በተደጋጋሚ የሚነሱ ጥያቄዎች (FAQs)
አንዳንድ ሰዎች ይቅርታ የማይደረግበት አንድ ኃጢአት አለ ብለው ይፈራሉ። ስለዚህ ይህን ኃጢአት ብናደርግ ደኅንነትን እናጣለን፥ ይቅርታም አይደረግልንም ብለው ይጨነቃሉ። ታዲያ ይህ «ይቅርታ የማይደረግለት ኃጢአት» ተብዬው ምንድን ነው?
ጥያቄ፡- ማቴ. 2፡22-32 አንብብ። ሀ) ፈሪሳዊያን ኢየሱስን በሰይጣን ኃይል አጋንንትን ያወጣል ማለታቸው በምን ምክንያት ሞኝነት ሆኖ ተቀጠረባቸው? (ቁ 26) ለ) ኢየሱስ አጋንንትን በእግዚአብሔር ኃይል የሚያወጣ ከሆነ፥ ይህ ምንን ያረጋግጣል? (ቁ 28)
በማቴ. 12፡22-32 ውስጥ ኢየሱስ ጋኔን ያደረበት ዓይነ ሥውርና ዱላ ሰው መፈወሱ ተጽፎአል (ቁ 22)። ይህን ተአምር የተመለከቱ ሰዎች ድርጊቱ መሢሐዊ ድርጊት መሆኑን ወዲያውኑ አስተዋሉ (ቁ 23)። እንደ መዝ (146)፡8፤ ኢሳ. 29፡18፤ 38፡5-6 ካሉት የብሉይ ኪዳን ትንቢቶች በመነሣት መሢሑ እንዲህ ያሉ ተአምራትን ይፈጽማል ብለው ይጠባበቁ እንደ ነበር ተጽፎአል። ስለዚህ «ይህ ሰው ኢየሱስ በእውነት መሢሑ የዳዊት ልጅ ይሆንን?» ሲሉ በአድናቆት ጠየቁ። ፈሪሳውያን ግን ስለ ኢየሱስ ኃይል ሌላ የሚሉት ነገር ነበራቸው። በብዔል ዜቡል ኃይል ይጠቀማል ሲሉ ከሰሱት፥ ብዔል ዜቡል የሰይጣን ሌላ ስሙ ነው (ቁ 24)።
ኢየሱስ ግን ፈሪሳውያን የመሠረቱበትን ክስ በሦስት መንገዶች መለሰ። በመጀመሪያ፥ ሰይጣን የራሱን ሥራ የሚያበላሽ ሞኝ አይደለም በማለት ትክክለኛ ያልሆነ ክሳቸውን ውድቅ አደረገው። ሰይጣን የሰውን ሕይወት በውስጡ በሚኖረው አጋንንት የሚያጠፋ ከሆነ አጋንንቱ ከሰውዬው እንዲወጣና ሰውዬውም ሕይወቱ ዳግም ታድሶ ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት እንዲኖረው ፈጽሞ አያደርግም። ይህ ደግሞ በሰውዬው ሕይወት ውስጥ የሚፈጽመውን ክፉ ሥራ የሚገታና መንግሥቱን የሚያፈርስበት ነው። ሰይጣን ደግሞ የራሱ የሆነ አጋንንትን አባሮ በማውጣት በፍጹም መንግሥቱን አያፈርስም አላቸው (ቁ 25-26)። ኢየሱስ በመጀመሪያ ለፈሪሳውያን የመለሰላቸው መልስ ሰይጣን ራሱን ስለማያጠፋ ክሳቸው ሐሰት መሆኑን የሚያመለክት ነው።
የኢየሱስ ሁለተኛው መልስ እርሱ አጋንንትን ያወጣበት የኃይሉ ታላቅነት፥ ያደረገው ታምራት ከእግዚአብሔር ዘንድ እንጂ ከሰይጣን አለመሆኑን በማረጋገጥ ክሳቸው ከእውነት የራቀ መሆኑን የሚያሳይ ነበር። እርሱ አጋንንትን ያወጣበትን ኃይል፥ እንዳንድ አይሁዳውያን ከሚፈጽሙት አጋንንትን የማስወጣት ሙከራ ጋር አመዛዝኖታል (ቁ. 27)፡፡ እነዚህ አጋንንትን እናስወጣለን የሚሉ አይሁዳውያን እንደተጠቀሱት የአስቄዋ ሰባት ልጆች ዓይነት ነበሩ (በሐዋ. 19፡13-16)። እነዚህ ሰዎች አጋንንትን በማውጣት ረገድ በመጠኑም ቢሆን የተሳካላቸው ይመስል ነበር። ግን ውጤታቸው የተወሰነና ጊዜያዊ ነበር። ይህ ሊሆን የቻለው እውነተኛ የሆነ መንፈሳዊ ኃይል ስላልነበረባቸው ነው። ከአይሁዶች ይልቅ የኢየሱስ አጋንንት አወጣጥ የሰይጣን መንግሥት በማፈራረስ ረገድ የበረታ ነበር። ታዲያ ፈሪሳውያንና ሕዝቡ የእነርሱ ወገን የሆኑ አጋንንትን እናወጣለን ሲሉ በሰይጣን ኃይል ትጠቀማላችሁ ብለው አይከስሱም ነበር። ግን ተአምራቶቹ በኃይል የተሞሉና የሰይጣንን መንግሥት ደምሳሽ የሆነ ኢየሱስ በሰይጣን ኃይል ትጠቀማለህ ብለው መከሰሳቸው እንዴት ሞኝነት ነበር? ለነገሩ ኢየሱስ አጋንንትን ያወጣ የነበረው በእግዚአብሔር ኃይል ነበር።
ፈሪሳውያን ተአምራቶቹን ከሰይጣን ኃይል ጋር ማያያዛቸው እንዴት ጅልነት (ሞኝነት) እንደ ነበረ የኢየሱስ የመጀመሪያዎቹ ሁለት መልሶች አረጋግጠዋል። በቁጥር 28 ውስጥ በሚገኘው በሦስተኛው መልሱ ፈሪሳውያን ተአምሩን ካዩ በኋላ ወደ ምን ዓይነት ድምዳሜ መድረስ እንደ ነበረባቸው አሳይቷቸዋል። እርሱ በተለየ ሁኔታ በመንፈስ ቅዱስ የተቀባ መሆኑን ተረድተው፥ «የእግዚአብሔር መንግሥት» እንደ መጣላቸው መቀበል ነበረባቸው። ማለት እርሱ የእስራኤል መሢሕ መሆኑን መገንዘብ ይገባቸው ነበር። ፈሪሳውያን ይህንን ማወቅ ለምን ነበረባቸው? ኢሳ 11፡1-5፤ 42፡1 እና 61፡1፤ እነዚህ ክፍሎች ሁሉ መሢሑ በልዩ ሁኔታ በእግዚአብሔር መንፈስ የተቀባ መሆኑን ይገልጻሉ። ኢየሱስ አጋንንትን የማስወጣት ከፍተኛ ኃይሉ፥ ይህን ልዩ ቅባት ለመቀባቱ ምስክር መሆኑን ተናግሮአል። በሌላ አነጋገር፥ አጋንንትን ሲያስወጣ፥ እርሱም መሢሑ፥ የእግዚአብሔር ንጉሥና የእግዚአብሔርን መንግሥት ወደ ምድር የሚያመጣ መሆኑን ማስመስከሩ በቁጥር 29 ውስጥ፥ አጋንንትን ማውጣቱ የመሢሕነቱ ማረጋገጫ ለመሆኑ ምሳሌ ያቀርባል።
አንድ ሌባ ወደ ኃይለኛ ሰው ቤት ገብቶ ንብረቱን ለመዝረፍ ያለው ብቸኛ መንገድ አስቀድሞ ኃይለኛውን ሰው ማሰር ነው ይላል። ኢየሱስ ያን ሲል ሰይጣንን በኃይለኛው ሰው ማስመሰሉ ነው። የሰይጣን አጋንንት ተሸነፉ
ማለት ሰይጣን ራሱ ተሸንፎ ታሰረ፥ ስለታሠረም አጋንንቱን ሊረዳቸው አይችልም ማለት ነው። ሰይጣን በኢየሱስ ከተሸነፈ፥ ኢየሱስ የእግዚአብሔር መሢሕ መሆኑ ነው። ለፈሪሳውያን የሰጠው ሦስተኛው የኢየሱስ መልስ አጋንንትን ያወጣበት ልዩ የሆነ የኃይል አጠቃቀም ሁኔታ እርሱ እግዚአብሔር ተስፋ የሰጠበት መሢሕ መሆኑን እንደሚመሰክር ነበር።
