባቸው የሚወስነው እግዚአብሔር ነው። በቁጥር 30 እንደምንመለከተው እግዚአብሔር መንፈሱን ሲልክ አዲስ ፍጥረታት ይፈጠራሉ፤ ምድርም በፍጥረታት ትሞላለች።
በኢዮብ 33፡4 መንፈስ ቅዱስ በሰው ሕይወት ውስጥ አዲስ ሕይወትን ስለመፍጠሩ እናነባለን። በምድር ላይ አንድ ዓይነት የሆኑ ሁለት ሰዎችን አናገኝም። የእያንዳንዱን ግለሰብ አፈጣጠር ተቆጣጣሪ መንፈስ ቅዱስ ነው። ይህ ማለት ልክ እንደተወለድን የሚኖረንን ልዩ ተፈጥሮ የሚወስን መንፈስ ቅዱስ ነው ማለት ነው። በተጨማሪ በቤተሰባችን፥ በማኅበረሰባችንና በሕይወት ዘመናችን ሁሉ በሚኖሩን ልምምዶች የሚፈልገውን ዓይነት ሰው እንድንሆን የሚመራን መንፈስ ቅዱስ ነው።
የውይይት ጥያቄ፦
- ሀ) ከአንድ ቤተሰብ ተወልደው የተለያዩ ባሕርያት ያላቸውን ልጆች በምሳሌነት ጥቀስ።
- ለ) መንፈስ ቅዱስ እያንዳንዳችንን ልዩ ለማድረግ የሚችል ታላቅ ኃይል ያለው አምላክ መሆኑን ይህ እንዴት ያሳየናል?
- ሐ) አሁን ባለህበት የሕይወት ደረጃ ላይ ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሕይወትህን የተቆጣጠረባቸውን የተለያዩ ጊዜያትና ሁኔታዎች ግለጽ።
- መ) እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለእግዚአብሔር ክብር ልዩ የሆንክ ሰው ስላደረገህ ጊዜ ወስደህ ክብርና አምልኮን ስጥ።
ሐ. ለፍጥረት ሥርዓት ያበጀላቸው መንፈስ ቅዱስ ነው (ኢሳ. 40፡12-14)፦ የትም ስፍራ ስንመለከት በፍጥረት ውስጥ ሥርዓትን እናያለን። ዓለም እንደ አንድ ቅንጅት እንድትንቀሳቀስ በፍጥረት ያለ ነገር ሁሉ የየራሱ ክልልና ልዩ ተግባር አለው። ይህ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ እንደሆነ በኢሳይያስ መጽሐፍ እንመለከታለን። የባሕርን ስፋት በመለካት እንዳያልፉም ድንበር አበጀላቸው። ከምድር በላይ ያለውንና ከዋክብትንና ፕላኔቶችን የያዘውን ሰማይ እንደዘረጋ ተዘግቧል። እያንዳንዱን ከዋክብት በስም እንደሚያውቃቸው እንኳ ተጽፏል። እያንዳንዱ ተራራ፥ ኮረብታ፥ ጅረትና ዛፍ ሁሉ መንፈስ ቅዱስ በዓላማ ባለበት እንዲሆን ተደርጓል።
የውይይት ጥያቄ፦ መዝ. 19፡1-6 አንብብ።
- ሀ) ይህ መዝሙር ፍጥረት በሥርዓቱና በውስጡ ምን እንደሚያደርግ ይናገራል?
- ለ) ይህ በሕይወትህ እውነት እንደሆነ እንዴት አየኸው?
