Site icon

ኢየሱስ ሁሉን ቻይ እና ሁሉን የሚገዛ ነው

ኢየሱስ የእግዚአብሔር ባሕርያት አሉት 

ትናንትና ኢየሱስን በግልጽ «አምላክ» ብለው የጠሩትን ጥቅሶች ተመልክተን ነበር። ዛሬ ደግሞ ኢየሱስ፥ የእግዚአብሔር ባሕርያት እንዳሉትና እግዚአብሔር የሚፈጽማቸውን ተመሳሳይ ተግባራት እንደሚፈጽም የሚያስተምሩንን ጥቅሶች በአዲስ ኪዳን ውስጥ እንመለከታለን። 

ኢየሱስ ሁሉን ቻይ እና ሁሉን የሚገዛ ነው

ጥያቄ፡- ሀ) መዝሙር 65፡7፤ 89፡9፤ ኤፌሶን 1፡11 እና ኢዮብ 42፡2 አንብቡ። እነዚህ ጥቅሶች ስለ እግዚአብሔር ምንን ያስተምራሉ? ለ) ማቴዎስ 8፡26-27፤ 14፡19፤ 28፡18፤ 1ኛ ጴጥሮስ 3፡22 አንብቡ። እነዚህስ ጥቅሶች ስለ ኢየሱስ ምንን ያስተምራሉ? ሐህ ዮሐንስ 13፤ ቆላስይስ 3፡16-17 እና ዕብራውያን 1፡3 አንብቡ። በእነዚህ ጥቅሶች ውስጥ እንደ ተገለጸው አንዳንዶቹ የኢየሱስ ሥራዎች ምንድን ናቸው? 

እግዚአብሔር ሁሉን ቻይና ሁሉን ገዢ ነው። ይህ ታዲያ እግዚአብሔር ከባሕርያቱ ጋር የሚቃረኑ ተግባራትን ይፈጽማል ማለት አይደለም። ለምሳሌ ያህል፥ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው፤ ኃጢአትን ሊሠራ አይችልም። እግዚአብሔር ሁሉንም ሊያደርግ ይችላል በምንልበት ጊዜ ሥልጣን ሁሉ አለው፥ ዓለም ሁሉ በሥልጣኑ ሥር ነው፥ ለባሕርያቱ ተጻራሪ ያልሆኑትን ተግባራት ሁሉ ይፈጽማል ማለታችን ነው። መዝሙር 65፡7 እና መዝሙር 89፡9 በፍጥረቶቹ ሁሉ ላይ ሥልጣን እንዳለውና የዓለምን ሕዝቦችም በሥልጣኑ እንደሚያስተዳድር ይናገራሉ። በተለይ ኤፌሶን 1፡11 እግዚአብሔር በዚህ ዓለም ውስጥ ያሉትን ማንኛቸውንም ነገሮች በሥልጣኑ፥ እንደ ራሱ ፈቃድ እንደሚመራ ይገልጻል። በተጨማሪም ኢዮብ 42፡2 ስለ እግዚአብሔር የመፍጠር ችሎታ ይናገራል። 

ኢየሱስም እግዚአብሔር መሆኑን የሚያረጋግጥ የማይወሰን ኃይልና ሥልጣን አለው። በመዝሙር 89፡9 ላይ፥ እግዚአብሔር በኃይለኛው የባሕር ማዕበል ላይ ሥልጣን አለኝ እንዳለው ሁሉ፥ ኢየሱስ በማቴዎስ 8፡26-27 ላይ አስደናቂ ምሳሌን አሳይቷል። ማቴዎስ 28፡18 ኢየሱስ በፍጥረታት ሁሉ ላይ ኃይልና ሥልጣን እንዳለው ይነግረናል። 1ኛ ጴጥሮስ 3፡22 የኢየሱስ ሥልጣንና ኃይል ከመላእክትና ከሌሎችም ኃይላት በላይ መሆኑንና መንፈሳዊ ኃይላትም እንደ ተገዙለት ይገልጻል። ስለዚህ የኢየሱስ ችሎታ እርሱ እግዚአብሔር መሆኑን ያረጋግጣል። 

የኢየሱስ ኃይልና ሥልጣን፤ በአብዛኛው ሰማይና ምድርን በመፍጠር እና ሥርዓታቸውን ጠብቀው እንዲኖሩ በማድረግ ሥራው ውስጥ በግልጽ ይታያል። እግዚአብሔር ፈጣሪ ነው። ይሁን እንጂ ዮሐንስ 1፡3 ቃል ማለትም ኢየሱስ ሁሉንም ነገር እንደ ፈጠረ በማያሻማ ሁኔታ ይናገራል። ቆላስይስ 3፡16-17 ይህንን የበለጠ አጉልቶ ይገልጸዋል። ኢየሱስ የሚታየውንና የማይታየውን ሁሉ ፈጥሯል። ይህ መናፍስት የሆኑትንም ሁሉ ያጠቃልላል። ፈጣሪያቸው እንደ መሆኑ፥ እርሱ ከሁሉም ነገር በፊት ነበር። ሁሉንም ነገር በሥርዓት አድርጎ ደግፎ የያዘ እርሱ ነው (ዕብ 1፡3)። መጽሐፍ ቅዱስ ህልውና ያለውን ሁሉ ኢየሱስ ፈጠረ ሲል በግልጽ ይናገራል። እንግዲህ ይህ ሁሉ እርሱ እግዚአብሔር ለመሆኑ ምስክር ነው። 

ጥያቄ፡– የኢየሱስ ታላቅ ኃይልና ሥልጣን እንዴት መጽናናትን ይሰጣችኋል? ቢያንስ ሁለት መንገዶችን ጻፉ። 

የኢየሱስ ኃይልና ሥልጣን በብዙ መንገዶች ያጽናናናል። ኢየሱስ ወደ ሕይወታችን የሚመጣውን ነገር ሁሉ ይቆጣጠራል። ስለዚህ እርሱ ሳያውቅ በድንገት የሚደርስብን ነገር ሊኖር አይችልም። ኢየሱስ ለዓላማው ብሎ ካልፈቀደ በስተቀር፥ ሰብአዊም ሆነ አጋንንታዊ አደጋ ሊደርስብን ከቶ አይችልም። በእነዚህ አደጋዎች ላይም እርሱ ድልን እንድንቀዳጅ ይረዳናል። ኢየሱስ ለከበረ ዓላማው ካልፈቀደ በስተቀር፥ ምንም ዓይነት በሽታ እንደማያጠቃን እርግጠኞች ልንሆን ይገባል። በሽታውንም እንድንቋቋም እርሱ ኃይልን ይሰጠናል። የኢየሱስ ፈቃድ ካልሆነ በስተቀር፥ ፈተናም ሊያጋጥመን አይችልም። በፈተናም ላይ ድልን እንድንቀዳጅ እርሱ ኃይልን ይሰጠናል (1ኛ ቆሮ. 10፡13)። ኢየሱስ ሕይወታችንን ፍጹም ወደሆነ ፈቃዱ እንደሚመራ እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን (ምሳሌ 3፡5-6)።

ምንጭ፡- “አስተምህሮ ክርስቶስና ደኅንነት”፤ ጽሑፍ፣ በዶ/ር ስቲቭ ስራውስ፤ ትርጉም በኃይሉ ልመንህ

Exit mobile version