እነዚህ ፈሪሳውያን የእግዚአብሔርን መሢሕና የእግዚአብሔርን መንግሥት የሚጠባበቁ መሆናቸውን የሚናገሩ ሰዎች ነበሩ። መሢሑ ሊመጣ እንደሚቀበሉት ያወሱ ነበር። ነገር ግን ስማቴ. 12፡25-29 ውስጥ እንደተጻፈው ኢየሱስ «እኔ መሢሕ መሆኔን በልባችሁ ታውቃላችሁ ይላቸው ነበር። የብሉይ ኪዳንንም ትንቢቶች ታውቃላችሁ። ግልጽ ምስክር ሊሆኑ የሚችሉ ነገሮችንም በዓይናችሁ አይታችኋል። በአእምሮአችሁም እኔ መሢሕ መሆኔን አውቃችሁ ደምድማችኋል። ነገር ግን ይህን ሁሉ እያወቃችሁ አልተቀበላችሁኝም። እኔ መሢሕ መሆኔን እያወቃችሁ አልተቀበላችሁኝም፥ ሥራዩንም የሰይጣን ሥራ አደረጋችሁት» አላቸው። በዚሁ ምዕራፍ ከቁጥር 30-32 ባሉት ቁጥሮች ኢየሱስ ንግግሩን ያጠቃልላል። በልቡ ኢየሱስ ማን እንደሆነ እያወቀ የማይቀበለው የእርሱ ጠላት ነው (ቁ. 30)። ኢየሱስ መሢሕ መሆኑን በግልጽ የሚያረጋግጡ ሥራዎች መንፈስ ቅዱስ በሕይወቱ ውስጥ ሲፈጽም እነዚህ ሥራዎቹም መሢሕ መሆኑን እንደሚመሰክሩ የተረዳ፥ ነገር ግን አሁንም እርሱን በመሢሕነቱ የማይቀበል፥ እርሱ ይቅር አይባልም (ቁ 31)። እናም ኢየሱስ መሢሕ መሆኑን እያወቀ፥ እርሱ ከሰይጣን ነው ብሎ የሚከስውም ይቅርታ ውጭ ነው (ቁ 32)። እንዲህ ያለው ሰው ልቡን ያደነደነ ሰው በመሆኑ ወደ ክርስቶስ መጥቶ እንደ መሢሕ፣ እንደ መድኅንና ጌታ አድርጎ ሊቀበለው አይችልም።
ስለዚህ በማቴ. 12፡31 ውስጥ፥ በመንፈስ ቅዱስ ላይ የስድብ ቃል የተናገረ ይቅር አይባልም የተባለው ምን ማለት ነው? ይህ እንግዲህ መንፈስ ቅዱስን መሳደብ ብቻ አይደለም። እግዚአብሔርን መናቅም ብቻ አይደለም። ወንጌልንም ሰምቶ ክርስቶስን አለመቀበልም ብቻ አይደለም። እነዚህ ሁሉ የከፉ ተግባራት ስለሆኑ እግዚአብሔር ይቀጣቸዋል። ነገር ግን ማቴዎስ በምዕራፍ 12፡31 መንፈስ ቅዱስን ስለ መሳደብ ሲናገር ስለ እነዚህ ጥፋቶች መናገሩ አይደለም። ከጥቅሱ ጭብጥ እንደምንረዳው መንፈስ ቅዱስን መሳደብ ማለት ኢየሱስ በመንፈስ ቅዱስ በልዩ ሁኔታ የተቀባ መሢሕና አዳኝ መሆኑን እያወቁ ነገር ግን ልብን አደንድኖ ሆን ብሎ እርሱን አለመቀበልና ሥራውንም መቃወም ነው። ፈሪሳውያን ይህን ባደረጉ ጊዜ፥ ኢየሱስን ላለመቀበል ልባቸውን አጠነከሩ። ስለዚህም የእርሱን ይቅርታ ሳይቀበሉ ቀሩ።