በመዝ. 19 ላይ ፍጥረት እንደሚናገር ተጽፏል። ፈጣሪ የሆነ እግዚአብሔር ስለመኖሩ ለሰው ልጅ ይመሰክራሉ፤ ደግሞም እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ። ሰማያትና ምድር እግዚአብሔርን ያከብራሉ። ይህ ከመንፈስ ቅዱስ ተቀዳሚ ሥራ ጋር የሚስማማ ነው። መንፈስ ቅዱስ ትኩረትን በመሳብ ለራሱ ክብርን የሚፈልግ አይደለም። ይልቁኑ ለፍጥረታት ውስጣዊ ሥርዓትን በሚሰጥበት ወቅት የፍጥረት ሁሉ ምንጭ የሆኑት እግዚአብሔር አብና ወልድ እንዲከበሩ ይፈልጋል (ዮሐ. 16፡13-14)።
መ. የታሪክ አካሄድ የእግዚአብሔርን ዕቅዶች ተፈጻሚ ያደርግ ዘንድ የሚቆጣጠር መንፈስ ቅዱስ ነው (ኢሳ. 34፡16)፦ ኢሳይያስ 34 እግዚአብሔር ኤዶምን እንደሚቀጣ የሚናገር ነው። ምክንያቱም በ586 ዓ.ዓ ለይሁዳ ጥፋት ከባቢሎናውያን ጋር ተባባሪዎች ስለነበሩ ነው። እግዚአብሔር የኤዶምን ምድር የበረሃ አእዋፍና እንስሳት ብቻ የሚገኙበት ምድረ-በዳ እንደሚያደርጋት ተናገረ (ቁጥር 11)። ይህን ተግባራዊ የሚያደርግ ማን ነው? በቁጥር 16 እንደምንመለከተው የበረሃ እንስሳት በተባለበት ስፍራ እንዲገኙ የሚያደርግ የእግዚአብሔር መንፈስ እንደሆነ ይናገራል። ይህ የሚያመለክተን የእግዚአብሔር መንፈስ እግዚአብሔር በኤዶም ላይ በሚያመጣቸው ሌሎች ፍርዶችም (ቅጣቶችም) ውስጥ ተሳታፊ እንደነበረ ነው። እግዚአብሔር የታሪክ ተቆጣጣሪ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ቢያሳየንም (ለምሳሌ ዳን. 4፡17)፥ ይህ የኢሳይያስ ጥቅስ የሚያሳየን መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔርን ዓላማዎች ለማስፈጸም ነገሮችን በመቆጣጠር ዋና ተሳታፊ መሆኑን ነው።
2. መንፈስ ቅዱስ ሰው የእግዚአብሔርን ሥራ ይፈጽም ዘንድ በችሎታና በብርታት የሚሞላ ነው
የውይይት ጥያቄ፦ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት፦ ዘፀ. 31፡1-11፤ 35፡30-35፤ 1ኛ ዜና 28፡12፤ ሐጌ 2:5፤ ዘካ. 4፡6።
- ሀ) በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ልዩ ችሎታ እንደተሰጣቸው የተነገረላቸውን የተለያዩ ሰዎችን ጥቀስ።
- ለ) የተሰጣቸው ልዩ ችሎታዎች ምን ምን ነበሩ?
- ሐ) የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ውጤት ናቸው ብለህ የምታምናቸውንና የምታውቃቸው ሰዎች ያሏቸውን አንዳንድ ልዩ ችሎታዎች ዘርዝር። እነዚህ ችሎታዎች የመንፈስ ቅዱስ ስጦታዎች ጭምር እንጂ ተፈጥሯዊ ችሎታዎች ብቻ እንዳልሆኑ እንዴት አመንክ?
