የሉቃስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ እና ትርጓሜ
በቄሳር አውግስጦስ ትእዛዝ መላው ዓለም እንዲጻፍ በታወጀ ጊዜ፣ ዮሴፍና ማርያም ከገሊላ ናዝሬት ተነስተው ወደ ዳዊት ከተማ ወደ ቤተልሔም ተጓዙ። ይህ ታሪካዊ ክስተት እግዚአብሔር የዓለምን ገዥዎች ትእዛዝ እንኳን ሳይቀር ለገዛ መለኮታዊ ዕቅዱና ለትንቢቱ ፍጻሜ እንዴት እንደሚጠቀምበት ያሳየናል። በዚያም ሳሉ የማርያም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ፤ በከተማዋም የእንግዳ ማረፊያ ስላልነበረ የዓለም መድኃኒት በግርግም ተወለደ። የሰማይና የምድር ጌታ በጨርቅ ተጠቅልሎ በከብቶች መመገቢያ ውስጥ መተኛቱ፣ የእግዚአብሔርን ዝቅ ማለትና ለሰው ልጅ ያለውን ጥልቅ ፍቅር በታላቅ ትሕትና የገለጠበት ድንቅ ምስጢር ነው።
በዚያው ምድር መንጋቸውን በሌሊት ሲጠብቁ ለነበሩ እረኞች የጌታ መልአክ ተገለጠላቸው፤ የጌታም ክብር በዙሪያቸው በራ። እረኞች በወቅቱ ማኅበረሰብ ዘንድ የተናቁና ምስክርነታቸው የማይቀበል ተራ ሰዎች ቢሆኑም፣ እግዚአብሔር ግን የታላቁን የምሥራች የመጀመሪያ ምስክሮች እንዲሆኑ መረጣቸው። መልአኩም ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋል በማለት አበሰራቸው። ምልክቱም ሕፃኑ በጨርቅ ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ማግኘታቸው ነበር። ድንገትም ከሰማይ መላእክት ሰራዊት ጋር በመሆን ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ እያሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ።
እረኞቹም መልአኩ የነገራቸውን ለማየት ወደ ቤተልሔም በፍጥነት ሄዱ፤ ማርያምንና ዮሴፍን ሕፃኑንም በግርግም ተኝቶ አገኙት። ካዩትም በኋላ ስለ ሕፃኑ የተነገራቸውን ነገር ለሁሉም አወሩ። የሰሙትም ሁሉ በእረኞቹ ንግግር ተገረሙ፤ ማርያም ግን ይህንን ነገር ሁሉ በልቧ እያሰላሰለች ትጠብቀው ነበር። እረኞቹም እንደተባለላቸው ሁሉ ስላዩና ስለሰሙ እግዚአብሔርን እያከበሩና እያመሰገኑ ተመለሱ። ሕፃኑም በተወለደ በስምንተኛው ቀን እንደ ሕጉ ሊገረዝ በደረሰ ጊዜ፣ ገና ሳይጸነስ በመልአኩ እንደተባለው ስሙ ኢየሱስ ተብሎ ተጠራ። ይህ ስም ጌታችን ሕዝቡን ከኃጢአታቸው የሚያድን መሆኑን የሚያረጋግጥ የድኅነታችን መሠረት ነው።
ተግባራዊ የውይይት ጥያቄዎች
👉ሉቃስ የታሪክ ሰዎችን (አውግስጦስ ቄሣር፣ ሬንዮስ) መጥቀሱ ለወንጌሉ ታሪካዊ ተአማኒነት ምን ጠቀሜታ አለው?
👉የኢየሱስ በግርግም መወለድ (ቁ. 7) ስለ መንግሥቱ ተፈጥሮና ስለ ትሕትና ምን ያስተምረናል?
👉እግዚአብሔር ለምን የምሥራቹን ለአሕዛብ ወይም ለነገሥታት ሳይሆን መጀመሪያ ለእረኞች ገለጠ?
👉እረኞቹ የምሥራቹን ከሰሙ በኋላ ያደረጉት ፈጣን ምላሽ (ቁ. 15-16) ለኛ ምን ትምህርት ይሰጣል?
👉መላእክቱ ስለ ኢየሱስ የሰጡት ሦስት መጠሪያዎች (መድኃኒት፣ ክርስቶስ፣ ጌታ) ትርጉማቸው ምንድን ነው?
👉ማርያም “ይህን ሁሉ ነገር በልቧ ትጠብቀውና ታሰላስለው ነበር” (ቁ. 19) መባሉ ስለ እሷ መንፈሳዊ ጥልቀት ምን ይናገራል?
👉በምድር ላይ “ሰላም” መታወጁ ከክርስቶስ የማስታረቅ ስራ ጋር እንዴት ይያያዛል?
👉የኢየሱስ በስምንተኛው ቀን መገረዙና ስሙ መጠራቱ ስለ ሕግ ታማኝነትና ስለ መታዘዝ ምን ያስተምራል?