ዛሬስ ቢሆን አንድ ሰው መንፈስ ቅዱስን በመሳደብ ይህንኑ ኃጢአት ሊሠራ ይችላል? መልሱ አዎን እና አይደለምም ይሆናል። ኢየሱስ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የሠራቸውን ታምራት ማንም ሰው ዛሬ በትክክል በግንባር እንደነበረው ሁኔታ ሊያይ አይችልም። ስለሆነም ማንም ሰው ይህን ፈሪሳውያን የሠሩትን ኃጢአት ራሱን መልሶ መሥራት አይችልም። በሌላ በኩል ግን የማያምኑ ሰዎች አሁንም ቢሆን በጣም ተመሳሳይ ኃጢአትን ሊፈጽሙ ይችላሉ። ዛሬም ቢሆን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ ስለመሆኑና የዓለም መድኃኒት ስለመሆኑ ብዙ ምልክቶችን ያሳያል። አሁንም የእርሱ መንፈስ በመጽሐፍ ቅዱስ በተሰበከው ቃል፥ በአማኞች ሕይወትና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በተደረጉ ታምራት አማካይነት እየሠራ ነው። የማያምን ሰው እነዚህን የኢየሱስ ሥራዎች ተመልክቶ እርሱ በእውነት ከእግዚአብሔር ዘንድ የመጣ ክርስቶስ የዓለም አዳኝ መሆኑን አውቆ ነገር ግን ችላ ቢለውና ባይቀበለው፥ ይህ ሰው ወደ ክርስቶስ ዘንድ በሚያድን እምነት ሊመጣ እስከማይችል ልቡን ያደነድናል።
እንግዲህ በማቴዎስ ምዕራፍ 12 ውስጥ መንፈስ ቅዱስን በመሳደብ ምክንያት ይቅር የማይባለው ኃጢአት፥ በዚህ ረገድ በማያምኑ ሰዎች የሚፈጸም ኃጢአት ነው እንጂ በእውነት ዳግም በተወለዱ ክርስቲያኖች የሚፈጸም በደል አይደለም። ስለሆነም ኢየሱስ ማን እንደሆነ እያወቁ በአንጻሩ እርሱን ያለመቀበል ኃጢአት ነው። ይቅርታ የማይደረግለት ኃጢአት ነው የተባለበት ምክንያት አንድ ሰው ክርስቶስ ማን እንደሆነ ካወቀ በኋላ ችላ ቢል፥ ልቡን ፍጹም ስለሚያደነድን እርሱን እንደ አዳኙ ለመቀበል በምንም ዓይነት አይመርጥም ማለት ነው። አንድ ሰው ሌላው ሰው ይህን ኃጢአት መፈጸሙን ሊያውቅ ይችላል? ኢየሱስ ፈሪሳውያን ይህን ኃጢአት መፈጸማቸውን አውቆ ነበር። ነገር ግን ዛሬ አንድ ሰው ሌላው ሰው ይህን ኃጢአት ለመፈጸሙ እርግጠኛ ሊሆን አይችልም። በሰብአዊና በውስን ግንዛቤአችን የሌላውን ሰው ልብና አእምሮ ማወቅ አንችልም። አንድ ሰው የክርስቶስን ማንነት ፍጹም ተገንዝቦ ሲያበቃ፥ ነገር ግን ከናካቴው ችላ በማለት ሳይቀበለው መቅረቱን ጠንቅቀን ማወቅ ፈጽሞ ያዳግተናል። ስለዚህ አንድ ወዳጃችን የሆነ ሰው ወይም ቤተሰብ ክርስቶስን ባለመቀበሉ ተስፋ መቁረጥ አይገባንም። በቃላችንና በተቀደሰ ሕይወት መመስከራችንን መቀጠልና የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ወደ እራሱ መልሶ እንዲያመጣቸው ጸሎታችንን አለማቋረጥ ያስፈልገናል። በመሆኑም ማንም በእውነት ዳግም የተወለደ ክርስቲያን መንፈስ ቅዱስን ስለ ተሳደብኩ ይቅር የማይባል ኃጢአት ሠርቻለሁ ብሎ ሊፈራና ሊጨነቅ አይገባም።
ምንጭ፡- “አስተምህሮ ክርስቶስና ደኅንነት”፤ ጽሑፍ፣ በዶ/ር ስቲቭ ስራውስ፤ ትርጉም በኃይሉ ልመንህ