እግዚአብሔር አንድ ልዩ ሥራ ሊኖረው ወይም ለክብሩ የሚሆን አንድ ነገር ሲያደርግ ያንን ሥራ ይፈጽሙ ዘንድ አንዳንድ ሰዎችን ልዩ ችሎታ የሚሰጣቸው መንፈስ ቅዱስ ነበር። በብሉይ ኪዳን በርካታ ሰዎች በዚህ መንገድ ኃይል ተቀብለዋል። የመገናኛውን ድንኳን ለመሥራት እንዴት እንደሚያከናውኑ (እንደሚሠሩ) ሌሎችን ለማስተማር በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የተሰጣቸው ሰዎች ባስልኤልና ኤልያብ ነበሩ (ዘፀ. 31፡1-11)። ዳዊት የሰለሞንን ቤተ መቅደስ ንድፍ እንዲያወጣ መንፈስ ቅዱስ ረድቶት ነበር (1ኛ ዜና 28፡12)።
ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር ኢያሱና ዘሩባቤል የተባሉ ሁለት መሪዎችን በኢየሩሳሌም ያለውን ቤተ መቅደሱን እንደገና ይገነቡ ዘንድ ጠራቸው። ይህ መሠራት ያለበት እንዴት ነበር? ለእነርሱና በእስራኤል ለነበሩ ጥቂት ሰዎች ቤተ መቅደሱን ለመገንባት ብርታትና ችሎታ የሰጣቸው ማን ነበር? የእግዚአብሔር ቃል መንፈስ ቅዱስ እንደነበር ይነግረናል። መንፈስ ቅዱስ በእግዚአብሔር ሕዝብ መካከል ስለነበረ በቁጥር ጥቂት ቢሆኑም እንኳ የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነውን ቤተ መቅደሱን ሠሩ። እግዚአብሔር ከመሪዎችም ጋር ነበር። ሥራው ለእግዚአብሔር ክብር ይሆን ዘንድ እግዚአብሔር ሊቀ ካህናቱን ኢያሱንና አገረ ገዢውን ዘሩባቤልን ሥራውን ይቆጣጠሩ ዘንድ አስቻላቸው (ሐጌ 2፡4-5)።
እግዚአብሔር ብዙ ጊዜ ከሕዝቡ ተፈጥሯዊ ችሎታ በላይ የሆነ ሥራ ወደ ሕዝቡ ያመጣል። እነዚህ ልዩ ተግባራት ለእግዚአብሔር ክብር የታቀዱ ናቸው። እነዚህ የማይቻሉ ነገሮች የሚፈጸሙት እንዴት ነው? ከእነዚህ ጥቅሶች የምንማረው በመንፈስ ቅዱስ የማስቻል ኃይል እንደሚፈጸሙ ነው። ሥራውን ይሠሩ ዘንድ እግዚአብሔር ልዩ ስጦታ ያላቸውን ሰዎች ይልካል። የማይቻል የሚመስሉ ተግባራትን ይፈጽሙ ዘንድ መሪዎችን በብርታት ያቆማል።
የውይይት ጥያቄ፦ በእናንተ ቤተ ክርስቲያን ይህ ሲፈጸም ያያችሁት እንዴት ነው?
3. ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ጻድቅና ቅዱስ ይሆኑ ዘንድ ያስተማራቸው መንፈስ ቅዱስ ነው
የውይይት ጥያቄ፦ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት፦ ነህ. 9፡19-20፤ መዝ. 143፡10። እነዚህ ጥቅሶች የእግዚአብሔር ሰዎች በታማኝነት መንገድ እንዲሄዱ መንፈስ ቅዱስ ስለሚሠራው ሥራ ምን ያስተምረናል?
በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑት እስራኤላውያን የእግዚአብሔርን ሙሉ ፈቃድ ለመረዳት እንደ መነሻ የሚያነቡት ሙሉ መጽሐፍ ቅዱስ በእጃቸው አልነበረም። በተለይ እስራኤላውያን በምድረ-በዳ በነበሩበት ጊዜ ይህ እውነት ታይቷል። ይመራቸው ዘንድ የእግዚአብሔር ክብር ቀን ቀን በደመና ማታ ማታ ደግሞ በእሳት ዓምድ ከእነርሱ ጋር ነበር። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ማፈንገጥ በሚችሉበት አጋጣሚ ውስጥ ሆነው እግዚአብሔርን ደስ በማሰኘት መኖር የሚችሉበትን የእግዚአብሔር ፈቃድ ማወቅ የነበረባቸው እንዴት ነው?
በነህምያ 9፡20 የእግዚአብሔር ሕዝቦች በምድረ-በዳ በሚንከራተቱበት ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ይመራቸው እንደነበር ተጽፏል። ይህ እንዴት ተፈጸመ? እግዚአብሔር ሕዝቡ እንዲሠራ የሚፈልገውን ነገር ሙሴ በትእዛዝ መልክ በሚያስተላልፍበት ወቅት በአመዛኙ ይመራው የነበረው መንፈስ ቅዱስ ነበር። ይህም በዘፀአት፥ በዘሌዋውያን፥ በዘኁልቁና በዘዳግም የምናገኛቸውን በርካታ ትእዛዛትን ይጨምራል።
ይህ ግን ለሙሴና በምድረ-በዳ ለነበረ የእስራኤል ሕዝብ ብቻ የሆነ አልነበረም። በመዝ. 143፡10 እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት ፈቃዱን እንዲያስተምረውና ምቹ በሆነው በእግዚአብሔር መንገድ እንዲመራው ዳዊት ይጸልያል።
4. የእግዚአብሔርን ፈቃድና እውነት በተለያዩ ነቢያት አማካኝነት ለሕዝቡ የገለጠው መንፈስ ቅዱስ ነው
የውይይት ጥያቄ፦ ዘኁል. 24፡2-4፤ 2ኛ ሳሙ. 23፡1-2፤ 2ኛ ዜና 15፡1-2፤ ነህ. 9::30፤ ኢሳ. 61፡1-4፤ ሕዝ. 2፡2-3፤ 11፡24-25፤ 37፡1-4፤ ሚክ. 3፡8፤ ዘካ. 7፡8-12 አንብብ። መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የገለጠባቸውን የተለያዩ ሰዎች ጥቀስ።
ስለ እግዚአብሔር ስናስብ ከሚያስደንቀን እውነቶች አንዱ እርሱ ሁልጊዜ ዝም የሚልና ድብቅ ሳይሆን ሁልጊዜ ነቅቶ የሚሠራ ለሕዝቡም የሚናገር መሆኑ ነው። ለእግዚአብሔር ሕዝብ የእግዚአብሔርን መልእክት የሚናገር የትኛው የሥላሴ አካል ነው? ከላይ ከተጠቀሱት ጥቅሶች የምንመለከተው እግዚአብሔር ለሕዝቡ የተናገረው በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት መሆኑን ነው።
የእግዚአብሔርን መልእክት መንፈስ ቅዱስ ለሕዝቡ የተናገረባቸው ሁለት መንገዶች አሉ።
- በመጀመሪያ፦ የብሉይ ኪዳን ሰዎች ዛሬ ብሉይ ኪዳን ብለን የምንጠራውን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲጽፉ ልባቸውን ያንቀሳቀሰው መንፈስ ቅዱስ ነበር (2ኛ ጴጥ. 1፡20-21)። በብሉይ ኪዳን ነቢያት የተጻፉት በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ለመሆናቸው በአዲስ ኪዳን በበርካታ ስፍራዎች ተገልጧል (ለምሳሌ፦ የሐዋ. 1፡16፤ 4፡25)።
- በሁለተኛ ደረጃ፦ የምንመለከተው በየዘመናቱ ለነበሩ የእግዚአብሔር ሰዎች በተለያዩ መልእክተኞች ውስጥ አልፎ የተናገረው መንፈስ ቅዱስ ነው። ነቢዩ በለዓም፥ ዳዊት፥ ነቢዩ ኢሳይያስ፥ ነቢዩ ሕዝቅኤልና ነቢዩ ሚክያስ እንደ ምሳሌ የሚጠቀሱ ናቸው።
የውይይት ጥያቄ፦ በብሉይ ኪዳን የታዩትንና ከዚህ ቀደም የተነጋገርንባቸውን የተለያዩ የመንፈስ ቅዱስ አገልግሎቶች ከልስ።
- ሀ) ከእነዚህ አገልግሎቶች መካከል ዛሬም ቢሆን መንፈስ ቅዱስ የሚጠቀምባቸው የትኞቹን ነው? መንፈስ ቅዱስ እነዚህን አገልግሎቶቹን ሲቀጥል ያየሃቸውን አንዳንድ ምሳሌዎች ጥቀስ።
- ለ) ከእነዚህ አገልግሎቶች መካከል በአንዳንድ መንገድ ከብሉይ ኪዳን ዘመን በኋላ ለየት ያሉት የትኞቹ ናቸው? ለመልስህ የሰጠኸውን ምክንያት ግለጽ።
ምንጭ፦ «የመንፈስ ቅዱስ የጥናት መምሪያና ማብራሪያ»፣ በቲም ፌሎስ ተጽፎ፣ በጌቱ ግዛው የተተረጎመ እና በኤስ አይ ኤም (SIM) ጽሑፍ ክፍል የተዘጋጀ ነው። ለዚህ ድንቅ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው። ይህን ጽሑፍ ኮፒ እና ፕሪንት አድርጎ መጠቀም ይቻላል፤ ሆኖም ጽሑፉን መለወጥና ለሽያጭ ማዋል በሕግ የተከለከለ ነው።
ተባረኩ በጣም አመሰግናለሁ በብዙ ጠቅሞኛል።